Thursday, April 2, 2015

ከኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ ለኢትዮጵያ ወጣቶች የተላለፈ ማሳሰቢያ!!!

March 2,2015
ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሚገነዘበው በጥቂት ጠባብ አምባገነኖች የሚመራው የህወሓት/ኢ ህአዴግ ሥርዓት ላለፉት 23 አመታት በህዝብ መካከል የጥላቻና የጥርጣሬ መርዙን እየረጨ፤ ለዘመናት ተፋቅሮና ተከባብሮ የኖረውን ጠንካራ ህዝብ በተለያዩ ጐራዎች በመከፋፈል፤ እምቅ ጉልበቱን በማዳከም፤ ብሎም ትውልድ የማምከን ሰይጣናዊ አላማውን ለማሳካት ነጥሎ በማጥቃት፤ በሃገርና በህዝብ ላይ እጅግ ዘግናኝ ጭካኔዎችንና በደሎችን አየፈፀመና፣ ለከፍተኛ ስቃይና መከራ እየዳረገ እንደሚገኝ ይታወቃል። ይህ አርቆ ማየት የተሳነው ሥርዓት በተለይ ወጣቱ ትውልድ በራስ የመተማመንና አርቆ የማሰብ እምቅ ችሎታው እንዲዳከምና ባክኖ እንዲቀር፤ ብሄራዊ ስሜቱ ጨርሶ እንዲጠፋና ከግለኝነትና ከጐጠኝነት የማያልፍ ጠባብ አስተሳሰብ ውስጥ ሰጥሞ እንዲቀር፤ ብሎም ትውልድን የማምከንና ሃገር የማጥፋት እኩይ አላማውን ለማሳካት፤ በትምህርት ካሪኩለሙ ላይ ሳይቀር መርዙን ለመርጨት ሌት ከቀን እየኳተነ ይገኛል። በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማህበራዊ ሚዲያዎች አማካኝነት በጥቂት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል እያየን የምንገኘው አላስፈላጊና ዋጋቢስ ንትርክ፤ የሥርአቱ ትውልድን የማምከን እኩይ አላማ መገለጫ ተብሎ የሚገለፅ ቢመስልም፤ እውነታው ግን ሥርአቱ አላማውን ለማሳካት ቀጥሮም ሆነ አሳስቶ፤ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ፤ የተፅዕኖው ሰለባ በማድረግ እየተጠቀመባቸው ባሉ ጥቂት ወጣቶች አማካኝነት የሚካሄዱ መሰሪ ተግባራት ናቸው። ይሁንና ዛሬ ይህ ትዕይንት መረን እየለቀቀ የመጣበት ደረጃ ላይ ይገኛል።
EYNM New Logo
ሃገራችን ኢትዮጵያ ከ85 ያላነሱ ብሄር ብሄረሰቦችና ጐሳዎች የሚኖሩባት፤ የ92 ሚሊዮን ህዝብ መኖሪያ ውብ ሀገር ነች። ኢትዮጵያ ከ3000 ዓመት በላይ ታሪክ ያላት ሀገር ስትሆን፤ በአለም ላይ ከታየና ከተመዘገበ ታሪክ ሁሉ፤ ልዩ በሆነ መልኩ የተለያዩ ጎሳ/ዘር፣ ኃይማኖት፣ እምነት፣ አመለካከት ያላቸው ዜጐች የሚኖሩባት ቢሆንም፤ ለዘመናት ተከባብረው፣ ተቻችለውና፣ ተዋደው፤ በፍቅርና በአንድነት በመኖር እንደምሳሌ የሚጠቀሱና የሚወደሱ ናቸው። ልዩነቶች ኖሮባቸው እንኳን ጠላት በመጣ ጊዜ በኢትዮጵያዊነታቸው አንድ ላይ በጽናት በመቆም፤ ጠላትን አሳፍሮ በመመከትና ድባቅ በመምታት፤ የሀገር ሉዓላዊነትን ጠብቀው፤ ህዝባቸውን ከጠላት ጥቃት ለመከላከል ደማቸውን አፍስሰው አጥንታቸውን አድቅቀው መስዕዋትነትን በመክፈል፤ የምንወዳትና የምንመካባት ኢትዮጵያን በክብር አስረክበውናል።
ይህን ማለት ግን ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋና ሰላማዊ ነበር ማለት አይደለም። እውነታው በተለያዩ ጊዜአት የመጡ ስርዓቶች በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ በደል በመፈፀም የታሪክ አሸራ ጥለው አልፈዋል። እዚህ ጋር ግልፅ ሊሆንልን የሚገባው፤የተፈፀመው በደል በወቅቱ የነበሩት ገዢዎች ተግባር እንጂ፤በሃገራችን ኢትዮጵያ ታሪክ አንድም ጐሳ በምንም ሁኔታ በሌላው ላይ ለማጥቃት ተነስቶ አያውቅም። ይህ ታሪካችን በሃገራችን ኢትዮጵያ ዜጐች በፍቅርና በአንድነት ለዘመናት ተቻችለው ሊቆዩ የቻሉበት ዋንኛ ሚስጢር ከመሆኑም በላይ፤ ልንሸሽገው የማይቻለን፤ለአንድነታችን አይነተኛ ማረጋገጫ የሆነ እውነት ነው።
በመሆኑም በወጣትነታችን የዚህ ትውልድ ፈርጥ መሆናችንን አውቀን፤ አእምሮአችንን አስፍተን ታሪካችንን በጥልቀት በመመርመርና በመረዳት፤ብሎም እውነታውን ለይተን በማገናዘብ፤ በታሪክ የነበሩ ችግሮቻችንን አሶግደን፤ የተሻሉ መፍትሄዎችን በሰከነ ውይይት በማፍለቅ፤ አባቶቻችን በክብርና በአንድነት ያስረከቡንን ታላቅ ሃገር በክብር ለመጪው ትውልድ የማስረከብ ታሪካዊ ግዴታችንን እንድንወጣ ሲል፤ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በአብሮት ጥሪውን እያቀረበ የወያኔ መሳሪያም እንዳይሆን ያሳስባል።
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ

No comments: