Friday, April 17, 2015

ሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ፖስተሮች በገዥው ፓርቲ እየተቀደዱብኝ ነው ሲል ገለጸ

April 17,2015
• ‹‹ወንብድና ነግሷል›› አቶ ዮናታን ተስፋዬ
የሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ ፖስተሮች በገዥው ፓርቲ ካድሬዎች ሆን ተብለው እየተቀደዱበት እንደሆነ የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ለነገረ ኢትዮጵያ ገለፀ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የለጠፋቸው ፖስተሮችን የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች እየተከታተሉ እንደቀደዷቸውና ላያቸው ላይ ማስታወቂያ እንዲለጠፍባቸው እየተደረገ መሆኑን አቶ ዮናታን ገልጸዋል፡፡
‹‹ፖስተሮቹ የተቀደዱት አንድ ቦታ ላይ አይደለም፡፡ በአሁኑ ወቅት ሰማያዊ ፓርቲ ወደ ህዝብ እንዳይደርስ እያደረገ የሚገኘው ገዥው ፓርቲ ሆን ብሎ እየተከታተለ እያስነሳ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ የሰማያዊ ፖስተሮች ሲቀደዱ የኢህአዴግ ፖስተሮች ላይ ግን ምንም አይነት ጉዳት አልደረሰም፡፡ ይህ ከፍርሃቱ የመነጨ ነው›› ያለው አቶ ዮናታን ተስፋዬ የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች የሰማያዊ ፓርቲን ፖስተሮች እየቀደዱ ከህዝብ እንዳይደርስ ለማድረግ ቢጥሩም በህዝቡ ትብብር አማራጫቸውን በማቅረብ ላይ በመሆናቸው ገዥው ፓርቲ ባሰበው መልኩ እንቅፋት መፍጠር እንዳልቻለ አስታውቋል፡፡
‹‹ውንብድና ነግሷል›› ያለው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ሆኖም ሰማያዊ ይህን የገዥው ፓርቲ ህገ ወጥነት በሞራል የበላይነት እና ከህዝብ ጋር በመተባበር እስከመጨረሻው ድረስ ለህዝብ እንደሚያጋልጥ ገልጾአል፡፡ የገዥውን ፓርቲ ድርጊት ሰማያዊ ፓርቲ ለምርጫ ቦርድም እንደሚያሳውቅ የገለጸው አቶ ዮናታን ፓርቲው ይህን የሚያደርግው ሂደቱን ለመጠበቅና የትግሉ አንድ አካል በመሆኑ እንጅ ምርጫ ቦርድ በጉዳዩ ላይ መፍትሄ ይሰጣል ብለን አይደለም ብሏል፡፡
አቶ ዮናታን አክሎም ‹‹ኢህአዴግ ወደ ህዝብ እንዳንደርስ የቻለውን ሁሉ ሊያደርግ ይችላል፡፡ በቀጣይነትም የዕጩዎችን ፎቶዎችና ሌሎች ፖስተሮችን ስንለጥፍ እንደሚቀዱ እናውቃለን፡፡ እኛም ወደ ትግሉ ስንገባ ኢህአዴግ እንዲህ አይነት ባህሪ እንዳለው ስለምናውቅ ይበልጡን ትግላችን እናጠናክራለን እንጅ ወደኋላ አንልም፡፡ እሱ 20 ፖስተሮችን ሲቀድ እኛ 40 ፖስተሮችን እየለጠፍን ወደ ህዝብ እንደርሳለን፡፡›› ሲል ገልጾአል፡፡

No comments: