Monday, April 13, 2015

በቤተመንግስት አካባቢ አለመተማመኑ በገሃድ እየታየ ነው * የቤተመንግስቱ ጠባቂዎች በሙሉ ወደ ቤንሻንጉል ተላኩ

April13,2015
(ዘ-ሐበሻ) ሕወሓት በሚያስተዳድረው መንግስት ውስጥ እርስ በ እርስ በባለስልጣናቱ መካከል ያለው አለመግባባት እና አለመተማመን እያየለ መሄዱ ቤተመንግስትም መድረሱ ተሰማ:: በተለይም የመለስን ራዕይ ገደል ይግባ የሚለው የአቶ አርከበ ቡድን ሃይለማርያም ደሳለኝን ይዞ እያየለ መሄዱና በሌሎች የሕወሓት አባላት ላይ ያለው አለመግባባት ወደ አለመተማመን ደርሶ የቤተመንግስት ጠባቂዎችን እንዳስቀየረ የዘ-ሐበሻ ምንጮች አጋለጡ::

ቤተመንግስቱን ሲጠብቁ የነበሩ የሕወሓት ተላላኪ ወታደሮች በጠቅላላ ወደ ቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ጉባ ወረዳ መላካቸውን ያጋለጡት የዘ-ሐበሻ ምንጮች እነዚህ ጠባቂዎች ደግሞ የአየር ሃይል አባላት መሆናቸው ጉዳዩን ከረር አድርጎታል:: ሕወሓት በሚመራው አየር ኃይል ውስጥ ያለው መታመስና በርካታ የአየር ሃይል አባላትም እየከዱ ወደ ጎረቤት ሃገራት መሰደድና ተቃዋሚዎችን መቀላቀል ያስደነገጠው መንግስት የአባይን ግድብ ትጠብቃላችሁ በሚል ሰንካላ ምክንያት መሳሪያቸውን በጠቅላላ አስቀምጠው ወደ ቤንሻንጉል እንዳዘዋወራቸውና በምትካቸውም ጆሮዋቸውን ቢቆርጧቸው ያለውን መከፋፈል የማያውቁ ወታደሮችን በቤተመንግስቱ አካባቢ አስፍሯል::

በገዢው ፓርቲ ውስጥ ያለው መከፋፈል ወደ እርስ በ እርስ መበላላት ሊያደርስ እንደሚችል ከውስጣቸው የሚወጡ መርጃዎች ይጠቁማሉ::

Friday, April 10, 2015

የመን ለሚገኙ ወገኖቻችን እንድረስላቸው!

April 10,2015
pg7-logoየመን የሚገኙ በመቶ ሺዎች የሚገመቱ ኢትዮጵያዊያን አደጋ ላይ ናቸው። ኢትዮጵያ ውስጥ ካለው የመብት አፈና፣ ሥራ አጥነት፣ ችጋርና ተስፋ ማጣት ለመሸሽ የራሳቸውንና የዘመዶቻቸውን ጥሪት አሟጠው ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ለሚሰደዱ ወገኖቻችን የመን መሸጋገሪያቸው ናት። ዛሬ የህወሓት ወዳጅ የሆኑም ያልሆኑም የየመን አምባገነን ገዢዎች እርስ በርሳቸው እየተላለቁ፤ ከምድር እሳት እየነደባት መሆኑ ሳያንስ ከሰማይም እሳት እየዘነበባት ነው።
እንኳን አሁንና በሰላሙም ጊዜ የመን ለኢትዮጵያዊያን ምቹ አልነበረችም። በበረሀ ጉዞ የዛሉ እግሮች፤ ከአቅማቸው በላይ በጫኑ ታንኳዎች ባህር በመሻገር የታወኩ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች የመን ጠረፍ ላይ የሚጠብቃቸው ተጨማሪ እንግልት፣ ስቃይና መደፈር ነበር። የመን የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ሕይወት እኛ ኢትዮጵያዊያን እንደ አገር የደረስበት አሳፋሪ ደረጃ መገለጫ ሆኖ ቆይቷል። በየመን፣ ወገኖቻችን ተደብድበዋል፤ አካላቸው በስለት ተዘልዝሏል፤ ሴቶች ብቻ ሳይሆን ወንዶችም ተደፍረዋል፤ ጓዳችን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ታፍኖ ለህወሓት ተላልፎ ተሰጥቶብናል። አሁን የመን እየነደደች ነው።
እጅግ የሚያሳስበን ቁጥራቸው ከመቶ ሺህ ይበልጣሉ ተብሎ የሚታሰበው በአሁኑ ሰዓት የመን ውስጥ የሚገኙ ወገኖቻችን እጣ ፈንታ ነው። የሌሎች አገሮች ዜጎች መንግሥቶቻቸው ደርሰውላቸው ከእቶኑ አውጥተዋቸዋለሁ። የኛ ወገኖች ግን የሚደርስላቸው መንግሥት የላቸውም።
ወገኖቻችን በዚህ ጭንቅ ውስጥ ባሉበት ሰዓት የህወሓት አገዛዝ ያንዣበበባቸው አደጋ የሚያባብሱ ተግባራትን እየወሰደ ነው። ሌሎች አገሮች በየመን ጉዳይ ላይ ያላቸውን አቋም በይፋ ከማሳወቃቸው በፊት ዜጎቻቸውን አስወጥተዋል። ህወሓት ግን ወገኖቻችን ለማዳን አንዳችም ጥረት ሳያደረግ ኃላፊነት በጎደለው መንገድ አንዱን ተፋላሚ ወገን በይፋ በመደገፍ በመቶ ሺህ የሚገመቱ ወገኖቻችን ከወላፈኑ ወደ እቶኑ ወርዉሯቸዋል። ገንዘብ የሚያገኝበት ከሆነ ወያኔ ወታደር ከመላክም ወደ ኋላ አይልም። እናም ለወገኖቻችን ካለ እኛ ማን አላቸው?
ስለ የመን ብቻ ሳይሆን ስለ ስደተኝነት በተነሳ ቁጥር አዕምሮዓችን ውስጥ የሚጉላላ ቁም ነገር አለ። እኛ ኢትዮጵያዊያን አገራችን ውስጥ ያለውን ሥርዓት ለውጠን፤ በምንወዳት አገራችን ውስጥ በክብር እንደመኖር እስመቼ አገራችንን ለህወሓት ወንበዴዎች ትተን እየሸሸን እንኖራለን? ስቃይና ሞት ተሸሽቶም አልተመለጠም። ሞት ኢትዮጵያዊያንን ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ሱዳን፣ ሰሀራ በረሃ፣ ሜዴትራኒያን ባህር፣ ቀይ ባህር፣ ሳውዲ አረቢያ እና የመን ውስጥ መሽጎ ይጠብቀናል። ኢትዮጵያዊያን በስደት ላይ እያለን የከፈልነው ዋጋ ተጠራቅሞ በአገራችን ውስጥ ለሥርዓት ለውጥ ውሎ ቢሆን ኖሮ ወያኔ አስወግደን በውሸት ሳይሆን በእውነት የበለፀገች ኢትዮጵያን መገንባት አንችልም ነበርን? እውን ወያኔ ከስልጣን ማስወገድ በስደት ምክንያት ያጣነውን ያህል ነብስና በስደት ላይ እየተቀበልነው ያለ ፍዳ ያህል ያስከፍላልን? ለምን በሀገራችንና በራሳችን ላይ እምነት አጣን? ይህ አፋጣኝ እርምት የሚሻ አብይ ጉዳይ ነው።
አርበኞች ግንቦት 7:የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የመን ለሚገኙ ወገኖቻችን ለመድረስ የተቻለንን ሁሉ እንድናደርግ ጥሪ ያደርጋል። ይህ ሥራ እየተሠራም ትኩረታችን ለዚህ ሁሉ መከራ የዳረገንን የህወሓት አምባገነን አገዛዝን ለማስወገድ በርትተን እንታገል ይላል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

የህወሕት ትግሬ ወጣቶች የሚሰሩት ድብቅ ስራና ሴራ።

April 10,2015
አማራ ወጣቶች የጋራ ንቅናቄ

በአንድ ወቅት በአይቲ (ICT) ኢንፎርሜሽን ቴክኖሌጅ ሳይንስ የትምህርት ክፍል ስልጠና ወደ ቻይና ከተላኩ ሁለት መቶ (200) ኢትዮጵያዊያን አንድ መቶ ዘጠና ስምንቱ (198) ትግሪወች ሁነው ተገኝተዋል።ጆሮ ለሰሚው ባዳ ነው አንድ ከአማራ አንድ ከኦሮሞ ሁለቶችን ለምልክት አስቀምጠዋቸዋል ።ኢትዮጵያ የብሔሮች እናት ቅብጥሴ ገለመሌ የሚባለው ለዚህ ነው ?ትግሬ የብሔሮች ክፉ የእንጀራ እናት ቢሆን የሚጠጋጋ ይመስለኛል ።

ትግራዊያን ከቻይናው ስልጠና ከተመለሱ በኋላ ስልክን ፣ፊስቡክን የተለያዩ ወብሳይቶችን በመጥለፍ (ሀክ) በማድረግ መሰማራታቸውን ጽሀይ የሞቀው አገር ያወቀው ሀቅ ሁኗል። በተጨማሪ በእያንዳንዱ ክፍለ ሀገር ቴሌኮሚኒኬሽን ተቋማ ባለበት ከተማ ውስጥ በሀላፊነት ተቀምጠው ስልክን ጠልፎ በመሰለል ስራ ተጠምደዋል ።

አሁን ደግሞ በተለየ ሁኔታ ፊስቡክ ሚዲያ ላይ በመሰግሰግ እልፍ አላፋ ዘመን አብሮ የኖረን ህዝብ ለማጣላት እና መልካም ግንኙነቱን ለማቃቃር ኦሮሞ ከአገራችን ይውጣ፣አማራ ከአገራችን ይውጣ፣ጉራጌ ከአገራችን ይውጣ አፋር ከአገራችን ይውጣ ወዘተረፈ እያሉ በመሰሪ አቋማቸው ለጸብ እና ለብጥብጥ ዋና ምክንያቶች ሁነዋል። ኦሮሞ ኢትዮጵያዊ ካልሆነ ፣አማራ ኢትዮጵያዊ ካልሆነ ፣ጉራጌ ኢትዮጵያዊ ካልሆነ ሁሉም ከአገር ከወጡ ማን ኢትዮጵይልዊ ሊሆን እንደሚችል ሊገባን አልቻለም ።

የወንበዴ ህወሕት ትግሬወችን ቅማላቸውን አራግፎ ሲርባቸው አብልቶ፣ሲጠማቸው አጠጥቶ፣ችግር ሲደርስባቸው ደብቆ የጎንደር ህዝብ አይደለም ሀላፊነቱን ያዙት ከደርግ የማይሻል የለም ብለው አዲስአበባ አራት ኪሎ ቤተ መንግስት ያስገባቸው???

ጅብ እስኪናከስ ያነክስ ነውና ነገሩ ዛሬ አማራውን የሌለው ህዝብ ጠላት ቅኝ ገዥ አድርጎ በመሳል የየዋሁን ህዝብ መልካም ግንኙነት በካፋ ደረጃ አቃቅሮታል ።

ዛሬ ዛሬ ደግሞ በህወሕት ትግሬ ወጣት ምልምሎች በፊስቡክ ሚዲያ ብቅ አድርገዋቸዋል ፣እውነት እና ንጋት እየቆየ ይጠራል እንዲሉ ለጊዜው በአሸናፊነት ስሜት ፈረስ ላይ ሁነው ቢጋልቡም ቅሉ ጊዜውን ጠብቆ ወደ ነበረበት መመለሱ አይቀሬ ነው ።

በአሁነ ስዓት ደግሞ አማራ በመምሰል በአጸያፊ ስድብ ኦሮሞን መሳደብ ፣ኦሮሞ በመምስል በአጸያፊ ስድብ አማራን መሳደብ ዘመቻ ስለወጡ የተከበርህ የኢትዮጵያ ወጣት ሆይ ይህን መሰሪ አቋም የማወቅ ግዴታ አለብህ እላለሁ ፣ከለዚያ ግን በእልህ ጎደና ተያይዘን መውደቃችን ነው እና ከተኛህበት የርኩስ መንፈስ ውስጥ ንቃ ንቃ ንቃ!!!!!!!!!

ለነጻነት የሚደረግ እውነተኛ የትግል ጥሪ

ገዛኸኝ አበበበ
ወያኔ ኢህአዲግ የስልጣን ወንበሩን በሀይል ከተቆናጠጠበት ጊዜ ጀምሮ በስልጣን በቆየባቸው በሃያ ሶስት አመታቶች በየጊዜው በህዝባችን ላይ የሚያደርሰው ግፍ እና ጭቆና ከእለት ወደ እለት እየጨመረ መምጣቱ በአደባባይ የሚታይ እውነታ ሲሆን ከዚህም ጨቋኝና ገዳይ ስርዓት የተነሳ የሀገሪቷ ዚጓች በሀገራቸው ላይ በሰላም መኖርና የነጻነትን ሀየር መተንፈስ በማይችሉበት ክፉ ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ::
በአሁኑ ጊዜ ከማንኛውም ጊዜ በተለየ መልኩ ገበሬው፣ ተማሪው፣ ፣ አስተማሪው ፣ ነጋዲው፣ ጋዜጠኛው ፣ ስፖርተኛው፣ ዘፋኙ፣ አርቲስቱ፣ ወዘተ......በማንኛውም እርከን ላይ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች በሀገራቸው ላይ በነጻነት መኖርን ስላልቻሉ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ሀገራቸውን ትተው እየወጡ በየጊዜው ለስደት ሲዳረጉ ይታያሉ:: ምክንያቱም ዜጓች በሀገራቸው በተረጋጋ ሁኔታ ለመኑር የሚያስፈልጋቸው ዋንኛውና ቁልፉ ነገር ሰላም እና ነጻነት ነውና::ማንኛውም ሰው በሚኖርበት ሀገር በሚኖርበት ሰፈር ወይም አካባቢ እና በሚኖርበት ቤት ውስጥ ሳይቀር በሰላምና በነጻነት መኖርን ይፈልጋል:: ነጻነት በምንም ዋጋ ሊተመን የማይችል ትልቅ ጸጋ ነውና:: ሰላም እና ነጻነት በሌለበት ሀገር የሚኖሩ ዜጓች፣ መብታቸው ይረገጣል ፣ ነጻነታቸው ይታፈናል ዜጓች ለእስር፣ ለሞት፣ እና ለስደት ይደጋሉ::በሀገራችን ኢትዮጵያ የምናየውም ይህንኑ ነው::
እንደ አለመታደል ሆኖ ሀገራችን ኢትዮጵያም በአለም ላይ ካሉት ሀገራት በግንባር ቀደምነት የሰው ልጆች ነጻነታቸውን እና መብታቸውን ከሚገፈፉበት ሀገር ተርታ እንደምትገኝና የሀገሪቷ ዜጓች በጨቋኙ ገዥ ስርዓት ነጻነታቸውን ተገፈው ባሪያ ሆነው የሚኖሩበት ሀገር እንደሆነች በየጊዜው ከሚወጡ አለም አቀፍ ሪፖርቶች መረዳት ይቻላል::
ዜጓች በከፍተኛ ሁኔታ ለስደት እየተዳረጉ ባሉበት በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የሚደረገው አፈና፣ እስራት እና ግድያው በከፍተኛ ሁኔታ ተባብሶ የሚገኝ ሲሆን ይህም በገሃድ እየታየ ያለ እውነታ ነው :: በእነዚህ ሃያ ሶስት አመታቶች በፋሺስቱ የወያኔ ቡድን ነጻነቱ እየተገፈፈና መብቱ እየተረገጠ ያለው የኢትዮጵያ ሕዝብም ከእንግዲህ ወዲህ ይሂን የወሮበሎች ቡድን እሽሩሩ እያሉ የመኖር አቅም ያለው አይመሰልም :.: በአሁኑ ጊዜ ከየአቅጣጫው ከሚሰሙ ነጻነት ናፋቂ የኢትዮጵያኖቸ ሕዝብ ጩኸት ድምጽ መረዳት እንደሚቻለው ሕዝባችን ለወያኔያዊ አንባገነን ስርዓት መገዛትን የጠላበትና ከመቺውም ጊዜ በተለየ መልኩ እምቢ አሻፈረኝ ብሎ ነጻነቱን ለማስመለስ በአንድነት ለመቋም የተነሳበት ዘመን ላይ የደረሰን በሚያስመስል መልኩ ከየቦታው የሚሰማው የነጻነትና የሰላም ናፋቂዎች የጀግንነት ድምጽ ምስክር ነው::
በቅርቡ እንኳን እንደምናየው የቀድሞው የግንቦት የግንቦት 7 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄያአሁኑ አርበኞች ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ዋና ጸሀፊ የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከየመን ታግተው በወያኔ እስር ቤት ታስረው በግፍ እየተሰቃዩ እንዳለ ይታወቃል የነጻነት ታጋዩ አቶ አንዳርጋቸው በወያኔ ሴራ ከየመን ታግተው በወያኔ እጅ ላይ መውደቃቸው ከተሰማ ጊዜ ጀምሮ የኢትዮጵያ ሕዝብ የወያኔን አውሬነት በይበልጥ በመረዳት ከዳር እስከ ዳር በአንድነት መቋሙን እያስመሰከረ ሲገኝ የፖለቲካ ግለቱም ጨምሮ የአረመኔው የወያኔን ቡድን በከፍተኛ ሁኔታ አርበድብዶት እንደሚገኝ ወያኔ ከሚሰራው ስራና ከሚያደርጋቸው ድርጊቷች ማወቅ ይቻላል::የአቶ አንዳርጋቸውን መታሰር ተከትሎ እየከረረ ያለውን የሕዝብን ቁጭትና ቁጣ ለማጥፋት በሚያስመስል መልኩ ይኼ አረመኔው መንግስት በአሁኑ ጊዜ በሀገር ቤት በሰላማዊ መንገድ ለመብታቸው እና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነት በህጋዊ መንገድ እንኮን ሳይቀር እየታገሉ ያሉትን ሰዎች ከየመንገዱ እየለቀመ እስር ቤት አስገብቶ እያሰቃያቸው እንዳለ ይታወቃል ::ይህንንም ተከትሎ ሁላችንም እንደምናውቀው የአንድነት ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባልና ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የፓርቲው ምክር ቤት አባል አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የአረና የሕዝብ ግንኙንት ኃላፊ አቶ አብረሃ ደስታና የሰማያዊ ፓርቲ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባዔ አቶ የሸዋስ አሰፋን ጨምሮ ሌሎችም እጅግ ብዙ ለየጻነታቸው የሚታገሉ ኢትዮጵያን ወገኖቻችን የወያኔ መንግስት በግፍ አስሯቸው እያሰቃያቸው እንደሚገኝ ይታወቃል::
ይኼ መንግስት እሱን የሚቃወሙትን ሰዎችንና በድፍረት እየተጋፈጡት ያሉትን የፖለቲካ መሪዎች አአሸባሪ የሚል የታርጋ ስም እየለጠፈላቸው ወደ እስር ቤት መወርወር የተጠናወጠው ክፉ ባህሪው ሆኖል:: የፖለቲካ መሪዎችንና የፖለቲካ ሰዎችን ማፈንና እየያዙ ወደ እስር ቤት መወርወር ይበልጥኑ ትግሉን እያከረረውና የኢትዮጵያን ሕዝብ ይበልጥኑ ለነጻነቱ በመታገል ለድል እያነሳሳው ነው እንጂ ፈጽሞ ከትግል ወደ ኋላ እይመለሰው እንዳይደለ የወያኔ ባለስልጣኖች ጠንቅቀው ሊያውቁት የሚገባቸው ነገር ይመስለኛል:: የኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነትን ተጠምቷል ::Freedom is more than food በአሁኑ ሰአት በሀገር ቤትም ሆነው በሰላማዊ መንገድ እየታገሉ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ይሁኑ ወይም በውጭ ሆነው በሁለገብ ትግል እየታገሉ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች አላማቸውም ሆነ ጥያቄያቸው አንድ ነው የስልጣን ወይም የገንዘብ ሳይሆን የነጻነት ጥያቄ ነው :: የኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነት ያስፈልገዋል ::እኛም ሰላምና ነጻነት የናፈቀን ህዝቦች መብታችንን ለማስከበር ለነጻነት ከሚታገሉ ድርጅቷች ጎን በመቆም ለነጻነታቸው ሲታገሉ በወያኔ አንባገነን ትህዛዝ ወደ እስር እየተወረወሩ እና በግፍ እየተሰቃዩ ላሉ ወገኖቻችን ከመንኛውም ጊዜ በተለየ መልኩ ሀገራዊ ስሜት ተሰሞቶን ልንጮህላቸውና የእነሱንም ፈለግ በመከተል ከሁለት አስርት አመታት በላይ የዜግነት መብታችንና እየረገጠና ነጻነታችንን እያፈነ ህዝባችንን ለስደት እያደረገ ያለውን ያለውን ይኼን ሰይጣናዊና አረመናዊውን ስርዓት በማንኛውም መንገድ በመታገል፣እውነተኛ ሰላምና ነጻነት በኢትዮጵያ ምድራችን እንዲመጣ ለማድረግ የወያኔን መንግስት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ዳግም እንዳይነሳ አከርካሪውን ሰብሮ ለመጣል በእውነተኛ ኢትዮጵያዊ ስሜት መነሳት ይጠበቅብናል እላለው::

ለዚህ ወቅታዊ የነጻነት የትግል ጥሪ ምላሽ ለመስጠት  የግንቦት 7 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አርበኞችን አስከትሎ መዋቀሩን በማሥፋት አርበኞች ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በሚል አዲሥ ስያሜ ለቀረበው ሀገርን የማዳን የትብብር ጥሪ ምላሽ በዲሞክራሴዊ ለውጥ በኢትዮጵ ድጋፍ ድርጅት በኖረውይ አዘጋጅነት ለቀረበው የምክክርና የትብብር ጥሪ ነውሪነታቸው በኖሮዌይ የሆነ ኢትዮጵያዊያዊንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን መልስ ለመስጠት ከምሥራቅ፣ ከምራብ፣ ከሰሜንና ደቡብ ኖርዌይ  እንዲሁም ካአዋሳኝ የአውሮፓ ሀገሮች አፕሪል (April18,,2015) ወደ ኖርዌይ ኦስሎ ይተማሉ፥
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ !!!
09፣04፣2015
ሚያዚያ 1 2007 ዓ/ም

Thursday, April 9, 2015

“ምስክር ፈላጊው ችሎት” – 27ተኛ የፍርድ ቤት ውሎ (ዞን 9)

April 9, 2015
በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ከጎንዬሽ ጉዳዬች ውጪ ለ25ተኛ ጊዜ (በአጠቃላይ ለ27ተኛ ጊዜ) የተሰየመው ችሎት ዛሬም የደረጃ ምስክሮችን ሲያሰማ ውሏል፡። ከሳምነትት በፌት የተሰየመው ችሎት አቃቤ ህግ 41 ምስክሮች አሉኝ ነገር ግን ላገኛቸው ስላልቻልኩ ተከሳሾቹ በማረሚያ ቤት ቆይተው ተጨማሪ ማፈላለጊያ ጊዜ ይሰጠኝ በማለት ጠይቆ ለዛሬ የተቀጠረ ቢሆንም ዛሬም “የሽብር ተግባሩ “ ዋና ምስክሮች ባለመገኘታቸው ፍተሻ ላይ ተገኝተናል ያሉ አምስት ምስክሮች ተሰምተዋል፡። የምስክሮቸን ቁጥርም 35 ነው በማለት ቀይሮታል፡፡Ethiopian arrested zone 9 bloggers
ባለፈው የተሰሙት 13 ምስክሮች ሲሆኑ በዛሬው ችሎት ባልተካደ ነገር ላይ ሲመሰክሩ የዋሉት የደረጃ ምስክሮች
14ተኛ ምስክር ተወዳጅ ኃ/ማርያም ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 34 ሲሆን የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ‹‹የመጣሁበት ኬዝ ግንቦት 7/2006 ዓ.ም በምኖርበት ልደታ 5ኛ አካባቢ የፌደራል ፖሊስ ታዛቢ ሁነኝ ብሎ ጠይቆኝ በታዛቢነት ያየሁትን ለመመስከር ነው፡፡ ማህሌት ጤና ጥበቃ ሚ/ር ትሰራለች መሰለኝ፣ እዚያ መስሪያ ቤት ፖሊስ ማህሌት ኮምፒውተርና ጠረጴዛ ላይ ያለውን ሲበረብር አይቻለሁ፡፡ መንግስት መስሪያ ቤት የምትጠቀምበት ኮምፒውተር ላይ የተገኙ ሰነዶች ላይ ማህሌት ስትፈርም እኛ ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡ የፈረምነው ግንቦት 7/2007 ዓ.ም ነበር፡፡ የገጹን ብዛት አሁን አላስታውስም፤ ወደ 40 ገጽ ይሆናል፡፡ እንግሊዝኛና አማርኛ ጽሁፎች አሉበት፡፡ የተወሰነ የፖለቲካ ይዘት የነበረው አለ፡፡ የፖለቲካ ፕሮግራም ማኒፌስቶ አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ ማህሌትን ሲጠይቃት ከኦነግ የወጣው የሌንጮ ፓርቲ ፕሮግራም ነው ብላለች፡፡ ጎስፕ ንግግሮችም አሉ›› ብሏል፡፡ ዳኛው ጎሲፕ በአማርኛ ምንድነው ሲላቸው ምስክሩ ‹‹ሽሙጥ ንግግር ነው›› ብለው መልሰዋል፡፡ ምስክሩ የተገኙ ሰነዶች ላይ ፌደራል ፖሊስ ሄደው እንደፈረሙና ይሄን ያደረጉትም ግንቦት 9/2006 ዓ.ም ነው ብለዋል፡
15ተኛ ምስክር ፀሐይ ብርሃኔ እድሜያቸው 33 የሆኑ የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ‹‹ግንቦት 7/2006 ዓ.ም ከቀኑ 4፡00 ፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ፖሊስ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አሳይቶ ቢሮ ሲፈተሽ ታዘብ ተብዬ ተገኝቼ ነበር፡፡ ሲ.ዲ እና ዲክሜንት ሲወሰድ አይቻለሁ፡፡ ከዚያ ፖሊስ በ9/2006 ዓ.ም ሄጄ በሶፍት ኮፒ የነበሩት ሰነዶች ፕሪንት ተደርገው ማህሌት የፈረመችባቸው ላይ ፈርሜያለሁ፡፡ በእንግሊዝኛና አማርኛ የተጻፉ ናቸው፡፡ በግምት ወደ 40 ገጽ ይሆናል፡፡ አብዛኛው የፖለቲካ ነክ ጽሑፎች ናቸው፡፡ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጽሑፎች አሉበት፡፡ ያየናቸው መረጃዎች ከእሷ ኮምፒውተር ላይ ስለመገኘታቸው አይተን ፈርመናል፡፡››
ለእኒህ ምስክር መስቀለኛ ጥያቄዎች ቀርበውላቸው ነበር፡፡
የጠበቆቹ መስቀለኛ ጥያቄ፡- ሲዲውን ማን እንዳመጣው
ታውቃለህ…ውስጡ ምን ነበረበት…
የምስክሩ መልስ፡- እኛ ራሳችን ቼክ አድርገናል፤ ባዶ ሲ.ዲ ነው፡፡
ጥያቄ፡- የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ብለሃል….ስንት ናቸው
መልስ፡- አንድ ብቻ አይደሉም
ጥያቄ፡- የተለያዩ ፓርቲዎች ሰነዶች ብለዋል እኮ….እነዚህ ላይ ሁሉ ፈርመዋል
መልስ፡- አሁን በትክክል የማስታውሰው የሌንጮ ፓርቲ ሰነድ ላይ መፈረሜን ነው፡፡ ሌሎች ላይ አልፈረምኩም፡፡
(አንድ ሰነድ ቀርቦላቸው ፊርማው የእሳቸው ስለመሆኑ እንዲለዩ ተደርገው የእሳቸው መሆኑን አረጋግጠው የፈረሙበትን ሰነድ ይዘት ግን እንደማያውቁ አስረድተዋል፡፡)
ፍርድ ቤቱ ‹‹40 ገጽ ማየትህን ተናግረሃል፤ 40 ገጽ ላይ ፍርመሃል፣ ይዘቱንስ ታውቃለህ›› ብሎ ጠይቋቸው ምስክሩ ‹‹እያንዳንዱ ሰነድ ላይ ፍረሜያለሁ፤ ግን አላነበብኩትም፡፡ ክፍት የስራ ማስታወቂያ የሚል ግን አይቻለሁ›› ብለዋል፡፡ በተለየ የትኛውን ነው ያነበብከው ለተባሉት ደግሞ ‹‹አሁን አላስታውስም፤ የሌንጮ ሰነድ ላይ ፈርሜያለሁ፡፡ ማህሌት ፖሊስ ሲጠይቃት ሌንጮ የራሳቸውን አዲስ ፓርቲ እያቋቋሙ እንደሆነ ስትናገር ሰምቻለሁ›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
16ተኛ ምስክር ዳግማዊ እንዳለ 25 ዓመታቸው ሲሆን የመንግስት ሰራተኛና የአ.አ ከተማ የካ ክ/ከተማ ነዋሪ ናቸው፡፡ በ5ኛ ተከሳሽ አጥናፍ ላይ ለመመስከር እንደመጡ ተናግረው የአባቱን ስም አላስታውስም ብለዋል፡፡
“ሚያዝያ 17/2006 ዓ.ም 11፡00 ገደማ ከስራ ወደ ቤት ስሄድ 22 ትራፊክ ፖሊስ ጀርባ ፌደራል ፖሊስ የፍርድ ቤት ወረቀት አሳይቶ ታዛቢ ሁነኝ ብሎኝ ተገኝቻለሁ፡፡ አጥናፍ ቤት ገብተን ሰነዶች ሲገኙ አይቻለሁ፡፡ ፍላሽ፣ ሴኪዩሪቲ ኢን ኤ ቦክስ የሚል መጽሐፍ፣ ሲ.ዲ ተገኝተዋል፡፡ ሌሎች ታዛቢዎችም ነበሩ፡፡ ሰነዶቹ ላይ አጥናፍ ሲፈርም እኛም ፈርመናል፡፡›› ብለዋል፡፡
17ኛ ምስክር፡- ሳምሶን ሲሳይ ይባላሉ፤ 29 ዓመታቸው ሲሆን በግል ስራ ላይ የተሰማሩ ናቸው፡፡ አድራሻቸው አ.አ የካ ክ/ከተማ ነው፡፡ አጥናፍ ላይ ለመመስከር መምጣታቸውን ተናግረዋል ‹‹ሚያዝያ 17/2006 ዓ.ም 11፡00 አካባቢ ትራፊክ ጽ/ቤት ጀርባ ፖሊሶች ታዘብልን ስላሉኝ ታዝቤያለሁ፡፡ ሲ.ዲ፣ ፍላሽ፣ የተለያዩ ዶክሜንቶች፣ ላፕቶፕ፣ ማስታወሻ ደብተሮች መገኘታቸውን አይቻለሁ፡፡ በዝርዝር አላስታውስም፡፡ ግን 150 አካባቢ መጽሐፍ ቆጥረናል፡፡ ፋክት መጽሔት ተገኝቷል፡፡ መጽሐፎቹ በእንግሊዝኛና አማርኛ የተጻፉ ናቸው፡፡ አጥናፍ የፈረመባቸው ላይ እኛም ፈርመናል፡፡›› ብለዋል፡፡
18ኛ ምስክር፡- እኒህ ምስክር ደግሞ በረከት ብርሃኔ የሚባሉ ሲሆን እድሜያው 29 ነው፡፡ በግል ስራ ላይ የተሰማሩና የአ.አ አራዳ ክ/ከተማ ነዋሪ ናቸው፡፡ 6ኛ ተከሳሽ ዘላለም ላይ ለመመስከር እንደመጡ በመግለጽ ዘላለምን በአካል ለይተው አሳይተዋል፡፡ ‹‹ግንቦት 16/2006 ዓ.ም ማዕከላዊ ለግል ጉዳይ ሄጄ ፖሊስ በጠየቀኝ መሰረት ታዝቤያለሁ፡፡ ሰነዶች ልናይ ስለሆነ እይልን አሉኝ፡፡ እሺ ብዬ ወደ ቢሮ ገባሁ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ይሆናል፡፡ እኛ ከገባን በኋላ ዘላለም ተጠርቶ መጣ፡፡ ላፕቶፑን ራሱ ፓስወርዱን ከፈተው፡፡ ከዚያ ከላፕቶፑ የወጡ ሰነዶች ፕሪንት ተደርገው ፈረምንባቸው፡፡ እንግሊዝኛም አማርኛም ነበር፡፡ ደሞ ምሳ ተጋብዘናል፡፡ ዘላለም ብላ ሲባል አልበላም አለ፡፡ አሁን ሰነዶቹ ምን እንደሆኑ አላውቅም፡፡ ዘላለም የፈረመበት ላይ ነው እኔ የፈረምኩት፡፡ ለማንበብ ግን ጊዜ አልነበረኝም፡፡ ስለዚህ ይዘቱን አላውቀውም፤ እሱ የፈረመበት ስለሆነ ብቻ ፈርሜያለሁ፡፡ አልፈርምም ያለው ሰነድ አልነበረም፡፡ ሌሎች ታዛቢዎችም ነበሩ፡፡ እነሱም ፈርመዋል›› ብለዋል፡፡
ምስክሮች ከመሰማታቸው አስቀድሞ አቃቤ ህግ ባለፈው የተሰጠው ቀጠሮ አጭር በመሆኑ ሌሎቹን ምሰክሮች ለማግኘት ረዘም ያለ ጊዜ ቀጠሮ አንዲሰጠው አንዲሁም አስመዝግቤያለው ካላቸው ሲዲዊች ውስጥ 7ቱ አንዲሰሙለት የጠየቀ ሲሆን የቀሩት ግን ሲዲውን የያዘው ባለሞያ ከአገር ውጪ በመሆኑ ማቅረብ አልቻልንም ብሏል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች ተከሳሾች ከታሰሩ አንድ አመት ሊሞላ ጥቂት አንደቀረ ምስክሮቸን ማዘጋጀት ቀደም ብሎ መሰራት የነበረበት የአቃቤ ህግ ስራ መሆኑን ነገር ግን በተደጋጋሚ እድል እየተሰጠው አንዳልተጠቀመበት በመጥቀስ ዛሬ የቀረቡት የሰው ምስክሮች መጨረሻ አንዲሆኑ እና የቀሩ ማስረጃዎቸን ለመስማት አጭር ቀጠሮ እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡ “ፍርድ ቤቱ” የአቃቤ ህግን ክርክር በመደገፍ የሚቀጥለውን ቀጠሮ ከአንድ ወር በላይ በማራዘም ግንቦት 18-21 2007 አም ድረስ እንዲሆን አንዲሁም የሲዲ ማስረጃዎቹ በወቅቱ ተሟልተው አንዲቀርቡና ቀሪ ምስክሮቹም በዚያው ቀን ወስኖ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡
የዞን9 ማስታወሻ
አንደሁልጊዜው ሁሉ የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ክስ ፓለቲካዊ ነው ያልተሰራ ወንጀል ምስክር አይገኝለትምና ፈጣን ፍትህን የማግኘት መብትን መቀለጃ ላደረገው ፍርድ ቤትም ሆነ የመንግስት ስራ አስፈጻሚ ጓደኞቻችንን ለመፍታት አሁንም ጊዜው አልረፈደም የሚለውን መልእክት ለማስተላለፍ አንወዳለን፡፡

በሳምንታዊዋ ‹‹ፍቱን›› መጽሔት ላይ፣ ከሰርካለም ፋሲል ጋር ያደረግነው አጭር ቃለ-ምልልስ (ኤልያስ ገብሩ )

April 9, 2015
‹‹የማምነው ነገር፣ የሀገሪቷ ችግር ሲፈታ፤ እስክንድርም አብሮ እንደሚፈታ ነው››
‹‹የስደት ህይወት ሁሉንም ነገር ከዜሮ ያስጀምርሃል››
‹‹የእስክንድር ፅናት እና ብርታት ከፈጣሪ የተሰጠው ፀጋ አድርጌ እመለከተዋለሁ››
‹‹በሀገራችን ጉዳይ ላይ ለመሳተፍ የግድ ፖለቲከኛ መሆን አይጠበቅብንም›› ሰርካለም ፋሲል (ጋዜጠኛ)
በአንባቢያን ዘንድ ታዋቂ የነበሩት ‹‹አስኳል››፣ ‹‹ሚኒሊክ‹‹ና ‹‹ሳተናው›› ጋዜጦች አንዷ አሳታሚ ነበረች፡፡ የ97 ምርጫን ተከትሎ በተፈጠረ ግርግር ለእስር ከተዳረጉት ጋዜጠኞች እና አሳታሚዎች መካከልም አንዷ ነች – ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል፡፡ በሀገራችን የግል ፕሬስን በመጀመር ፈር ቀዳጅ የሆነው የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ባለቤት ሰርካለም ልጃቸው ናፍቆትን የወለደችው በቃሊቲ እስር ቤት መሆኑ ይታወቃል፡፡Serkalem Fasil
ከእስር ከተለቀቁም በኋላ እስክንድር የጋዜጣ ፍቃድ ቢከለከልም ሀገሬን ጥዬ አልመሄድም በሚል አቋሙ በመጽናቱ ጽሑፎቹን በተለያዩ በውጭ ሀገር ባሉ ድረ-ገጾች ላይ ማቅረብ ቀጠለ፡፡ በሀገር ውስጥ የግል ጋዜጦች ላይም ቃለ-ምልልስ በማድረግ የግል ሀሳቡን በድፍረት በማቅረብ ላይ ሳለ ነበር በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥሮ መስከረም 03 ቀን 2004 ዓ.ም ለእስር የተዳረገው፡፡ በፍርድ ሂደትም 18 ዓመት ጽኑ እስራት ተፈረደበት፡፡ በዚህ ሁሉ ውጣ ውረድ ውስጥ ባለቤቱ ሰርካለም ከጎኑ ነበረች፡፡
ሰርካለም በአሁኑ ወቅት በስደት አሜሪካ ሀገር ትገኛለች፡፡ የዚህ ሳምንት የ‹‹ፍቱን›› እንግዳ የሆነችው እ.አ.አ በ2007 ዓ.ም ከዓለምአቀፍ የሴቶች ሚዲያ ፋውንዴሽን “Courage in Journalism Award” የሚል ሽልማት ካገኘች በኋላ የሽልማት ገንዘቡን ለአምነስቲ ኢንተርሽናል ተቋም ድጋፍ እንዲውል ያደረገችው ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል ነች፡፡ ጋዜጠኛ ኤልያስ ገብሩ የተወሰኑ ጥያቄዎችን (ስደትን፣ እስክንድርን፣ ልጃቸው ናፍቆትን በተመለከተ) በማንሳት እንዲህ አነጋግሯታል፡፡
በቅድሚያ ለቃለ-መልልሱ ፈቃደኛ በመሆንሽ በ‹‹ፍቱን›› መጽሔት ስም እናመሰግናለን፡፡
እኔም ለቃለ-ምልልሱ ዕድሉን ስለሰጣችሁኝ በአንባቢዎቻችሁ እና በራሴ ሥም አመሰግናለሁ።
ሰርካለም፣ ከሀገር ከወጣሽ ምን ያህል ጊዜ ሆነሽ? ለምን እንደወጣሽም በአጭሩ ንገሪን?
ከሀገር ከወጣሁ አንድ ዓመት ከስድስት ወር አካባቢ ሆኖኛል። ከሀገር የወጣሁትም በግሌ ወስኜ ሳይሆን፣ ከእስክንድር ጋር ለረጅም ጊዜ ተነጋግረንበት፣ በጋራ በደረስነው ውሳኔ መሰረት ከሀገር ልወጣ ችያለሁ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ፣ ማንም እንደሚያውቀው ልጃችን ናፍቆት የተወለደው እኔ እስር ውስጥ ሆኜ ነው። በ1998 ዓ.ም የአንድ ወር ተኩል ነብሰ ጡር ሆኜ ነበር የታሰርኩት። የወለድኩትን ልጅ ማቀፍም ሆነ ማጥባት ሳልችል ነው ከልጄ ጋር የተለያየሁት። ከእስር ስንፈታ፣ ልጃችን አንድ ዓመት ሊሆነው የአንድ ወር ዕድሜ ሲቀረው ነበር ዳግም የተገናኘነው። በአጠቃላይ የልጃችን ታሪክ ከእስር እና ከመከራ ጋር የተያያዘ ነው። በአሁኑ ሰዓት ካለአንዳች ወንጀል፣ በሀሰት ክስ እስክንድር በግፍ 18 ዓመት ተፈርዶበት ቃሊቲ ይገኛል። ትላንት ቃሊቲ የተወለደው ናፍቆት ዛሬ ነብስ አውቆ፣ የልጅነት መቦረቂያ ጊዜውን አባቱ ጋር እየተመላለሰ ማሳለፍ ዕጣ ፈንታው ሆኖ ነበር። እስክንድርም ከእስሩ በላይ የልጁ መንከራተትና ስቃይ በየዕለቱ እረፍት እንደነሳው በተደጋጋሚ ይገልጽልኝ ነበር። ከዚህም ባሻገር ‹‹ይህ ህፃን ጥላቻ ይዞ ማደግ የለበትም፣ ቂም ይዞ ማደግ የለበትም›› በሚል መነሻ ናፍቆትን ይዤ ከሀገር ለመውጣት ተገድጃለሁ።
የስደት ሕይወትን እንዴት አገኘሽው?
የስደትን ህይወት እንዲህ በቀላሉ መግለጽ እቸገራለሁ። የስደት ህይወት ሁሉንም ነገር ከዜሮ ያስጀምርሃል። የእውነት ሀገርህ የሚናፍቅህ፣ የእውነት መንደርህ የሚናፍቀው በስደት ዓለም ውስጥ ነው፤ በተለይ እንደእኔ በማኅበራዊ ህይወት ትስስር ቁርኝት ላደገ ሰው። አሜሪካ በርህን ዘግተህ ጎረቤት አታውቅ፣ ጎረቤትህ አያውቅህ፣ መንገድ ላይ ረጅም መንገድ ብቻህን ብትሄድ አንድም ሰው ላታይ በምትችልበት ሀገር፣ ራስን ከዚያ ጋር ማላመዱ ትንሽ ያስቸግራል። ሀገርህ ላይ ያለው ማኅበራዊ ህይወት ቢናፍቅህም፣ በሌላ ጎኑ ያለው ነፃነት ደግሞ እጅግ ያሥገርማል። የሰውን መብት እስካልነካህ፣ ያሻህን ብትሆን ቀና ብሎ የሚመለከትህ እና የሚያስፈራራህ አንዳችም ሀይል የለም። ‹‹ስጋት ውስጥ ይጥለኛል›› ብለህ የምትጠነቀቀው ወይም የምታስበው አይኖርም። አሜሪካ የሁሉም ነች፡፡ ሁሉም እኩል ይስተናገድበታል። ሁሉም እኩል መብት አለው። …ይህ ግን የሥደትን ህይወት ጣፋጭ አያደርገውም። …ከነምናምኗ ሀገርን የመሰለ ምንም ነገር የለም።

ባለቤትሽ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በሽብርተኝነት ወንጀል 18 ዓመት ተፈርዶበት በቃሊቲ እስር ቤት ይገኛል፡፡ አንቺም ከማዕከላዊ እስከ ቃሊቲ በነበረው እስሩ በጥየቃ አብረሽው ነበርሽ፡፡ አሁን ከልጃችሁ ናፍቆት ጋር በአሜሪካ ቨርጂኒያ ትገኛላችሁ፡፡ ባለቤትን ከጎን አጥቶ ሕይወትን መኖር እና ልጅን ለብቻ ማሳደግ እጅግ ከባድ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እስኪ በዚህ ጉዳይ ላይ ያለሽን ስሜት አጋሪን?
እስክንድር “አሸባሪ” የሚል የሀሰት ታርጋ ተለጥፎበት ከታሰረ አራት ዓመት ሊሞላው ትንሽ ወራቶች ይቀሩታል። እስክንድር ሀገሩን እና ወገኑን የሚወድ ኢትዮጵያዊ እንጂ፣ ተሸባሪዎቹ እንደሚገልጹት “አሸባሪ” ወይም ህዝብና ሀገርን የሚጎዳ አንዳችም ነገር አድርጎ እንደማያውቅ የኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ ሳይሆን፣ እነጆን ኬሪ በአደባባይ የመሰከሩለት ሀቅ ነው። የኢህአዴግ መንግሥት በግፍ፣ ማዕከላዊ ውስጥ (ለጊዜው ስማቸው ይቆየን) በሃላፊዎች ደረጃ ንፅህናው እየተነገረው ግን ‹‹ከአቅማችን በላይ ነው››፣ ‹‹ይታሰር ተብሏል፣ ትዕዛዝ ነው›› እየተባለ የታሰረ የግፍ እሥረኛ ነው። እስክንድር ላመነበት ነገር የሚያስከፍለውን ሁሉ ለመቀበል የተዘጋጀ ጠንካራ ሰው በመሆኑ፣ እኔም ለብቻዬ ልጃችንን ለማሳደግ በብዙ ማይልሶች ርቀት ላይ ብገኝም፣ ከሁለታችንም በኩል ጥንካሬ ብቻ እንደሚጠበቅብን አምናለሁ። በተለይ የእኛ ጥንካሬ፣ ለእስክንድር ሞራል እንደሚሆነው ስለማውቅ ልጅን ለብቻ ማሳደጉንም ሆነ ተለያይቶ በመኖሩ ጊዜያዊ አድርጌ ነው የምቆጥረው። ደግሞም እግዚያብሄር ይችላል!
በስደት ዓለም ሆናችሁ፣ ሰዎች ስለእስክንድር እና ስለእናንተ ያላቸው ያላቸው ቦታ …
….ከእኔ ልጀምር፣ ‹‹በእጅ የያዙት ወርቅ እንደመዳብ ነው›› ይላል የሀገሬ ሰው። እስክንድር በውጪ ዓለም በዚህ ደረጃ አድናቂ እና ተከታይ እንዳለው በጭራሽ አላውቅም። በተጓዝንበት ሥፍራ ሁሉ፣ ለእስክንድር ያላቸውን ክብር የሚገልጹ ሥደተኛ ወገኖቼ፣ ለእኔ እና ለናፍቆት የተለየ እንክብካቤና ፍቅር እያደረጉልን ይገኛሉ። ሁልጊዜ አዲስ ነው የምንሆንባቸው።
እስክንድር በእስር ላይም ሆኖ፣ መንፈሰ ጠንካራነቱ ወደር አይገኝለትም፡፡ ጠያቂ ሊያበረታታው ሄዶ ጠያቂውን አበረታቶ የሚመልስ ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ ነው፡፡ ስለእስክንድር የዓላማ ጽናት፣ ውስጣዊ ጥንካሬና ብርታት እሱን ለምታውቂው አንጻር ይህ ብትታቱ እነና ጽናቱ ከምን የመነጨ ነው?
የእስክንድር ፅናትና ብርታት ከምን የመነጨ እንደሆነ ለመግለፅ፣ ለመናገር ከቃላት በላይ ነው። በአጭሩ ማለት የምችለው፣ ከላይ (ከፈጣሪ) የተሰጠው ፀጋ አድርጌ ነው የምመለከተው። ምክንያቱም የሰው ልጅ የሆነ ቦታ ላይ ሲደክመው ወይም ተስፋ ሊቆርጥ ይችላል። እስክንድር ግን ብዙ መከራና ግፍ፣ እንግልት፣ በየጊዜው ቢደርስበትም፣ ለአንዲትም ቀን ‹‹አሁንስ ደከመኝ›› የሚል ነገር አስቦ አያውቅም። አካላዊ ስጋው ቢጎዳም መንፈሱ ግን ሁልጊዜ አዲስ፣ ሁልጊዜ ጠንካራ፣ ከራሱ አልፎ ሌላውን የሚያበረታታ ምርጥ የኢትዮጵያ ልጅ ነው። የእሱ መከራ መቀበል ከቆመለት ዓላማ ትንሽም እንደማያነቃንቀው በተግባር ያሳየ የዘመኑ ጀግና ነው። ሞራሉን ለመግደል በሀሰት ተወንጅሎ 18 ዓመት ቢፈረድበትም፣ ‹‹ለዴሞክራሲ መከፈል ያለበት ዋጋ ነው›› ብሎ ውስጡ ፀፀት እንደሌለበት አውቃለሁ። ውስጡ ትልቅ ሰላም እንዳለውም አውቃለሁ። ላመነበት ነገር የሚከፍለው ዋጋ ጥንካሬ እንጂ፣ ቁጭትን እንደማይፈጥርበት አውቃለሁ። ከምንም በላይ በሀሰት የተፈረደበት በመሆኑ፣ ለአሳሪዎቹን እንጂ የእሱ ጭንቅላት ነጻ በመሆኑ የጥንካሬው ምንጭም ሊሆን ይችላል – የሚፀፀትበትን ነገር ባለመፈፀሙ።
በባለሽበት ስቴት፣ በቅርብሽ ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና፣ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ከልጇ ሃሌይ ጋር አሉ፡፡ በ1997 ዓ.ም ምርጫን ተከትሎ በተፈጠረው ችግር፣ ከሁለቱም ጋር በቃሊቲ አብራችሁ ታስራችሁ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ በስደት ዓለም አብራችሁ ትገኛላችሁ፡፡ አጋጣሚውን እንዴት ታይዋለሽ?
እንዳጋጣሚ ሆኖ ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና፣ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ፣ ንግሥት ገብረህይወት (የቅንጅት ማዕከላዊ ኮሚቴ) …አሁን ደግሞ የቀድሞው የመንግሥት ጉዳዮች ኮሙኑኬሽን ሚኒስትር ደኤታ የነበሩት አቶ ኤርምያስ ለገሰ በአንድ አካባቢ እንገኛለን። ይህ ደግሞ፣ ቅርበታችንን ከጓደኝነት አልፎ ቤተሰብ እስከመሆን አድርሶናል። አንዳችን ሌላኛችን ቤት ለመድረስ ከአምስት ደቂቃ በላይ አይጠበቅብንም። በስደት ሀገር እንደዚህ ከምታውቀው እና ከምትግባባው ሰው ጋር አንድ አካባቢ መኖር፣ ውስጥህ ያለውን ብቸኝነት በትልቁ የሚቀርፍ ነው። በአጋጣሚ በአንድ አካባቢ መገኘታችን ለእኔ ትልቅ ደስታ ሰጥቶኛል።
በማኅበራዊ ድረ-ገጽ ላይ በንቁ በመሳተፍ እመለከትሻለሁ፡፡ ብዙ ጊዜ መረር ያሉ የቁጭት፣ የሀዘንና ልብን የሚነኩ ጽሑፎችን ትጽፊያለሽ፡፡ የጠቀስኳቸውን ስሜቶች ምን ፈጠራቸው?
በማኅበራዊ ድረ-ገፅ ላይ የሚጠበቅብኝን ወይም በምፈልገው መጠን እየተንቀሳቀስኩ እንዳልሆነ ይታወቀኛል። የዚህም ምክንያቱ፣ ልጄን በብቸኝነት ለማሳደግ የምሮጠው የህይወት ሩጫ በመጠኑም ቢሆን ገድቦኛል። ልጅ ትምህርት ቤት ማመላለስ፣ የልጄን ትምህርት በአግባቡ መከታተል እንዲሁም ለመኖር የሚያስችለንን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ መከወን በዋናነት የሚጠቀሱ ናቸው። ይህ ማለት ግን፣ ተሳትፎዬ ይቀንስ እንጂ፣ የሀገሬን ማንኛውንም ነገር ከመከታተል ወደ ኋላ ብዬ አላውቅም። ለተጠየኩት ጥያቄ መልሴ ግን፣ ባለችኝ ጊዜ የምፅፋት ነገር ምሬት እንደሚበዛባት አውቃለሁ። የዚህ ምሬት ምክንያት ደግሞ፣ ከሀገሬ መራቄ አንዱ ምክንያት ነው። ከሀገርህ ርቀህ ዜጎች ላይ የሚደርሰውን ጭቆና ማድመጥ በጣም ያማል። ምናልባትም ከመላመድ ብዛት፣ ውስጡ ሆነህ (ሀገርህ ላይ) እምብዛም አይታወቅም፡፡ ራቅ ስትል ግን፣ ‹‹እንደዚህ ለምን ይሆናል?››፣ ‹‹..እስከመቼ?›› የሚለው ነገርን ነገር በተደጋጋሚ እንድታስበው ያደርግሃል። በትንሹም ቢሆን የእኔም መረር ያለ ፅሁፍ ከዚህ የመነጨ ነው ብዬ አስባለሁ።

በአሜሪካ ሆነሽ፣ እስክንድርን በተመለከተ ምን እያደረግሽ ነው?

ባለሁበት ሀገር፣ እስክንድርን በተመለከተ፣ ከተለያዩ አካላት ጋር እገናኛለሁ። ስቴት ዲፓርትመንት ከጎንግረስ ማኖች (Congress man)፣ ከሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እንዲሁም የተለያዩ ተቋማት ስለእስክንድር የማያውቁት ነገር ባይኖርም፣ በተጨማሪ እኔም ስለሚገኝበት ሁኔታ እና በእስር ቤት ውስጥ ስለሚደርስበት የሰብዓዊ መብት ጥሰት አሳውቃቸዋለሁ። የሚገርመው ነገር በየሄድኩበት ትላልቅ ተቋማት በእስክንድር ጉዳይ ላይ ከበቂ በላይ መረጃ ያላቸው መሆኑን ነው። ‹‹እስክንድር አሸባሪ ነው›› የሚለውን የሀሰት ፍረጃ ጠንቅቀው እንደሚያውቁ በተደጋጋሚ በአንደበታቸው ሲገልፁ ይሰማል። ከኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን በተጨማሪ፣ በትልቅ የኃላፊነት ቦታ ላይ የሚገኙ ባለሥልጣኖች ለእስክንድር ያላቸውን ክብር መስማት የተለመደ ነው። …ገፍተው ሌላ ነገር ማድረግ ባይችሉም እስክንድርን የሚመለከቱት በተለየ መነፅር ነው። ለጊዜው በዚህ እንቅስቃሴ ላይ እገኛለሁ። ወደፊት ግን እስክንድርን በተመለከተ ለመስራት የታሰበ ሰፊ ሥራ አለ። ጊዜው ሲደርስ የምገልጸው ይሆናል።
በግልሽ እስክንድር ከእስር ወጥቶ በቅርቡ እንገናኛለን የሚል እምነት አለሽ?
እስክንድር የጊዜ ጉዳይ እንጂ ከእስር እንደሚፈታ ጥርጣሬ የለኝም። መቼ? ለሚለው ግን እስክንድር ከዚህ በፊት እንደገለጸው ጊዜው ሊያጥርም ሊረዝምም ይችላል። ነገ ይፈታል፣ ከነገወዲያ ይፈታል ብዬ የቀን ስሌት አላስቀመጥኩም። አንድ የማምነው ነገር፣ የሀገሪቷ ችግር ሲፈታ፣ እስክንድርም አብሮ እንደሚፈታ ነው። እስከዚያው ከጨለማው ስር የሚወጣውን ብርሃን እጠብቃለሁ።
በሀገር ጉዳይ ላይ፣ ከሴት እህቶቻችን ምን ይጠበቃል?
በሀገሬ ጉዳይ ላይ ከሴት እህቶቻችን ብቻ ሳይሆን ሁሉም ሀገር ወዳድ ወገኖቻችን ንቁ ተሳትፎ በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ማድረግ አለባቸው እላለሁ። በሀገራችን ጉዳይ ላይ ለመሳተፍ የግድ ፖለቲከኛ መሆን አይጠበቅብንም። ከዚህ ባለፈ ሩቅ ሆኜ፣ እንዲህ ቢደረግ፣ እንዲያ ቢደረግ የሚል ነገር ለማስተላለፍ የሞራል ብቃቱ የለኝም። ‹‹እንዲህ አድርጉ›› ለማለት ከህዝብ ጋር ሆነህ በሀገር ላይ ተቀምጠህ እንጂ፣ በርቀት ሆኜ የምናገረው አንዳችም ነገር የለም።
በሀገር ውስጥ ለሚገኙ (ለሚያውቁሽና ለማያውቁሽ) ወገኖችሽ ያለሽ መልዕክት …
በመጨረሻ… ለሚያውቁኝ ወገኖቼ የማስተላልፈው መልዕክት፣ እስክንድር ከታሰረ ጀምሮ በሞራልም በገንዘብም ከጎናችን ላልተለያችሁን ወገኖቼ በያላችሁበት ሰላማችሁ ይብዛ የሚል ነው፡፡

Wednesday, April 8, 2015

በ24ኛው ክፍለጦር ውስጥ የሚገኙ ወታደሮች ትጥቃቸውን እየሸጡ በመጥፋት ላይ ናቸው ተባለ

April 8,2015
ትህዲኤን እንደዘገበው በምዕራብ እዝ በ24ኛ ክ/ጦር ውስጥ የሚገኙ የገዢው ኢህአዴግ ጉጅሌ ወታደሮች በየወቅቱ መሳሪያቸውንና ትጥቃቸውን እየሸጡ በመጥፋት ላይ እንዳሉ ተገለፀ::

ትህዴን ከክፍለጦሩ ውስጥ ባገኘነው መረጃ መሰረት ሲል በዘገበው ዘገባው በምዕራብ እዝ 24ኛ ክ/ጦር የገዢው ኢህአደግ ጉጅሌ የሰራዊት አባላት በሚቀጠሩበት ወቅት በስርአቱ የሚገባላቸው ቃል ሰለማይተገበር ካላቸው የማህበራዊ ችግር የተነሳ መሳሪያዎቻቸውንና ትጥቃቸውን እየሸጡ በመጥፋት ላይ እንደሚገኙ ከገለፀ በኋላ። በተለይ ደግሞ የክፍለ ጦሩ አባላት 2ኛ ረጅመንት የሆኑት ሁለት ወታደሮች መጋቢት 20/ 2007 ዓ/ም ክፍላቸውን ትተው ዳንሻ አልፈው በጎንደር መንገድ በመሄድ ላይ እያሉ ለሲቪሉ ማህበረሰብ መሳሪያቸውንና ትጥቃቸውን ግዙን መሳፈሪያ አጥተናል እንዳሏቸው ሊታወቅ ተችሏል::

መረጃው በማከል እንዳስረዳው የክፍለ ጦሩ አዛዦች ለሰራዊቱ የማህበራዊ አገልግሎት ተብሎ የመጣውን ገንዘብ። ከታች እስከ ላይ ተሳስረው ለግል ጥቅማቸው እያዋሉት መሆናቸውን በሰራዊቱ ተገምግሞ ሲያበቃ። እስከ አሁን ድረስ ግን የተተገበረ ለውጥ እንደሌለ መረጃው ጨምሮ አስረድቷል ሲል ትህዴን ዘግቧል:
:

Monday, April 6, 2015

“ህዝቡ ነጻ አውጪዎችን መጠበቅ ሳይሆን ራሱን ነጻ መውጣት አለበት” አቶ ዮናታን ተስፋዬ (የሰማያዊ ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ )

April 5,2015
በእድሜ ትንሹና ገና ከመምጣቱ የህዝብን ትኩረት ለማግኘት የበቃው ሠማያዊ ፓርቲ በተለይም ከአንድነትና መኢአድ ሁለት ሁለት ቦታ መሰንጠቅ በኋላ ጎልቶ የመታየት ቀለሙ ይበልጥ የደመቀ ይመስላል ። ፓርቲው ከየት ተነስቶ እስከምን ይጓዛል ? የሚለውን ጥያቄ ከወቅታዊ ሁነቶች ጋር በማዛመድ የፓርቲው ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ከሆነው አቶ ዮናታን ተስፋዬ ጋር 1:50 ሰዓት የፈጀ ቃለመጠይቅ አካሂደናል ። በፌስ ቡክ የደረሱኝንና ሌሎች ጥያቄዎችን አንስቻለሁ
ኢትዮዴይሊፖስት -ሰማያዊ ፓርቲ ሕጋዊ እውቅና አግኝቶ የተቋቋመው መቼ ነው ?
አቶ ዮናታን – 2004 ዓ.ም ታህሳስ ወር ጠቅላላ ጉባኤውን አድርጎ በይፋ መመስረቱን አውጇል ። ምርጫ ቦርድ እውቅና ሰጥቶ የመዘገበው ግን ሐምሌ /2004 ዓ.ም ነው ።
Yonatan Tesfaye
Yonatan Tesfaye

ኢትዮዴይሊፖስት – ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች እያሉ ሰማያዊ ፓርቲ ለምን ተቋቋመ ? ቁጥሩን በአንድ ከመጨመር ባለፈ ሌሎች ያልሰሩትን ምን የመሰራት አላማ ኖሮት ነው?
አቶ ዮናታን – ከምርጫ 97 በኋላ የነበረውን የፖለቲካ ድብታ ሁሉም ሰው የሚረሳው አይደለም ። ከዚያ በኋላ የነበሩት የፖለቲካ ድርጅቶች በ3 አይነት የተዋቀሩ ናቸው ። በዶ/ር መረራ የሚመራው ህብረት በነበረበት ቀጥሏል፡፡ ቅንጅት ለሁለት ተከፍሎ አንዱ ትጥቅ ትግልን እንደ አማራጭ ወስዶ ከሀገር ወጥቷል፡፡ ሶስተኛው ደግሞ እነ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲን መስርተው የቻሉትን ያህል ሰላማዊ ትግሉን ለማስቀጠል ተንቀሳቅሰው ነበር ። በእነዚህ መካከል ግን የወቅቱ የፖለቲካ ሁኔታ ድብታ ውስጥ የከተተው የህብረተሰብ ክፍል ነበር ። ያን ድብታ የሚገፍ ሀይል ያስፈልግ ነበር ። ፖለቲካው ለኢህአዴግ የጎሳ ፖለቲካ እጅ የሰጠ የሚመስልበት ሁኔታ ነበር ። እነዚህንና ሌሎች ምክንያቶችን ከግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ የአዲሱን ትውልድ ጥያቄ ሊያስተጋባ የሚችል ፣ ዘመኑን የሚዋጅ፣ የፖለቲካ ድብታውን ሰብሮ ሊወጣ የሚችል የፖለቲካ ሀይል ያስፈልግ ነበር ። በዚያ ውስጥ ነው የተፈጠርነው ።
ኢትዮዴይሊፖስት – የምርጫ ወቅት ነውና ስለእሱ እናውራ ። በምርጫ ላይ ያላችሁ አቋም ምንድንው ? በፌስቡክ የደረሱኝ ተደጋጋሚ ጥያቄዎች በምርጫ ገዢውን ግንባር ከስልጣን ማውረድ ይቻላል ብላችሁ ታምናላችሁ ? የሚል ነው ። በእግርጥ ታምናላችሁ ?
አቶዮናታን – አናምንም ።
ኢትዮዴይሊፖስት – ካላመናችሁ ለምን በምርጫ ትወዳደራላችሁ?
አቶዮናታን – የሰማያዊ ፓርቲ ትልቁ ግብ ሕዝቡ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን ማድረግ ነው ። ሕዝቡ የስልጣን ባለቤት ሆነ ማለት ነጻነት አለው ማለት ነው ። ዲሞክራሲያዊ መብቱ ተከበረ ማለት ነው ። ወደ ምርጫው የገባነው የዋህ ሆነን አይደለም ። ኢሕአዴግ በምርጫ ይወርዳል የሚል ቀቢፀ ተስፋ ውስጥም አልገባንም ። የፓርላማ ወንበር አግኝተን ተመቻምቸን እንቀጥላለን የሚል ሀሳብ ውስጥም አልገባንም ። ግን ምርጫ ሰላማዊ ትግል በመደገፍ ረገድ ትልቅ አቅም ይኖረዋል ። እንደ ፖለቲካ ፓርቲ በምርጫ መወዳደር ፣ ለማሸነፍ መጣር ቢኖርም ትግላችን ከአገዛዝ ወደ ነጻነት መሆኑን ማንም አይስተውም ።
ኢትዮዴይሊፖስት – “ጉዟችን ከአገዛዝ ወደ ነጻነት ነው” ካላችሁ፣ ኢሕአዲግ በምርጫ ስልጣን ይለቃል የሚል የዋህነት ከሌላችሁ፣ የጦር መሳሪያ አንስተው ነጻነትን በጠመንጃ ሊያገኙ የሚሞክሩ ሀይሎችንም ካልደገፋችሁ በየትኛውም መንገድ ነው ከአገዛዝ ወደ ነጻነት የምትጓዙት?
አቶዮናታን – በየትኛውም መንገድ ሊሳካ ይችላል። ሂደቱ ነው የሚወስነው ። የቱም ቢሆን ረጅም ጊዜ ይወስዳል ።ትጥቅ ትግሉ እንደውም ከሰላማዊ ትግሉ የበለጠ ረጅም ጊዜ ይወስዳል ። ምክንያቱም የምትከፍላቸው ዋጋዎች ይበዛሉ ። በሀገርህ ልትደራደርባት ሁሉ ትችላለህ ። ሕወሓት ሀገራችንን ይህን አይነት ዋጋ አስከፍሏታል ። ከኤርትራ መገንጠል ጀምሮ አሰብን ማጣት ፣ ባድመ ላይ ሕይወት መክፈል ፣ በአለም አቀፍ ፖለቲካውም ላይ የከፈልነው ዋጋ አለ በትጥቅ ትግሉ ምክንያት ። አሁንም በዚያ መንገድ የሄዱ ሀይሎች ይህን ሁሉ አገናዝበው እንዲሆን ተስፋ አለኝ ።
ሰማያዊ ፖርቲ እንደ የፖለቲካ ፓርቲ ሰላማዊ ትግሉ ላይ ተጣብቆ ፣ የሚከፈለውን መስዋዕትነት ሁሉ ከፍሎ ፣ የሄደውን መንገድ ሁሉ ሄዶ ከግብ እንዲደርስ እናደርጋለን ስንል ዋናው ግባችን ሕዝብ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን እስከዛሬ ከሄድንበት የተለየ መንገድ መሄድ አለብን ፡፡ሰላማዊ ትግል ኢትዮጵያ ውስጥ አልተሞከረም ። የፓርቲ ፖለቲካ ነው ያለው ። በብዛት ቢሮ ውስጥ ከመቀመጥ ያለፈ አልተሰራም ። ሰማያዊ ፖርቲ የተለየ መንገድ እከተላለሁ ሲል እነዚህንና በአለም የተካሄዱ ሰላማዊ ትግሎችን ከሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ ጋር አዛምዶ ነው ።
ኢትዮዴይሊፖስት – የምርጫን ፖለቲካ እንደኪሳራ ቆጥረው ነፍጥ ያነሱ ሀይሎች አሉ ። እናንተ ደግሞ በምርጫ የስርአት ለውጥ ማምጣት እንደማይቻል አያመናችሁም ሰላማዊ ትግል የተባለ ሌላ አማራጭ አለ እያላችሁ ነው ። የእናንተ አማራጭ ከባለጠመንጃዎቹ የተሻለ መሆኑን አስረዳን እስቲ ።
አቶዮናታን – እኛ ከምርጫና ከጠመንጃ ፣ ከጠመንጃና ከሰላማዊ ትግል የቱ ይበልጣል? የሚለው ክርክር ውስጥ አንገባም ። ነባራዊ ሁኔታውን ማየት ግን የተሻለ ነው ። ደርግ ንጉሡን ገልብጦ በጠመንጃ ስልጣን ያዘ ። ራሱ ደርግም የወረዳው በጠመንጃ ነው ። ኢሕአዴግም በጠመንጃ ስልጣን ይዞ ምርጫ የሚባል የጨዋታ ሜዳ አበጅቶ አልወርድም ነው ያለው ። ኢሕአዴግ በጠመንጃ ቢወርድም መጪው ያለጠመንጃ ለመውረዱ ዋስትና የለም ። የሰላማዊ ትግል አማራጭ ግን ሕዝቡን የስልጣን ባለቤት የሚያደርግ ነው ፡፡
Yonatan Tesfaye
Yonatan Tesfaye

ኢትዮዴይሊፖስት – አሁንም እኮ ሕዝብ የስልጣን ባለቤት ሆነ እየተባለ ነው ።
አቶዮናታን – ልክ ነህ ይባላል ። ሕዝብ የስልጣን ባለቤት ቢሆን ግን በጋምቤላ ፣ በኦሮሚያ ፣ በሶማሌ፣ በአማራው አካባቢ ያሉ አይነት ግጭቶች ውስጥ አይገባም ። ይሁንናም ግን በሰላማዊ ትግል የሚመጣ ስልጣን “እምቢኝ አሻፈረኝ ፤ከተቀመጥኩበት ወንበር አልነሳም” ለማለት አይመችም ። ወደ ስልጣን መውጫ ብቻ ሳይሆን መውረጃውንም ቀድሞ ያበጀ ስርዓት ነው የሚመጣው ። ኢሕአዴግን በሰላማዊ ትግል ከስልጣን ያወረደ ሕዝብ ቀጣዩንም በተመሳሳይ ለማውረድ የሚከለክለው ሀይል አይኖርም ። በ1997 ትልቅ ንቅናቄ ተፈጥሯል፡፡ ግን በትግል የመጣ አልነበረምና ካሸፈ ። ሕዝብ በትግል መውጣት አለበት ። የግድ በሚሊዮኖች መቆጠር የለበትም ።አምስትና አስር ሺህ ሆኖም በህዝብ የበላይነት ፣ በሕግ የበላይነት ስርዓቱን እየፈተነ ፣ የስርዓቱን አገልጋዮች እያሸመደመደ ምንም ማድረግ እንዳይችሉ ምክንያት የሚያሳጣ ሀይል መፍጠር ይችላል ። ይህ ኢትዮጵያ ውስጥ አልተሞከረም ። በ1997 ያን ያህል ሕዝብ አይተን እንደረካነው አሁን ደግሞ በትግል ራሱን ችሎ የሚመጣ ሀይል እንፍጠር ነው አያልን ያለነው ። ሰላማዊ ትግል ሲባል ፖለቲካና ፓርቲ ላይ የታሰረ ይመስላል ፡፡ አይደለም ። ምንም እንኳን የፖለቲካ ሀይሉ እነዚያን ጥያቄዎች ቢያሳነም ብዙ ሰው ፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ ሳይገባ ፣ በትግሉ ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆን ማድረግ ይቻላል ፡፡
ኢትዮዴይሊፖስት – የምርጫና ጠመንጃ ትግል መዳረሻቸው ይታወቃል ። የሰላማዊ ትግል መዳረሻስ ምንድነው ?
አቶዮናታን – መወሰን አይቻልም ። ምናልባት በሕዝብም ሀይል ፣ በዲፕሎማሲም ፣ በአጠቃላይ በዲሞክራሲ ሀይሎች ግፊት አስገድደን ሊወድቅ ይችላል ። ሰላማዊ የሽግግር ሀይል ሊቋቋም ይችላል ። አብዮት ሊነሳ ይችላል ። ሕዝባዊ እምቢተኝነት ሊነሳ ይችላል ። መገመት አይቻልም ። እዚያ ጫፍ ላይ ከመድረሱ በፊት ግን ሕዝቡ መንቃት አለበት ። እንደሚችል ማሳየት መቻል አለብን ።ህዝቡ ነጻ አውጪዎችን መጠበቅ ሳይሆን ራሱን ነጻ መውጣት አለበት ። ይህን ማድረግ እንደሚችል ግን ቀድሞ ግንዛቤን ማዳበር ያስፈልጋል ፡፡
ኢትዮዴይሊፖስት – ከሌሎች ሀገሮች ተሞክሮ አንጻር ሰላማዊ ትግል ከምርጫም ሆነ ከጠመንጃ ትግል የተሻለ ውጤታማ የሚያደርገው ምን አለ ?
አቶ ዮናታን – በምርጫው ለውጥ ማምጣትን የተካ የተሻለ የዲሞክራሲ ስርዓት የለም ። በምርጫ ለውጥ ማምጣት ሲያቅት ፣ ስልጣን የያዘው አካል ምርጫው ነጻ እንዳይሆን ሊያደርግና ለምርጫ ሕግ አልገዛ ሲል ነው ወደ ጠመንጃም ሆነ ሰላማዊ ትግል የሚገባው ። ሰላማዊ ትግልም ሆነ የጠመንጃው ትግል በአንዳንድ ቦታ ውጤታማ ላይሆኑ ይችላሉ ። ይህ የሚሆነው አምባገነን የሚባሉትና የዲሞክራሲ መብት የሚጥሱት መንግስታት ለሕዝቡ የተሻለ ቁሳዊ ሕይወት የሚሰጡበት ሁኔታ አለ ። ለምሳሌ እነቻይናና ኢንዶኔዢያን ማየት ይቻላል ፡፡ስለዚህ ምንም እንኳ ለውጥና መደብለ ፓርቲ ስርዓት ብትፈልግ እንኳ ትግሉን የሚገዳደር ቁሳዊ እድገት ስላለ ይህ ለጊዜውም ቢሆን ውጤቱን ሊያኮላሸው ወይም ትግሉን ሊያራዝመው ይችላል ፡፡
ኢትዮዴይሊፖስት – ከሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ሲታይስ ?
አቶ ዮናታን – ወደ እሱ ልመጣልህ ነው ። ሀገራችን በጣም አስቸጋሪ የሆነ ሁኔታ ውስጥ ነው እየገባች ያለችው ። ለልጅ ልጆቻችን የምናወርሰው ብድር በጣም ጣራ እየነካ ነው ። አሁን ያለብን ከፍተኛ ችግር የሚተመንም አይደለም ።የሀይማኖት ችግር አለ ። ሙስሊሞቹ በንቃት ስለሚታገሉት የእነሱ ጎላ እንጂ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሀይማኖት ( ማህበረቅዱሳን ) ውስጥ የተፈጠረውን ችግር እናስታውሳለን ። የሀገር ውስጥና የውጭ የተባሉ ሁለት ሲኖዶሶች አሉ ። ሙስና በቤተክርስቲያን ውስጥ በጣም ተስፋፍቷል ። ይህ እየተስፋፋ ሲመጣ ህብረተሰብ የለውጥ ሂደት ውስጥ መግባቱ አይቀርም ።
በኢኮኖሚው ያለውን ችግር ስታየው ከጊዜ ወደ ጊዜ የደሀው ቁጥር በጣም እየጨመረ ፣ ከሀብታሙ ጋር ያለው ልዩነት እጅግ እየሰፋ ነው ። የስራ አጡ ቁጥር ከልክ እያለፈ ፣ የትምህርት ስርዓቱ የድህነትና ስራ አጥነት መጠኑን እያስፋፋው ነው ። አብዛኛው ስራ መፍጠር ሳይሆን ተዛዥ ሆኖ እንዲወጣ የሚያደርግ የትምህርት ስርዓት ነው ያለው ። ለሕዝብ አገልግሎት የሚሰጡት ትራንስፖርት ፣ መብራት ፣ ውሃ ፣ ስልክ በሙሉ እየወደቁ ነው ። ከእነዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ የኢሕአዴግ ከጥንት ጀምሮ የነበረና አሁንም ድረስ የሕዝብ ተቀባይነት ያላስገኘለት ሀገራዊ እይታ አለ ። ለኢትዮጵያ ያለው ክብር ኢሕአዴግ የሚታወቀው ባንዲን በማራከስና ጨርቅ ነው በማለት ነው ። ከዚያ የባንዲራ ቀን ብለው ቢጀምሩም ቅቡልነቱን አላገኙትም ። እነዚህ ሁሉ ችግሮች እየባሱ እንጂ እየረገቡ አልመጡም ። ስለዚህ የእኛ ጥያቄ ማንሳት በራሱ ሳይሆን ለውጡን የሚያመጣው የገዢው ስርዓት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋ መምጣት ነው ። ከስህተቱ መማር አለመቻሉም ነው ፡፡
በሰብአዊ መብት ላይ ያለው ደግሞ ሁሉንም ይነካል ። ፖለቲከኞች ታሰሩ ፤ ዝም ተባለ ። የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊዎች በገፍ ታሰሩ ፤ ሕዝቡ ዝም አለ ፡፡ በድረገጽ ያገባናል ብለው የሚጦምሩ ወጣቶች ታሰሩ ። ጋዜጠኞች ተሰደዱ ። ጋዜጦች ተዘጉ ። አፈናው አየሰፋ ሲሄድ ሕዝቡን ወደ ትግሉ ይቀላቅሉታል ። አሁን ላይ የሚታዩ ነገሮች ባይኖሩም ችግሮቹ እየሰፉ ሲሄዱና እንደ ፖለቲካ ሀይል ግፊት ስታደርግ አንድ እርምጃ ወደፊት ይሆናል ። የሁሉም የዲሞክራሲ ሀይሎች የመጨረሻ ግብ ተመሳሳይ ነው ። ሕዝብ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን ማድረግ ነው ። በንጉሱ ጊዜ የነበረው ጥያቄ አሁንም አለ፡፡ ጥያቄውን ደግሞ ኢሕአዴግም አልመለሰውም ። እስኪመለስ ይቀጥላል ። መልሱ በማንኛውም መንገድ ሊመጣ ይችላል ። ግን ዘላቂ ውጤት የሚኖረው በሰላማዊ ( ነፍጥ አልባ ) ትግል ሲመጣ ነው ፡፡ ሕዝቡ ላይ “ይቻላል!” የሚለውን ስሜት መፍጠር እንጂ ኢህአዴግ በየትኛውም መንገድ የደከመ ድርጅት ነው ።
ኢትዮዴይሊፖስት – ብዙዎቹን ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች የሚያመሳስላቸው የምርጫ ሰሞን ከያሉበት ብቅ ብቅ በማለት ድምጻቸውን ማሰማት ፣ በምርጫው ሳይቃናቸው ሲቀር ወደ መፍረስø ድንዛዜ መግባትና ቀጣዩን አምስት አመት መጠበቅ ነው ። ከዚህ አንጻር ሰማያዊ ፓርቲ በ2007 ምርጫ አንድም የምክር ቤትና የክልል ወንበር ባያገኝ ፣ አንድም አባሉ ባይመረጥ ከምርጫው በኋላ የሚኖረው አቋም ምን ይሆናል?
አቶዮናታን – ጥሩ ጥያቄ ነው ። እንደውም ሰማያዊ ፓርቲ የተመሰረተበት ምክንያት ይሄ ነው ።
ኢትዮዴይሊፖስት – የቱ ምክንያት ?
አቶ ዮናታን – እስከዛሬ የነበሩት የፖለቲካ ድርጅቶች በፓርቲ ፖለቲካ ውስጥ ተወስነው አንድ ሁኔታ ሲከሰት መግለጫ ከማውጣት ያለፈ ፋይዳ ያልነበራቸው ነበሩ ። ይህን ስል ግን የተቃዋሚዎች ድክመት ብቻ አይደለም ። ገዢው ስርዓትም መንገዱን ዘግቶታል ። የተዘጋውን ለማስከፈትና ሕዝቡ ጋር ለመድረስ ግን መታገል ያለብን እኛ ነን ።ስለዚህ ሰማያዊ ፓርቲ ሲመሰረትም ይህን አሳካለሁ ብሎ ነው ። ሰማያዊ ፓርቲ በብርቱ መንቀሳቀስ የጀመረው አሁን ምርጫው ሲመጣ አይደለም ። ገና ከመሰረቱ ጀምሮ ነው ዋጋ መክፈል የጀመረው ። አሁን የምናደርገው ትግል መቀመጫ ለማግኘት አይደለም ። ትልቁ ትኩረታችንም አይደለም ።
ኢትዮዴይሊፖስት – መቀመጫ ለማግኘት የማይታገል ምርጫ ተወዳዳሪ አለ ?
አቶዮናታን – በሂደቱ ውስጥ ሕዝቡ ጋር መድረስ ባለብን መጠን መድረስ ነው ዋና ጉዳያችን ። ኢ/ር ያልቃል ከምርጫ ሲሰረዝ “ትልቁን አላማዬን ተነጠቅሁ” የሚል ስሜት አልነበረውም ። በፊቱንም ጓጉቶ አልነበረም የተመዘገበው ። ማንም የፓርቲያችን አባል ለመመረጥ ጉጉት ያለው አይመስለኝም ። ስንመዘገብም “ይቻላል !” የሚለውን የለውጥ መንፈስ በሁለት እግሩ ለማቆም ነው ድካምና ልፋታችን:: እንደ ፖለቲካ ፖርቲ ይህን ያህል ወንበር አገኛለሁ ብለህ ልታቅድ ትችላለህ ። ፖለቲካው ላይ ለወጥ የሚያመጣው ግን ሁለትና አስር ወንበር ማግኘቱ ባለመሆኑ ምርጫው ሲያልፍም አሁን ባለንበት ሁኔታ የምንቀጥል ይሆናል ፡፡
ኢትዮ ዴይሊ ፖስት ከአቶ ዮናታን ጋር ያደረገውን ቃለመጠይቅ ቀጣይ ክፍል
-ግን አቶ ዮናታን የባቡር መንገዱ ላይ የመኪናዎች አደጋ መብዛት የኢሕአዴግ ችግር ነው እንዴ የአሽከርካሪው ጥፋት ለምን አይሆንም የመኪና መሄዳ መንገድ እያለ የባቡር አጥር ላይ መውጣታቸው ለምን የመንግስት ችግር ይሆናል
– ሰማያዊ ፖርቲ የዛሬ 24 አመት ስልጣን ይዞ ቢሆን ኖሮ አሁን በሀገሪቱ ካለው ሁኔታ የትኛዎቹ እንዳይኖሩ ወይም እንዲኖሩ ያደርግ ነበገር የሚል ነው
-በአንዳንዶች አስተያየት አሁን ያለው ሰማያዊ ፓርቲ ምንም ስልጣን ላይኖረው እንኳ ለተቃዋሚዎች እልቅና አይሰጥም ተቃዋሚዎች ብዙም ለውጥ እንደሚያመጡና እሱ ብቻ የለውጥ ባለቤት እንደሆነ ያስባል የሚል ትችት ያቀርብባችኋል ስለዚህ ይህ ፓርቲ ስልጣን ቢኖረውና ጠመንጃ ፖሊ ደህንነት ቢኖረው ጭራሽ ወደ አምባገነንነት ይሄል የሚል ጥርጣሬ ያላቸው ጥቂት አይደሉም ይህን ሀሳብ በምን ታስተባብለዋለህ ፡፡
– ሰማያዊ ፓርቲን ከግንቦት 7 ከድምጻችን ይሰማ እና ከሙስሊሙ እንቅስቃሴ ጋር አያይዘው የሚያስቡ አሉ በተለይም የሙስሊሙ እንቅስቃሴ ደማቅ ስለሆነ ሰማያዊ ፖርቲ ራሱን ማስተዋወቂያና የሙስሊሙ ወገንተኛ አድርጎ ተጠቅሞበታል የሚሉ አሰብ ያንተ ምላሽ ምንድነው
– አንዳንድ ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶችና የፕሬስ ውጤቶች ውጭ ሀገር ለሚሄ ሰዎች የመኖሪያ ፍቃድ እንዲያገኙ አባላቸው እንደሆኑና ገዢው ግንባር ተጽእኖ እንዲደረግባቸው የሚገልጽ ሀሰተኛ ደብዳቤ በመጻፍና መታወቂያ በመስጠት ከፍተኛ ገቢ ያገኛሉ ሰማያዊ ፖርቲ ለአንድም ሰው ቢሆን መታወቂያ ላለመሸጡ እርግጠኛ ሆኖ መናገር ይችላል
እነዚህን እና ሌሎች ጥያቄወችን በሚቀጥለው ሳምንት ይዘንላቹ እንቀርባለን።

Saturday, April 4, 2015

የት ሂዱ ነው? ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም

April 4,2015

"ኑሮዬም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም እዚሁ ነው፤ ከኢትዮጵያ አፈር የሚለየኝ የለም"

ዓለም ሁሉ ጠላን፤ በየትም አገር እየሄድን “የሙጢኝ!” ከራሳችን መሬት በጉልበት እየተነቀልን፣ ከራሳችን ቤት እየተባረርን፤ ከተወለድንበትና ከአደግንበት አካባቢ እየተፈናቀልን፣ ጭራውን ቆልምሞ እንደሚሮጥ ባለቤቱ እንዳባረረው ውሻ በአገኘነው አቅጣጫ እየሮጥን፣ እጃችንን እያርገበገብን “የሙጢኝ!” እንላለን፤ የፈራነውን ሞት በየመንገዱ እናገኘዋለን፤ ሞትን ሸሽተን ሞት ያጋጥመናል፤ የሞቱ ልዩነት አይታየንም፤ በየመንገዱ የሚያጋጥመው ሞት የውርደት ሞት ነው፤ የብቸኛነት ሞት ነው፤ ዘመድ-ወዳጅ ለቀብር የማይገኝበት ሞት ነው፤ ሠለስት፣ አርባ፣ ሙታመት የማይወጣበት ሞት ነው፤ ባዕድ ምስጥ ያላሳደገውን አካል የሚበላበት ነው፤ የሞት ሞት ነው፡፡

ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ከአገር አስወጥቶ ባዶ መሬት ብቻ ይፈልግ ይመስል የወያኔ ሎሌዎች በማስፈራራት ሁሉም አገሩን እየተወላቸው እንዲሄድ ያቀዱ ይመስላል፤ ጥንት ኢሰመጉ በምሠራበት ጊዜ በየጊዜው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ሰዎችን በማስፈራራት ሰላማቸውን ለመረበሽ ወደስደት ወይም ወደወንጀል ተግባር የሚመሩ የወያኔ አባሎች ነበሩ፤ አሁን እንደገና ብቅ ማለት ጀምረዋል፤ ሕጋዊ ሥርዓት እየላላ ጉልበተኞች በግላቸው ለዘረፋና ለቅሚያ እየተሰማሩ ይመስላል፡፡

ስለራሴ ላውራ፤ ከእኔ የሚፈልጉት ምን እንደሆነ እርግጠኛ አይደለሁም፤ የሚፈልጉት የምኖርበትን አፓርትመንት እንደሆነም አላውቅም፤ በእኔ ቤት ያለ ሀብት የሚባል ለወያኔ አገልጋዮች የሚጠቅም ሁለት የገብረ ክርስቶስ ስዕሎች ብቻ ናቸው፤ (በዚህ አጋጣሚ እነዚህን ስዕሎች ለመግዛት የሚፈልግ ያነጋግረኝ)፤ ከዚህ ሌላ ለወያኔ ዋጋ የሌላቸው መጻሕፍት ናቸው፤ ስለዚህም አሁን በእኔ ላይ የተሰነዘረው ጥቃት እኔን ወደስደት ለመግፋት የሚደረግ ሙከራ ይሆናል፤ በ1992 ግድም ተሞክሮ ነበር፤ አልሠራም፤ ዛሬ ይበልጥ አይሠራም፤ ለማናቸውም ምክንያቱን በትክክል ለማወቅ ባልችልም በእኔ ላይ ዘመቻ መጀመሩን አንድ በቅርብ ከማውቀው ወያኔ በትክክል ተረድቻለሁ፤ ይህንን ዘመቻ በመምራት ላይ ያለውንም ሰው ማንነት ተነግሮኛል፡፡

ይህ አገር የአንድ ጉልበተኛ ቡድን ነው ብዬ አልቀበልም፤ የአባቶቼና የእናቶቼ፣ የአያቶቼና የቅድማያቶቼ አጥንትና ደም የገነባው አገር ነው፤ ማንም ለስደት አይዳርገኝም፤ ማንም አስፈራርቶ ኢትዮጵያዊነት መብቴን መግፈፍ አይችልም፤ አልፈቅድለትም፤ በግልጽ በማያጠራጥር ቋንቋ ኑሮዬም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም እዚሁ ነው፤ ከኢትዮጵያ አፈር የሚለየኝ የለም፡፡

እኔን ለማጥቃት ላሰፈሰፉት ወያኔዎችና ሎሌዎቻቸው አንድ እውነት ልንገራቸው፤– በፈለጉትና በተመቻቸው መንገድ በእኔ ላይ በጉልበታቸው ግፍ ቢፈጽሙ ነገ በነሱ ላይ የባሰ ግፍ እንደሚደርስባቸው ይወቁት፤ ሁልጊዜም ከሕግ የወጣ ጉልበተኛነት ጉልበተኛነትን ያነግሣል፤ በመግደል ድል ይገኛል ብለው የሚያምኑ ወያኔዎች ትንሽ ቆም ብለው ያስቡ፤ በመሞትም ድል ይገኛል፤ በመሞትም ማሸነፍ ይቻላል፡፡

በእኔ ላይ የዘመተው ወያኔ ወይም ሎሌ ማናቸውም ሥራ ውጤት እንዳለው ማወቅ አለበት፤ አንድ ነገር አድርጎ ምንም ዓይነት ውጤት አያስከትልም ብሎ ማሰብ ድንቁርና ነው፤ ይህ የሳይንስ ሕግ ነው፤ For every action there is a reaction ይላል!

(ምንጭ: Mesfin Wolde-Mariam Blog)

Friday, April 3, 2015

ቴድሮስ አድሃኖም መዋሸቱን ቀጥሏል? ኢትዮጵያውያን አሁንም ከየመን ለመውጣት እርዳታ አላገኙም

April 3, 2015
ቴድሮስ አድሃኖም መዋሸቱን ቀጥሏል? ኢትዮጵያውያን አሁንም ከየመን ለመውጣት እርዳታ አላገኙም
ትላንት አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ (Agence France‑Presse) እንደዘገበው ከሆን ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዲህ ብለዋል “ኢትዮጵያ በሁቲ አማጽያን ከስልጣን የተባረረውን የየመን መንግስት በቆራጥነት ትደግፋለች፣ ሳውዲ አረብያ የየመን መንግስትን ወደስልጣን ለመመለስ ጣልቃ መግባትዋም ትክክለኛ እርምጃ ነው” ብለዋል።
በአሁኑ ሰዓት ኃይለማርያም ኢትዮጵያ “በቆራጥነት ትደግፈዋለች…” ያሉት የየመን ምንግስት ፕሬዝዳንት አገር ጥለው በመሸሽ ሳውዲ አረብያ የሚገኙ ሲሆን አማጽያኑ ደግሞ ዋና ከተማዋን ሰንዓንና የወደብ ከተማዋን ኤደንን ተቆጣጥረው ይገኛሉ።
በቅድሚያ ከ50,000 በላይ ኢትዮጵያውያውያን መውጫ አጥተው በሳውዲ አረብያ የጦር አውሮፕላኖች እየተደበደቡ ባለበት ሁኔታ እና አማጽያኑ መላውን የመን እየተቆጣጠሩ ባለበት ሁኔታ ለተባረረው ይየመን መንግስት በግልጽ ድጋፍ መስጠት የሚያሳየው ነገር ቢኖር ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የወያኔ አዛዦቻቸው ምን ያህል በየመን መውጫ አጥተው ለሚገኙት ለኢትዮጵያውያን ደንታ እንደሌላቸው ነው።
ይህ በዚህ እንዳለ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የሚመሩት ቴድሮስ አድሃኖም የተለመደ “የአዛኝ ቅቤ አንጓች” ውሸታቸውን ማውራት ቀጥለዋል።
ቴድሮስ አድሃኖም በራሳቸው ጌዜ በጀልባ ተንጠላጥለው ጅቡቲ የደረሱትን ኢትዮጵያውያን ከየመን ያስወጡ በማስመሰል “እስከ አሁን 30 ኢትዮጵያውያን ጅቡቲ ደርሰው ኢንባሲያችን ተቀብሏቸዋል” ብለዋል።
ቴድሮስ አድሃኖም አያይዘውም “ሰንዓ የሚገኘው ኤምባሲያችን ወደ ዛሬ አጥቢያ የጦር መሳሪያ ድብደባ ደርሶበታል፡፡ አምባሳደሩም ሌሎች ዲፕሎማቶችም ደህና ናቸው፡፡ የብዙ አገሮች ኤምባሲዎች የተዘጉ ቢሆንም ከዜጐቻችን በፊት አንወጣም ብለው ዜጐቻችንን ለመርዳት ጥረት እያደረጉ ላሉ ዲፕሎማቶችና አስተዳደር ሰራተኞች ምስጋናየን አቀርባለሁ፡፡” ብለዋል።
የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስቴር ተብዬው ለተባረረው የየመን መንግስት በግልጽ ድጋፋቸውን እየሰጡ ባለበት ሁኔታ ነው እንግዲህ ቴድሮስ አድሃኖም አማጽያኑ በተቆጣጠሩት ከተማ የሚገኘው ኢምባሲያቸው እና ሰራተኞቹ በየመን የሚገኙ ስደተኛ ኢትዮጵያውያንን ለመታደግ በሰንዓ መሽገው እንደሚገኙ እየተናገሩ ያሉት።
ቴድሮስ አድሃኖም ቀደም ሲል በፌስቡክ ገጻቸው የአዲስ አበባ ስልክ ቁጥሮችን አስቀምጠው በየመን የምትገኙ ኢትዮጵያውያን እርዳታ ከፈለጋችሁ ደውሉልን ማለታቸው ይታወሳል።
ሌሎች ሃገሮች አውሮፕላኖችን እና መርከቦችን ወደ የመን በመላክ ዜጎቻቸውን በማውጣት ላይ ናቸው።
ECADF

በጋሞ ጎፋ ፖሊስ በህዝብ ላይ የጭካኔ እርምጃ ወሰደ

April 3,2015
በጋሞ ጎፋ ዞን ምዕራብ አባያ ወረዳ አልጌ ቀበሌ ፖሊስ በንፁሃን ላይ የጭካኔ እርምጃ መውሰዱን የአካባቢው ነዋሪዎች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ በአባያ ሀይቅ ዙሪያ በእርሻ ስራ ላይ የተሰማሩት ነዋሪዎች መሬት ትንባሆ ለሚያለማ ባለሀብት እንደተሰጠባቸው መነገሩን ተከትሎ የአካባቢው ሽማግሌዎች ከሶስት ጊዜ በላይ ለክልሉ አስተዳደር ማመልከቻ ቢያስገቡም መልስ ሊያገኙ እንዳልቻሉ ገልጸዋል፡፡ የክልሉ አስተዳደር ምንም አይነት መልስ ባይሰጥም የዞኑ አስተዳደር ‹‹መሬቱ ትንባሆ ለሚያለማ ባለሀብት ተሰጥቷል፡፡›› የሚል ውሳኔ በማስተላለፉ ነዋሪዎቹ ይህን የዞኑን አስተዳደር ውሳኔ እየተቃወሙ ይገኛሉ፡፡ ይህን የህዝቡን ተቃውሞ ተከትሎም ፖሊስ በአባያ ነዋሪዎች ሰፈር እየመጣ እያስፈራራ እንደሚመለስ ነዋሪዎቹ ገልጸዋል፡፡
የካቲት 30/ 2007 እንደተለመደው ፖሊስ ነዋሪዎቹን ለማስፈራራት ወደ ሰፈር በሄደበት ወቅት ነዋሪዎቹ ፖሊሶቹን ‹‹ከሰፈራችን ውጡልን!›› እንዳሏቸው ተገልጾአል፡፡ ይሁንና ፖሊስ ከሰፈራቸው እንዲወጡለት የጠየቁትን አዛውንቶችን ጨምሮ ነዋሪዎች ላይ ድብደባ መፈጸሙ ተገልጾአል፡፡ ፖሊስ አዛውንቶቹ ላይ ድብደባ መፈጸሙን የተቃወሙ ወጣቶች ላይ ጥይት በመተኮስ ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ ወስዷል፡፡ በወቅቱም አንድ ሰው ሲሞት ከ8 ሰዎች በላይ ከፍተኛ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ተገልጾአል፡፡
እስካሁን ድረስ በንጹሃኑ ላይ የጭካኔ እርምጃ የወሰዱት ፖሊሶች ምንም አይነት ህጋዊ እርምጃ እንዳልተወሰደባቸውና በስራ ገበታቸው ላይ እንደሚገኙም የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡

የአማራዉ ሕዝብ ሁኔታ፣ ለኢትዮጵያዉያን ሁሉ

April 3, 2015
ለማስታወስ ያህል የዛሬ ሶስት ዓመት “ሞረሽ የአማራ አብሮነት ድርጅት” ብለን እኔ ራሴ፡ አምባሳደር አያሌው ማንደፍሮ፡ አቶ ይስሃቅ ክፍሌና ዶክተር ምስማኩ አስራት ሁነን ግቡ ለአማራዉ እርዳታ ለመስጠት የሆነ ማሃበር አዘጋጅተንና አስመዝገበን ነበር፤ የድርጅቱም አላማ ከማናቸዉም የፖሊቲካ ንቅናቄ ነጻ የሆነ የመረዳጃ ማህበር ብቻ እንዲሆን ነበር።
Amhara Ethnic group members Ethiopia
ይህንን እርምጃ ለመዉሰድ የገፋፋን ባለፉት ዓመታት በተለይ የወያኔ ቡድን የመንግሥት ስልጣን ከያዘ ወዲህ በተለይ በአማራዉ ሕዝብ ላይ የሚያካሂደው ወሰን የለሽ ጭቆናና ግፍ፤ ሕዝቡን ለማጥፋት የምያደርገው ሙከራ በጣም አሳስቦንና አስጭንቆን ነው። በዚህም አንጻር በየቀኑ የሚወርድብት በደል አንሶ የአማራዉ ሕዝብ ቁጥር እስከ ስድስት ሚልዮን ተቀንሷል ይባላል። ይሄም የሕዝቡ ቁጥር ከሃገሪቷ ጠቅላላ እድገት ጋር እየተመዛዘነ እንዲካሄድ፤ እርጉዝናን ለመቆጣጠር በሚሰጠዉ ክትባትና ልዩ ልዩ መድሃኒት ስበብ፤ ሴቶችን ጭርሶ የሚያመክኑትን እንዲሰጥ ተብሎ በተቀናጀ ሴራ መደረጉ የማያጠራጥር ሆኗል።
ከሁሉ አስቀድሞ ይህ ሁሉ ኢሰባዊ በደልና ጥቃት የሚጣልበት የአማራ ወይንም የሃበሻ ሕዝብ ማን ነው፧ በራረጅም የታሪክ ጉዞ ከብዙ ነገዶችና ጎሳዎች ተጋብቷል፤ ተዋልዷል፤ ተዛምዷል፤ በዚህ ታሪካዊ ሂደት አብረን ተጉዘናል፤ ብዙ ችግር በጋራ አሳልፈናል፤ አበርን ደምተን አብረን ሞተን ኢትዮጵያ አገራችንን ነጻነቷንና ክብሯን ጥበቀን አቆይተናል፤ በኢትዮጵያዊነታችን ጸንተን እስካዛሬ ተጉዘናል።
ስለዚህ በቋናቋና በባህል አማራ ነን ስንል፤ በዘር ደግሞ ከልዩ ልዩ ነገድ ስለምንዋለድ የኢትዮጵያ ፍሬዎች ነን እንላልን፤ አማራ ወይም ሃበሻ የሚባለው በአንድ ጎሳ ወይም ባንድ አካባቢ አይተመንም፤ አይከለልም፤ በረጅም ክፍለ ዘመናት ታሪክ የተጥነሰሰ፤ የራሱን ቋንቋ፤ ፊደላትና ድርሰት፤ ፍልስፍናና ጥበባት ያመነጨ፤ የመንግሥት ሕግና ስርዓት የደነገገ፤ ይታላቅ ሃይማኖቶች ባለአደራ የሆነ፤ ከፍተኛ ስልጣኔ ለዓለም ያበረከተ ሕዝብ ነው።
የአማራው ብዛት ከግማሽ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያላነሰ ሲሆን፤ በጉልበትም፤ በችሎታም፤ በእዉቀትም የጎደለው ነገር ሳይኖር፤ ራሱን አዋርዶኖ አጎልብሶ የማንም መሳለቅያ ሁኗል፤ ይደበደባል፤ ይታሰራል፤ ይገደላል፤ ከተወልደበት ቦት እየተፈናቀለ በገዛ አገሩ ስደተኛ ሁኗል፤ የወያኔዎችና የአንድ አንድ ግለሰቦችና ፖሊቲከኞች የልፈፋና የግል አላማ የሚሰበክበት መሳርያ ሁኗል። ስለ አማራው መጎሳቆልና መወገር ብዙ ይወራል ይተቻል ነገር ግን እስካሁን ድረስ ካለበት ችግር ሊያድነው የሚችል አንድም አካል አልተገኘም። እንደዚህ ያለ ተግባር ለማድረግ በተመኮረ ጊዜ ከራሱ ከአማራው መሃል አፍራሽና ተቃራኒ ድርጊት ይፈጠራል፡ በዛሬ ወቅት የወያኔ ቡድን አገርን ቀጥቅጦ የሚገዛው ብቻዉን ሁኖ ወይም የአብዛኛውን ሕዝብ ድግፍ አግኝቶ አይደለም፤ ከአማራዉ ከኦሮሞው ከሌሎች ወገኖች ተባባሪና አብሮ አገብጋቢ ድጋፍ እያገኘ ነው።
በተለይ ባለፉት ስልሳ ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ በችግርና በድህነት እየታረዘ መድህን ይሆኑልኛል ብሎ ደሙን ተፍቶ ያፈራቸው ምሁራን ዛሬ በሚልዮን ይቆጠራሉ፤ በተቀረው የዓልም ክፍል ጊዝያዊና ዘመናዊ ዘዴ እያመነጨ የሕዝቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል አዉራ ሁኖ የሚመራዉ የተማረዉና ያወቀው መደብ ሲሆን፣ በሃገራችን ያለው ምሁር ይህንን ተግባር ለማሟላት አልቻለም። ነጻነትን ለመጎናጸፍ በሚደረግ ተጋድሎ ህብረሰቡ በሙሉ መሳተፍ አለበት፤ ሃብታሙም ደሃዉም በእኩያ የሚካፈሉት ግዴታ ነው፤ ይሄም የፖሊቲካ ወይም የሌላ ወገናዊነትን የሚነካ አይደለም፤ የዚህ ወይም የዝያ ድርጅት አባል ነኝ የሚያሰኝ አይደለም፤ ዛሬ በአማራው ላይ ነገ በኔ ብሎ የሚያሳስብ ነዉ፤ ወንድ ሴት ልጅ ሽማግሌ ሳይለይ የሁሉም የጋራ ትግል ነዉ።
በኢትዮጵያ ሕዝብ ዉስጥ የአማራዉ ህዝብ ቁጥር ከአንድ ሲሶ ይበልጣል እንጂ አያንስም፤ ይሔንን ያህል የሰው ጉልበት አቅፎ፤ በርካታ አዋቂዎችና ባለሃብቶች እያሉት፤ እንደዚህ ያለ ዉርደትና መስቃየት እስከ ጥፋት የሚያመራ ዘመቻ ሲካሄድበት አንገቱን ደፍቶ ሲቀበል ማየት ያሳፍራል፤ይጎመዝዛል፤ አለኝታን ያሳጣል። ያለመስዋእትነት የሚገኝ ነጻነትና ክብር የለም፤ ሁሌም አባቶቻችን እንዳደረጉት ተጋፍጦ መታገል አለ፤ ከንቱ ዛቻና ወሬ ድል አያስገኝም።
በተለይ ወጣቱ ትውልድ፤ የነገ ሰዉ የሆነው፤ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለው፤ የተያዘውን የጎሳ አወቃቀርና ዘመን አመጣሽ የባዕድ ባህልና ፖሊቲካ አሽቀጥሮ ጥሎ አዲሷን ኢትዮጵያ በታሪካዊ ቅርሷ ላይ መገንባት አለበት።
ከማክበር ሰላምታ ጋር፤
ኢምሩ ዘለቀ።

Thursday, April 2, 2015

ስልጣን ላይ አድሮ ለመገኘት ሃገርን መሽጥ፤ ህዝብን መሸፈጥ ለምን? እስከመቼ?

April 2, 2015
እስከ ነጻነት
የህወሃቱ መሪ መለስ ዜናዊ ሰሜን አፍሪቃ የተነሳሳው ህዝባዊ አመጽ በኢትዮጵያኖች ዘንድ መወያያ ርዕስ እንዳይሆንና አመጹም እንዳይዛመት “ዛሬን ስልጣን ላይ አድሮ መገኘት፤ ቀኑን እንዳመጣጡ ለማለፍ ስልት መቀየስ” በሚል እምነቱና ስልጣንን ከህዝብም ከሃገርም በላይ አምላኪነቱ የተነሳ: ለነገ ምን ችግር ያመጣል? ጉዳቱስ መጠኑና ስፋቱ ምን ያህል ይሆናል? ሃገር ሉዓላዊነትና ዘላቂ ብሄራዊ ጥቅም ላይ የሚኖረው አዎነታም ሆነ አሉታ ተጽዕኖ ሳያሳስበው: ብልጭ ባለለት ማምለጫ መንገድ ብቻ የሚንቀሳቀሰው መለስ “አባይን እገድባለሁ” የሚል ቅዥት ይዞ ብቅ እንዳለ ሁላችንም እናስታውሳለን። ይህን ያልታሰበበት፤ ያልተጠና፤ ህዝብ ያላወቀውና መክሮ ያልተስማማበትን ቅዥት በየሙያው ዘርፉ አንቱ የተባሉና የሃገራቸው ጉዳይ የሚያሳስባቸው ተናገረውበታል፤ ጽፈውበታል አስጠንቅቀዋል፡ ህወሃት ግን የዕለት ስልጣንና ከስልጣን የሚገኝ ጥቅም እንጂ የህዝብ ስሜትና ፍላጎት ስለማያስጨንቀው ሊሰማ አልቻለም፡ በምጣኔ ዘርፍ፤ በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ፤ በህግ ዘርፍ፤ በርካታ ባለሙያዎች አስተያየታቸውን ስለሰጡበት እኔ እሱ ላይ አልመለስም።
እኔ ማንሳት የምፈልገው: ከሙያው ቅርበት ካላቸው በስተቀር የኢትዮጵያ ህዝብ አያውቀውም ብዬ የምገምተውን: ማወቅ አለበት፤ አውቆም ለጥፋቱና ለሃገራዊ ሉዓላዊነት መደፈር ከህወሃት እኩል ተጠያቂ መሆኑን ሊያስገነዝብ ይችላል የምለውን አባይ ወንዝ ዙሪያ የተደረጉ ጥናቶችን፤ የቀረቡ ሃሳቦችንና እቅዶችን; ህወሃት የሄደበትን የተቃርኖ መንገድ በተመለከተ ይሆናል።
1.1 በአባይ ወንዝ ዙሪያ የተደረጉ አብይ ጥናቶች
በአባይ ዙሪያ የተደረገው የመጀመሪያ ጥናት በአሜሪካ ጂኦሎጂ ቅየሳ (United States Geological Surfay(USGS)) እ አ አ በ1960ዎቹ የነበረ ሲሆን በዚያን ጊዜ የተመረጡት አራት የግድብ ቦታውች ነበሩ፤ እነዚህም ከጎሃጽዮን-ደጀን አባይ ድልድይ ወደ ሱዳን አቅጣጫ ተከትለን ሲንሄድ በቀደም ተከተል (ካራዶቢ፤ ማቢል፤ መንዳያ እና የግርጌ (Karadobi, Mabil, Mandaia and Border) ናቸው።
ከታች ያለውን ንድፍ ይመልከቱ፡
Proposed dams on Blue Nile
ሁለተኛው ጥናት የተደረገው በ1980ቹ ሲሆን ቼዘን (CESEN) የተባለ የጣያን አማካሪ መሃንዲስ ቡድን ሲሆን የሃገሪቱን ጠቅላላ የሃይል ፍላጎትና አቅርቦት አጥንቶ ነበር፤ ይህም ጥናት እነዚህን አራት የአባይ ግድቦች በጥናቱ አካቶ ነበር።
ሶስተኛው ጥናት ደግሞ በ1990ዎቹ መጨረሻ ላይ የተጠናው የአባይ ተፋሰስ የተቀናጀ የማስተር ፕላን ዝግጅት ነው።
(በነገራችን ላይ ይህን የፕሮጀክት ጥናት ለመስራት በመጀመሪያ አሸናፊ የነበረው የሻውል ኮንሰልት ከውጭ ካሉ ድርጅቶች ጋር ነበር፤ ሻውል ኮንሰልት የኢንጅነር ሃይሉ ድርጅት ነው። ጨረታውን አሸንፈው ለፊርማ መለስ ዜናዊ ጋ ሲቀርብ ጠላቶቻችንን ራሳችን ነን ፋይናንስ የምናደርጋቸው ብሎ በመበሳጨቱና ውሉ እንዲሰረዝ ከመደረጉም በላይ በመንግሰት ወጪ በሚሸፈኑ ፕሮጀክቶች ላይ አገር ውስጥ ያሉአማካሪ መሃንዲስ ድርጅቶች (ኢትዮጵያውያንያቋቋሟቸው ድርጅቶች) በሙሉ ጫረታ ላይ እንዳይሳተፉ ታገዱ: ኢንጅነር ሃይሉ በወቅቱ የመ ኢ አ ድ ምክትል ፕሬዚዳንት ስለነበሩ ነው ጠላቶቻችንን ያለው መለስ ዜናዊ:: ኢንጅነር ሃይሉም በዚህ የተነሳ ከመ ኢ አ ድ ምክትል ፕሬዚዳንትነትም አባልነትም ለቀው፤ አገሪቷንም ለቀው ወጥተው።)
ከዚያም ሌላ ጫረታ ተካሂዶ (BCOEM, French Engineering Consultants) የሚባል የፈረንሳይ ኩባንያ ጨረታውን አሸንፎ ጥናቱን አከናውኗል። ይህም ጥናት አነዚህኑ አራት ግድቦች ያካተተ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ የልማት አማራጮችንም የካተተ ነበር።
1.2 የአባይ ተፋሰስና የደለል ችግር
አባይ ወንዝ በተለይ ከጎጃም፤ ከወሎና ከሸዋ የሚመጡ ገባሮች (እንደ በሽሎ፤ ጀማ፤ ሙገር ጉደር) የመሳሰሉት ከተራቆተው መሬት አፈሩን ጠርገው ስለሚመጡ ከፍተኛ ደለል ይሸከማሉ። አባይ በአማካኝ በአመት ከ140-150 ሚሊየን ቶን ደለል ተሸክሞ ካገርይወጣል፤ ይህም ደለል ለሱዳንና ግብጽ ከፍተኛ ራስ ምታት እየፈጠረባቸው ነው። ለደለል መጥረጊያ ብቻ በአመት በአማካይ $200,000,000 ሁለት መቶ ሚሊየን ዶላር ያወጣሉ።
1.3 ጥናቶቹ የደረሱበት ግኝትና የልማት እቅድ
አባይ እጅግ ከፍተኛ የሃይል ማመንጨት አቅም ያለው ተፋስስ መሆኑን ሁሉም ጥናቶች ይስማሙበታል፡ የአባይ ተፋሰስ ጥናት ላይ የተመሰረተ፤ ህዝብን ያሳተፈ፤ ባለሙያዎችን ያካተተ እቅድና ልማት ቢካሄድበት ኢትዮጵያን በሙሉ በሃይል አቅርቦትና ከአንዲ ሚሊየን በላይ የመስኖ ልማት በስርኣቱ ቢለማ ለሃገሪቱ የምግብ አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ድርሻ እንደሚኖረው ይታመናል: ግንባታው ግን በሚከተሉት ቀደም ተከተል መሆን እንዳለበት ሙያዊ ምክራቸውን አቅርበዋል::
በቅድሚያ አባይ ከፍተኛ ደለል ተሸካሚ ስለሆነ ይህ ደለል ደግሞ ለግድብ መሙላትና አካባቢ ብክለት ስለሚዳርግ መጀመሪያ በጣም ሊተኮርበት የሚገባው ተግባር ተፋሰሱን ማጎልበትና በጎርፍ የመሬት መሸርሸርን መቆጣጠር ነው። እነዚህም ተግባራት የእርከን ስራዎችን፤ የተራቆቱ መሬቶችን በደን መልሶ መሸፈንን፤ በጣም አስጊ የሆኑትን እንሰሳትና ምንጣሮ እንዳይካሄድባቸው መከለልን ያካትታል።
ግድቦቹ መሰራት ያለባቸው በምዕራፍ (phase) ሲሆን ግንባታውም ከላይ ወደታች መኬድ እንዳለበት (upstream to downstream) ነው፡ ለዚህም በቂ ምክንያት አለ፤ 1ኛ፤ የግድቡ ወጪ ቀለል ያለ ይሆናል፤ ሁለተኛ ከላይ ሲቆፈር የተቆፈረው አፈር ወደ ግድብ የመግባት እድል ስለሌለው ለግድብ መሙላት አሰተዋጽኦ አይኖረውም፤ 3ኛ፤ የኤሌክትሪክ ሃይል ካመረተ በሗላ መስኖ የማልማት እድል ይኖረዋል፡ በዚህ መሰረት ቅድሚያ የሚሰጠው የካራዶቢ (Karadobi) ግድብ ሲሆን በቀጣይ ማብል (Mabil) ማንደያ (Mandaia) በመጨረሻም የግርጌ (Border) ግድብ ናቸው፡ እንዚህ ግንባታዎች አቅም እየተገነባ ቀስ በቀስ የሚገነቡ ሲሆን ተፋሰሱ ላይ ደግሞ ከፍተኛና ተከታታይ ስራ መሰራት እንዳለ ሆኖ ነው። ይህ አሰራር አንድን ውሃ በቅብብሎሽ አራት ቦታ ላይ ሃይል ማመንጨት ሰለሚያስችል ከፍተኛ የሃይል ማመንጨት አቅም ከማስገኘቱም በላይ ግንባታውም አቅምን ያገናዘበና የተጠና ይሆናል። በተጨማሪ አባይ ተፋስሰስ ውስጥ ከአንድ ሚሊየን ሄክታር በላይ የሚሆን ለመስኖ ተስማሚ የሆነ መሬት ስላለ፡ የነዚህ ግድቦች ግንባታ ይህን የመስኖ ልማት እንዲያካትት ሆኖ መሰራት እንዳለበት ጥናቶቹ ይመክራሉ።
1.4 የህወሃት የተቃርኖ ተግባር
ኢትዮጵያ ውስጥ የውሃ ሃብት ጥናትን፤ ዲዛይንን፤ ቁጥጥርን በተመለከተ በባለቤትነት የሚመራው የውሃ ሃብት ሚንሰቴር ነው፡ አባይን እንገድባለን የሚባለውን ቃል የሚንስቴር መስሪያ ቤቱ መሃንዲሶች የሰሙት ግን እንደማንኛውም ዜጋ አፍሪካ አዳራሽ ለስብሰባ ተጠርተው ከበረከት ስምዖን አፍ ነው። በወቅቱ ከድንጋጤ የተነሳ ምን መናገር፤ ምን ማለት እንዳለባቸው አንኳ ማስብ በማይችሉበት ደረጃ ተገርመው እንደነበር ይታወቃል።
የግድብ ስራው በጥናቱ እንደተመከረው ከላይ ወደታች እየተሰሩ መሄድ ሲገባቸው የመለስ ግድብ ግን የጀመረው ሱዳንና ኢትዮጵያ ድንበር አቅራቢያ ነው። እንደዚህ አይነት ከሜዳ የተነሳ ግንባታን ለስማቸው የሚጨነቁና በሙያቸው የሚኮሩ የግንባታ ተቋማት በምንም መልኩ ተሳታፊ አይሆኑም ለዚህም ለስሙ ብዙም ለማይጨነቀውና ቀድሞም የጎደፈ ስም ላለው ሳሊኒ (SALINI CONSTRUCTION S.P.A.) ያለምንም ጫረታ የተሰጠውም በዚሁ ምክንያት እንደሆነ መጠራጠር አይቻልም።
1.5 ይህ ግድብ ኢትዮጵያ ላይ የሚያስከትለው መዘዝ
ግድብ ከታች ተሰርቶ ከላይ ቁፋሮ ማድረግ ስለማይቻል ከላይ ያሉት ሶሰቱ ግድቦች ካሁን በሗላ ለግንባታ የሚታሰቡ አይሆኑም፤ እነሱ እስካልተገደቡ ድረስ ደግሞ አንድ ጥማድ ማሳ እንኳ በመስኖ ለማልማት አይቻልም፡ ስለዚህ ከሶሶቱ የሚገኘውን ሃይልና ከሚሊየን በላይ የሆነ የመስኖ ልማት ያሳጣናል ማለት ነው።
ከላይ እንደተጠቀሰው አባይ ከፍተኛ ደለል ተሸካሚ ስለሆነና በተፋሰሱ ላይ ምንም ተግባር ያልተከናወነ በመሆኑ የተሰራው ግድብ ሃይል ከማመንጨት ይልቅ የደለል ማከማቻ ይሆናል ማለት ነው: ከዚህ የተነሳ ግብጽና ሱዳን ከደለል ነጻ የሆነ ውሃ ስለሚያገኙ በያመቱ ለደለል ጠረጋ ያጠፉ የነበረው $200 ሚሊየን ዶለላር በቀላሉ ያተርፋሉ።
በሌላ በኩል ደግሞ ኢትዮጵያ ለመስኖ ውሃ አንድ ባሊ ውሃ እንኳን መጠቀም የማትችልበት ሁኔታ ስለሆነ የአባይን ውሃ ሙሉ ለሙሉ ይቆጣጠሩታል፡ እኛ ኢትዮጵያውን አባይ ወንዝ ላይ ያለን የባለቤትነት መብት እናጣለን የሃገሪቷም ሉዓላዊነት ጥያቄ ውስጥ ይገባል ማለት ነው: ግድቡ ሲጀመር ግብጽም ሆኑ ሱዳን ለይስሙላና ተቃውመዋል ተብሎ ኢትዮጵያውያንን ለማታለል ብቻ እንጂ ጫን ያለ ተቃውሞ ያላሳዩትም ይህንን ጥቅማቸውን ጠንቅቀው ያውቁ ስለነበረ ነው።
እዚህ ላይ ሳይጠቀስ መታለፍ የለለበት መለስ ዜናዊ ገና ስልጣን እንደያዘ ወንበሩ ላይ እንኳ ገና ተስተካክሎ ሳይቀመጥ፤ በሽግግር ላይ እያለ ነበር ካይሮ ድረስ ሄዶ ከግብጽ ጋር መፈራረሙን ነው። ያ ውል የተዘጋጀው በሁለት ቋንቋ ሲሆን በአረብኛና በእንግሊዛኛ ነበር፡ አረብኛ የግብጽ ብሄራዊ ቋንቋ ሲሆን እንግሊዘኛ ምን እንደሆነ መለስና ህወሃቶች ናቸው።
ስምምነቱም ለግብጽ ታዛዥነትን ያመለከተ ከመሆኑ ባሻገር ለ ኢትዮጵያ ታላቅ ኪሳራ ያስከተለ ነበር፤ ያንን ፊርማ ተከትሎ ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ በወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ላይ የነበራትን ፍጹም የግዛት ሉዓላዊነት አቋም ለውጦ ምንነቱ እንኳ በውል መተርጎም ያልተቻለበትን (equitable utilization and non appreciable harm) ነው የምንከተለው ተባለ። ግብጽ ግንጥንት ጀምሮ ስትከተል የነበረውን ኣቋም ቅንጣት አልቀየረችም: አሁንም አልቀየረችም።
የህወሃት ባለስልጣናት ግድቡ የታቀደው የሰሜን አፍሪቃን ህዝባዊ አመጽ ትኩረት እንዳይስብ የኢትዮጵያን ህዝብ ትኩረት አቅጣጫ ለማስቀየር እንጂ ታስቦበትና ታቅዶ የተጀመረ አለመሆኑን ቢያውቁም ከህዝብ የሚሰበሰበው ገንዘብ ደግሞ የኤፈርትንና የህወሃት ባለስልጣናትን ኪስ እያደለበ በመሆኑ ሊያስቆሙት አልፈለጉም: የሚያመጣውም ጣጣ አልታያቸውም እንዳውም ይባስ ብለው ሌላ ውል እየተዋዋልን ነው አሉን።
1.6 ግድቡ ለግብጽና ለሱዳን ጠቃሚ ከሆነ ያሁኑ ስምምነት ፊርማ ለምን መጣ?
ከላይ ከላይ የሚታየው ስምምነቱን በፓርላሜንት አስጸድቀው ህጋዊ እውቅና ያገኘ ሰነድ በእጃቸው ለመጨበጥና ወደፊት ለሚነስ የይገባኛል ጥያቄዎች ማስረጃ ለመያዝ መስሎ ሊታይ ይችላል፡ ህጋዊ ሆነም አልሆነ አሁን ያለው ግድብ በዚሁ ካለቀ ሁሌም አገልግሎቱ ለግርጌ ተፋስስ ሃገሮች ሲሆን ኢትዮጵያ ግን ባዶ እጇን አጨብጭባ ዜጎችም በጉልበት ገንዘባቸው ከመበዝበዝ ያለፈ ጠብ የሚል ነገር አለመኖሩን በርግጠኝነት መናገር እችላለሁ።
ይህ ከላይ የተጠቀሰው ውጫዊና ማስመሰያ ሲሆን ዋናው አላማ ግን፡ ግድቡ እንደተባለው ለተቃውሞ ማስተንፈሻ፤ አቅጣጫ ማስቀየሪያ እንጂ ለእውነተኛ ልማት የታቀደ ባለመሆኑ መካተት ያለባቸው ጥናቶች አልተካተቱም፤ የአባይ የውሃ መቋጠሪያ ውሃው የሚጠራቀምበት፤ ሃይቅ የሚፈጥርበት ሸለቆ (Reservoir area) እሳተገሞራ ወለድ አለት በመሆኑ (volcanic rock) ስለሆነ ስንጥቅጥቅና ስብርባሪ (fractures and fissures) ይበዛበታል፡ ውሃ በነዚህ ስንጥቆች ውስጥ በቀላሉ ሊሰርግ ይችላል፡ ውሃ ሰርጎ ከገባ ደግሞ አለቱን የመፈንቀል፤ አፈሩን የመሸርሸር ከፍተኛ አቅም (uplift/pore pressure and piping) ስላለው ግድቡን እስከማፍረስ ሊደርስ ይችላል፤ ግብጽና ሱዳን ይህንን ጠንቅቀው ያውቁታል፡ ግድቡ ሲፈርስ ሊደርስባቸው የሚችለውን አደጋ ያሰሉታል: ስለሆነም ዋሰትና ይፈልጋሉ፤ እነሱ ከአባይ ጥቅሙን እንጂ ጉዳቱን መጋራት አይፈልጉም። አጋጣሚ ሆኖ ግድቡ ቢፈርስና ጉዳት ቢደርስባቸው ካሳ ይፈልጋሉ ለዚህም ነው የካሳን ነገር ስምምነቱ ውስጥ የሸነቀሩት። ህወሃት ደግሞ ዛሬን ስልጣን ላይ አድሮ መገኘቱን እንጀ ነገ የሚመጣውን ማሰብም ሆነ ማቀድ አይፈልግም፤ አቅሙም ፍላጎቱም የለውም። የተፈራው ደርሶ ግድቡ ቢናድና ሱዳንና ግበጽ ላይ አደጋ ቢደርስ ኢትዮጵያ የምትከፍለው ካሳ ምን ያህል ነው? ካሳውስ ከየት ነው የሚሰበሰበው? ያው ከህዝብ አደል?
1.7 አሁን ከህዝብ ምን ይጠበቃል?
ይህ ቀላል ጉዳይ አደለም፤ ለእለት ስልጣን ተብሎ የትውልድ ዘላቂ የተፈጥሮ ሃብትና የሃገር ሉዓላዊነትን አሳልፎ መስጠት ቀልድ አይደለም፤ እንኳን ሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ቀርቶ የህወሃት አባላትና ባለስልጣናት በእጅጉ ሊያስቡበት የሚገባ ጉዳይ ነው። ሃገሪቷን ምን አይነት ውስብስብ ችግር ውስጥ ሊከቷት እንደሆነ ሊገነዘቡ ይገባል።
ከዚሁ ጋር ለግድቡ ግንባታ እርዳታ አደረግን፤ ቦንድ ገዛን የምትሉ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ልማትን እየደገፋችሁ ሳይሆን የሃገርን ሉዓላዊነት አደጋ ላይ እየጣላችሁ፤ ለትውልድ መተላለፍ ያለበትን የተፈጥሮ ሃብት ለባዕድ ሃገር አሳልፋችሁ እየሰጣችሁ መሆኑን ልትገነዘቡ ይገባል፤ ሃገሪቷ ለሚደርስባት ማንኛውም ውድቀት ተሳታፊ መሆናችሁን መገንዘብ አለባችሁ።
ለዘለቄታው የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፎ ላለመስጠትና ሉዓላዊነቷን አደጋ ላይ ላለመጣል ግድቡ ለወፊት ሊቀጥል በሚቻልበት ደረጃ ተዘጋጅቶ መቆም አለበት (The construction of the dam should be halted right away with a condition to resume when the time is right.) ግንባታው አሁን ባለበት ቆሞ፤ ህዝብንና ባለሙያዎችን ያሳተፈ ጥናትና እቅድ ተይዞለት ለሃይል ማመንጫ ብቻ ሳይሆን የውሃ ሃብቱንም ለመስኖ መጠቀም በሚቻልበት መንገድ መሰራተ አለበት። ግንባታው ከጠረፍ ሳይሆን ከካራዶቢ (KIaradobi) መጀመር አለበት። ይህን ስል ለግድቡ እስካሁን የወጣውን ወጭ ግምት ውስጥ ማስገባት ተስኖኝ አደለም ግን ሃገርንና የተፈጥሮ ሃብትን ጨርሶ ከማጣትና ተተኪ ትውልድን ድህነትና ውርደትን ከማስረከብ እዚሁ ላይ ቢቆም ይበጃል ከሚል ግንዛቤ ነው።
እኔ የታየኝን፤ ያማውቀውን፤ የማምንበትን፤ የሚያስጨንቀኝን እንደ አንድ ዜጋ መልዕክቴን አስተላልፌያለሁ። እያንዳንዱ የዜግነት ድርሻውን ይወጣ፤ በተለይ ለዚህ ግድብ ግንባታ ቦንድ የምትገዙ፤ እርዳታ የምትሰጡ፤ አባይ አባይ እያላችሁ የምትጮሁ አርቲስቶች ሃቁን ተረድታችሁ የህሊናችሁን እንድታደርጉ ጥሪዬን አቀርባለሁ።
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይጠብቅ
እስከ ነጻነት

ከኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ ለኢትዮጵያ ወጣቶች የተላለፈ ማሳሰቢያ!!!

March 2,2015
ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሚገነዘበው በጥቂት ጠባብ አምባገነኖች የሚመራው የህወሓት/ኢ ህአዴግ ሥርዓት ላለፉት 23 አመታት በህዝብ መካከል የጥላቻና የጥርጣሬ መርዙን እየረጨ፤ ለዘመናት ተፋቅሮና ተከባብሮ የኖረውን ጠንካራ ህዝብ በተለያዩ ጐራዎች በመከፋፈል፤ እምቅ ጉልበቱን በማዳከም፤ ብሎም ትውልድ የማምከን ሰይጣናዊ አላማውን ለማሳካት ነጥሎ በማጥቃት፤ በሃገርና በህዝብ ላይ እጅግ ዘግናኝ ጭካኔዎችንና በደሎችን አየፈፀመና፣ ለከፍተኛ ስቃይና መከራ እየዳረገ እንደሚገኝ ይታወቃል። ይህ አርቆ ማየት የተሳነው ሥርዓት በተለይ ወጣቱ ትውልድ በራስ የመተማመንና አርቆ የማሰብ እምቅ ችሎታው እንዲዳከምና ባክኖ እንዲቀር፤ ብሄራዊ ስሜቱ ጨርሶ እንዲጠፋና ከግለኝነትና ከጐጠኝነት የማያልፍ ጠባብ አስተሳሰብ ውስጥ ሰጥሞ እንዲቀር፤ ብሎም ትውልድን የማምከንና ሃገር የማጥፋት እኩይ አላማውን ለማሳካት፤ በትምህርት ካሪኩለሙ ላይ ሳይቀር መርዙን ለመርጨት ሌት ከቀን እየኳተነ ይገኛል። በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማህበራዊ ሚዲያዎች አማካኝነት በጥቂት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል እያየን የምንገኘው አላስፈላጊና ዋጋቢስ ንትርክ፤ የሥርአቱ ትውልድን የማምከን እኩይ አላማ መገለጫ ተብሎ የሚገለፅ ቢመስልም፤ እውነታው ግን ሥርአቱ አላማውን ለማሳካት ቀጥሮም ሆነ አሳስቶ፤ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ፤ የተፅዕኖው ሰለባ በማድረግ እየተጠቀመባቸው ባሉ ጥቂት ወጣቶች አማካኝነት የሚካሄዱ መሰሪ ተግባራት ናቸው። ይሁንና ዛሬ ይህ ትዕይንት መረን እየለቀቀ የመጣበት ደረጃ ላይ ይገኛል።
EYNM New Logo
ሃገራችን ኢትዮጵያ ከ85 ያላነሱ ብሄር ብሄረሰቦችና ጐሳዎች የሚኖሩባት፤ የ92 ሚሊዮን ህዝብ መኖሪያ ውብ ሀገር ነች። ኢትዮጵያ ከ3000 ዓመት በላይ ታሪክ ያላት ሀገር ስትሆን፤ በአለም ላይ ከታየና ከተመዘገበ ታሪክ ሁሉ፤ ልዩ በሆነ መልኩ የተለያዩ ጎሳ/ዘር፣ ኃይማኖት፣ እምነት፣ አመለካከት ያላቸው ዜጐች የሚኖሩባት ቢሆንም፤ ለዘመናት ተከባብረው፣ ተቻችለውና፣ ተዋደው፤ በፍቅርና በአንድነት በመኖር እንደምሳሌ የሚጠቀሱና የሚወደሱ ናቸው። ልዩነቶች ኖሮባቸው እንኳን ጠላት በመጣ ጊዜ በኢትዮጵያዊነታቸው አንድ ላይ በጽናት በመቆም፤ ጠላትን አሳፍሮ በመመከትና ድባቅ በመምታት፤ የሀገር ሉዓላዊነትን ጠብቀው፤ ህዝባቸውን ከጠላት ጥቃት ለመከላከል ደማቸውን አፍስሰው አጥንታቸውን አድቅቀው መስዕዋትነትን በመክፈል፤ የምንወዳትና የምንመካባት ኢትዮጵያን በክብር አስረክበውናል።
ይህን ማለት ግን ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋና ሰላማዊ ነበር ማለት አይደለም። እውነታው በተለያዩ ጊዜአት የመጡ ስርዓቶች በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ በደል በመፈፀም የታሪክ አሸራ ጥለው አልፈዋል። እዚህ ጋር ግልፅ ሊሆንልን የሚገባው፤የተፈፀመው በደል በወቅቱ የነበሩት ገዢዎች ተግባር እንጂ፤በሃገራችን ኢትዮጵያ ታሪክ አንድም ጐሳ በምንም ሁኔታ በሌላው ላይ ለማጥቃት ተነስቶ አያውቅም። ይህ ታሪካችን በሃገራችን ኢትዮጵያ ዜጐች በፍቅርና በአንድነት ለዘመናት ተቻችለው ሊቆዩ የቻሉበት ዋንኛ ሚስጢር ከመሆኑም በላይ፤ ልንሸሽገው የማይቻለን፤ለአንድነታችን አይነተኛ ማረጋገጫ የሆነ እውነት ነው።
በመሆኑም በወጣትነታችን የዚህ ትውልድ ፈርጥ መሆናችንን አውቀን፤ አእምሮአችንን አስፍተን ታሪካችንን በጥልቀት በመመርመርና በመረዳት፤ብሎም እውነታውን ለይተን በማገናዘብ፤ በታሪክ የነበሩ ችግሮቻችንን አሶግደን፤ የተሻሉ መፍትሄዎችን በሰከነ ውይይት በማፍለቅ፤ አባቶቻችን በክብርና በአንድነት ያስረከቡንን ታላቅ ሃገር በክብር ለመጪው ትውልድ የማስረከብ ታሪካዊ ግዴታችንን እንድንወጣ ሲል፤ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በአብሮት ጥሪውን እያቀረበ የወያኔ መሳሪያም እንዳይሆን ያሳስባል።
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ

Wednesday, April 1, 2015

የቴድሮስ አድሃኖም ዋና አማካሪ የሃሰት ፕሮፌሰር መሆናቸውን አበበ ገላው አጋለጠ

April 1,2015
አዲስ ቮይስ– የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤትና የሚኒስትሩ ዋና አማካሪ እንዲሁም የፖሊሲ ጥናትና ትንተና የበላይ ሃላፊ የሆኑት “ፕሮፌሰር” መኮንን ሃዲስ የሃሰት ፕሮፌሰር እደሆኑ አዲስ ቮይስ ባካሄደው እረዘም ያለ ምርመራ ማረጋገጥ ችሏል።። ግለሰቡ ለ15 አመታት በፕሮፌሰርነት አገልግየዋለሁ የሚሉት አንድ የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ እንደማያውቃቸው የገለጸ ሲሆን የዶክትሬት ዲግሪ ያገኙበት ተቋምም በአሜሪካ ህግ መወሰኛ ምክር ቤት “የዲፕሎማ ወፍጮ” (diploma mill) ተብሎ የተፈረጀ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።
Mekonnen Haddis
“ፕሮፌሰር” መኮንን ሃዲስ ከኦክቶበር 2010 ጀምሮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋና አማካሪ ሆነው በመንግስት የተሾሙ ሲሆን አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በነበሩ ወቅት ዋና አማካሪያቸው ሆነው ያገለገሉት እኚሁ ግለሰብ በአሁኑ ግዜ የዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ዋና አማካሪ እንዲሁም የፖሊሲ ጥናትና ትንተና ክፍል የበላይ ሃላፈ ሆነው በመስራት ላይ ይገኛሉ።
“ፕሮፌሰር” መኮንን ለረጅም አመታት በአሜሪካን አገር ሜሪላንድ ውስጥ የኖሩ ሲሆን በዚሁ ግዛት ውስጥ በሚገኘው ባዊ ስቴት ዩኒቨርሲቲ (Bowie State University) ለ15 አመታት ያህል በፕሮፌሰርነት ማገልገላቸውን በይፋ ሲናገሩ ቆይተዋል። ከዚህም በተጨማሪ በካሊፎርኒያ ፓስፊክ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ በሚል ስም ይንቀሳቀስ ከነበረ ተቋም የዶክትሬት ዲግሪ ማገኘታቸውን በተለያየ ግዚያት ሲገልጹ የነበረ ቢሆንም ዩኒቨሲቲው ዲግሪ ያለ ምንም ትምህርት እንደሚሸጥ በአሜሪካ ሴነት ትእዛዝ በተካሄደ ስምንት ወራት በፈጀ ምርመራ ከተረጋገጠበትና “የዲፕሎማ ወፍጮ” በሚል ስያሜ ከተፈረጀ በሁዋላ እአአ 2005 መዘጋቱን ለማወቅ ተችሏል። ምርመራው በተጨማሪም ኬኔዲ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ፣ ሃሚልተን ዩኒቨርሲቲ እና ካሊፎርንያ ኮስት ዩኒቨርሲቲዎች ዲግሪ ያለ ትምህርት የሚቸበችቡ ወፍጮ ቤቶች መሆናቸውን ይፋ አድርጎ እንደነበር እጃችን የገቡ መረጃዎች አረጋግጠዋል።
ይሄው በካሊፎኒያ ግዛት ይንቀሳቀስ የነበረውና የተዘጋው ዩኒቨርሲቲ የባችለር ዲግሪ በ $2295፣ የማስተርስ ዲግሪ $2395፣ እንዲሁም የዶክትሬት ዲግሪ 2595 ዶላር ይሸጥ እንደነበር ለህግ መወሰኛው ም/ቤት በልዩ ምርመራ ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር በነበሩት ሮበርት ክሬመር የቀረበው ሪፖርት አረጋግጧል።
ለአስራ አምስት አመታት በፕሮፈሰርነት አገለገልኩት የሚሉት ባዊ ስቴት ዩኒቨርሲቲ የግለሰቡን ፕሮፌሰርነትም ይሁን ቅጥር ጉዳይ እንደማያውቅ ለአዲስ ቮይስ ገልጿል። አዲስ ቮይስ በጉዳዩ ላይ መረጃ ከዩኒቨርሲቲው ለማግኝት በጠየቀው መሰረት የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ከፍተኛ ዳይሬክተር የሆኑት ሼይላ ሆብሰን በሰጡት ምላሽ ዩኒቨሲቲው በአሁኑ ወቅትም ይሁን ቀደም ባሉ አመታት መኮንን ሃዲስ የሚባል የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር እንደማያውቅ አስታውቀዋል።
አዲስ ቮይስ በጉዳዩ ላይ መረጃ ከዩኒቨርሲቲው ለማግኝት በጽሁፍና በስልክ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ከፍተኛ ዳይሬክተር የሆኑት ሼይላ ሆብሰን በሰጡት ምላሽ ዩኒቨሲቲው አሁንም ይሁን ባለፉ አመታት በፕሮፌሰርነት ይሁን በሌላ ደረጃ መቀጠራቸውን የሚያሳይ ምንም መረጃ መግኘት አለመቻሉን በኢሜይል በላኩት ምላሽ አሳውቀዋል። ዳይረክተሯ የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ክፍል ከኮምፒውተር ሰነዶች በተጨማሪ በወረቀት የያዛቸውን የመረጃ ክምችቶች ፈትሸው መኮንን ሃዲስ የሚባል ሰው የፕሮፌሰርነት ሹመትም ይሁን የቅጥር ማስረጃ ማግኘት አለመቻላቸውን አስረድተዋል።
አዲስ ቮይስ ባቀረበረበው ተጨማሪ የስልክ ጥያቄ መሰረት ፕሮፌሰሩ የተለያዩ ኮርሶችን አስተምርበት ነበር ያሉትን የታሪክና የስነ መንግስት የትምህርት ክፍል ሊቀመንበር የሆኑትን ፕሮፌሰር ሳሚ ሚለርን ዳይሬክተሯ ጠይቀው የተሩዱት መኮንን ሃዲስ አንድ ወይንም ሁለት ሴሜስተር ለሚሆን ግዜ ከረጅም አመታት በፊት በረዳትነት ማስተማራቸውን ብቻ እንደሚያውቁ አረጋግጠውላቸዋል። ዳይሬክተሯ ዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተለያዩ ግዚያት ለአጭር ግዚያት በረዳትነት የሚያስተምር ማንኛውንም ግለሰብ እንደ ዩኒቨርሲቲው ተቀጣሪ እንደማይቆጥር ገልጸዋል። በትምህርት ክፍሉ እንደ ፕሮፌሰር ሚለር ከሰላሳ አመታት በላይ ያገለገሉት ፕሮፌሰር ዊሊያም ሌውስ በበኩላቸው መኮንን በዩኒቨርሲቲው የማስተርስ ዲግሪ ተማሪ እንደነበር አስታውሰው ትምህርቱን ካጠናቀቀ በሁዋላ ለጥቂት ግዚያት ብቻ የተወሰኑ ኮርሶችን በረዳትነት ማስተማሩን አስታውሳለሁ በማለት የመኮንን ሃዲስን ለአስራ አምስት አመታት የዘለቀ የፕሮፌሰርነት አገልግሎት ትክክል አለመሆኑን አረጋግጠዋል።
ፕሮፈሰሩ ለጉዳዩ ምላሽ እንዲሰጡ ያደረግነው ሙከራ ሳይሳካ የቀረ ሲሆን በስራ ላይ መጠመዳቸውን ካስረዱ በሁዋላ “Leave me alone!” በማለት ስልኩን ዘግተዋል። ወደ ኢትዮጵያ በኤክስፐርት ደረጃ ግብረገብ፣ ዴሞክራሲ፣ የግጭት ማስወደድና ተዛማጅ ጉዳዮችን በተመለከተ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና፣ መንግስታዊ ድርጅቶች እየተዘዋወሩ እውቀት ለማካፈል በ2007 ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት መኮንንን ሃዲስ አለም አቀፍ የገጣሚያን ማህበር በአለፉት መቶ አመታት ውስጥ በአለማችን ከተገኘኑ ምርጥ አንድ መቶ ገጣሚዎች አንዱ ነህ ብሎ አክብሮኛል በማለት በይፋ ተናግረው እንደነበር በጋዜጦች ተዘግቦ ነበር። በ ኦክቶበር 2007 የወጣው “ዴይሊ ሞኒተር” ጋዜጣ ፕሮፌሰሩ በበርካታ መቶዎች በሚቆጠሩ ግጥሞቻቸው እንደሚታወቁ መናገራቸውን ከመጥቀስ አልፎ በአለፉት መቶ አመታት ውስጥ ከተከሰቱ ”100 ምርጥ የአለማችን ገጣሚያን አንዱ” በማለት የአለም አቀፍ የገጣሚያን ማህበር የሚባል ድርጅት እንደሰየማቸው ዘግቧል።
ይሁንና ጉዳዩን ለማጣራት ባደረግነው ጥረት በአሁኑ ግዜ የተዘጋው ይህ ድርጅት ሃሰተኛ የሆኑ የግጥም ውድድሮችን በማኪያሄድ አብዛኛውን ተወዳዳሪ በማጭበርበር በርካታ አቤቱታ ቀርቦበት የነበረ ሲሆነ ድርጅቱም ሌላ የንግድ ተቋም መሸጡ ታውቋል።
—-
ጥቆማና ጠቃሚ መረጃ ለመላክ ይህን ኢሜይል ይጠቀሙ editor@addisvoice.com

ተያያዥ መረጃዎች
Related links
Professor Mekonnen Haddis: Chief Advisor of the Ministry (MoFA biography)
http://www.mfa.gov.et/abtMnstrMore.php?pg=20
Biography: Screenshot
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/bio.png
Ethiopia: Media Behavior During Election 2005 ‘Shameful’ U.S. Scholar (Copy)
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/All-africa-monitor.pdf
Report on Degree Mills, U.S. Senate, Robert J. Cramer, Director Office of Special Investigations
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/Pacific-Western-Univesity.pdf
The Contester: Poetry.com Struggles for Legitimacy
http://www.pw.org/content/contester_poetrycom_struggles_legitimacy
Political Snapshots (Mekonnen Haddis’ blog)
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/Mekonnen-Haddis-Blog-screenshot.pdf