Sunday, March 2, 2014

ጥፋተኛ ጥፋቱን በይቅርታ እንጂ በዉሸትና በዕብሪት መሸፈን አይችልም

March 2/2014
በቅርቡ አንድም የወያኔ ጌቶቹን ለማስደሰት ደግሞም ከህወሃት ካድሬዎች ስድብና ግልምጫ የማያድን ጎደሎ ስልጣን ለማግኘት ሲል ተወልዶ ያደገበትንና እመራዋለሁ የሚለዉን የአማራን ህዝብ ክብርና ታሪክ ያጎደፈዉና ያዋረደዉ የአለምነዉ መኮንን አስጸያፊ ንግግር በአለም ዙሪያ የሚገኙ ኢትዮጵያዉያንን ያስቆጣና ያነሳሳ ጉዳይ ሆኖ መሰንበቱ ይታወሳል። ይህ የአማራን ህዝብ ማንነትና ይህ ጀግና ህዝብ በኢትዮጵያ ታሪክ ዉስጥ ያለዉን አኩሪ ቦታ ያላገናዘበና ባልተሞረደ አንደበት የተነገረ አስጸያፊ ንግግር ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተዉን የአማራን ህዝብ ብቻ ሳይሆን አገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የሚኖሩትን በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን አስቆጥቷል። አይናቸዉ ከገንዘብና ከሥልጣን ዉጭ ሌላ ምንም ነገር የማይመለከት ለሆዳቸዉ ብቻ ያደሩ ሰዎች የተከፈተ ሆዳቸዉንና ማለቂያ የሌለዉ የሥልጣን ጥማታቸዉን ለማርካት ሲሉ ምንም ነገር ከማድረግ ወደ ኋላ እንደማይሉ ወያኔ በሥልጣን ላይ የቆየባቸዉ ያለፉት ሃያ ሦስት አመታት በግልጽ አሳይተዉናል። ሆኖም ግን አይናቸዉ የታወረና ጭንቅላታቸዉ ባዶ የሆነ ሰዎች በነገሱበት በወያኔ ስርዐት ዉስጥም ቢሆን የሚጠሉትን፤ የሚንቁትንና የገዛ ወገኖቹን የገቡበት ቦታ ሁሉ እየተከተሉ ወደ አገራችሁ ግቡ እያሉ የሚያፈናቅሉ ዘረኞችን ለማስደስት ሲል ስቃይ የበዛበትን የራሱን ህዝብ ያዋረደ ከሀዲና ሂሊና ቢስ ሰዉ ያየነዉ አንድ አለምነዉ መኮንንን ብቻ ነዉ። አለምነዉ የተናገራቸዉን አጥንት የሚሰብሩ የንቀት ቃላት ይሀንን ከንቱ ሰዉ ባወገዝን ቁጥር እየደጋገምን ብንጠቅስ በአንድ በኩል የወያኔን ዘረኞች አላማ ያራምዳል ብለን ስለምናምን በሌላ በኩል ደግሞ እንደዚህ አይነቱን ጸያፍ ንግግር መደጋገም ሂሊናችን ስለማይፈቅድንና የጠፈፈ ቁስል መቆስቆስ ይሆናል ብለን ስለምንሰጋም ንግግሩን አንደግመዉም።
አሜሪካንን በመሳሰሉና በዕድገት ወደፊት በገፉ አገሮች ዉስጥ ዉሻ የሚታወቀዉ የሰዉ ልጅ ታማኝ ወዳጅ በመባል ነዉ። ዉሻ ባለቤቱን ለማስደስት ጭራዉን ከመቁላት ባሻገር የባለቤቱን እግር ይልሳል፤ ይንበረከካል፤ እግር ስር ይተኛል፤ ደግሞም አምጣ ብለዉ የወረወሩለትን ነገር እየሮጠ ሄዶ ያመጣል። የሚገርመዉ እንስሳዉ ዉሻ እንኳን እነዚህን ነገሮች ሁሉ የሚያደርገዉ ለባለቤቱና ለለመደዉ ወዳጁ እንጂ ለሌላ ለማንም ሰዉ አያደርግም። ዉሻ ባለቤቱንና ወዳጁን በተለይ ደግሞ የሱንና የባለቤቱን ጠላቶች ለይቶ ያዉቃል፤ ስለዚህም ዉሻን ባለቤትህን ንከስ ብለን ያንን የሚወደዉን ስጋ ያሻንን ያክል ብናሸክመዉ እኛዉ ላይ መልሶ ይጮህብን እንደሆነ ነዉ እንጁ ዉሻ ባለቤቱን በፍጹም አይነክሰም።
ዛሬ ኢትዮጵያ ዉስጥ እነ አለምነዉን የመሳሰሉ ለወያኔ ያደሩ ሂሊና ቢሶች፤ ሹምባሾች፤ ምስለኔዎችና ሆዳሞች አንድ የጎደላቸዉ ትልቅ ነገር ቢኖር የዉሻን ያክል ታማኝ መሆን ነዉ። እነ አለምነዉ እናስተዳድረዋልን ለሚሉት ህዝብ ታማኝነት ቢኖራቸዉ ኖሮ ዛሬ እነሱ እራሳቸዉ፤ የሚመሩት የአማራ ህዝብም ሆነ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ከአገሩ ተስድዶ እንደ አዙሪት በየአገሩ ከሚዞር በገዛ አገሩ ተከብሮ በወግና በማዕረግ ይኖር ነበር።ችግሩ “ባለቤቱ ያቀለለዉን አሞሌ ባለዕዳ አይቀበለዉም” ነዉና የኢትዮጵያ ህዝብ በእነ አለምነዉና መሰሎቹ የተነሳ ኢትዮጵያ ዉስጥም ከኢትዮጵያ ዉጭም መብቱንና ነጻነቱን ተገፍፎ የሚኖር ባተሌ ህዝብ ሆኗል። የአማራ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት ነኝ ባዩ አለምነዉ መኮንን እንደማናችንም እግዚአብሄር በአምሳያዉ የፈጠረዉ ሰዉ ነዉ፤ ታድያ ለምንድነዉ ሂሊና የሌላቸዉና ነገሮችን አመዛዝነዉ የመመልከት ባህሪይ የልታደላቸዉ እንስሳት እንኳን የማያደርጉትን አስጸያፊ ነገር እሱ በገዘ ወገኖቹ ላይ ያደረገዉ? በእርግጥ ይህንን ጥያቄ አለምነዉ በጥቅም የተገዛ ወይም ለሆዱ ያደረ ሰዉ ነዉ ብለን በቀላሉ መልሰን ማለፍ እንችል ይሆናል፤ ነገር ግን የኢትዮጵያ ህዝብ ከብዙ አፍሪካዉያን በተለየ መልኩ ነጻነቱንና አንድነቱን ጠብቆ መኖር የቻለበትን ምክንያት ለምንረዳ ሰዎች ለዚህ ጥያቄ የሚሰጠዉ መልስ የችግሩን ያክል የተወሳሰበ መሆኑን እንረዳለን። ይህንን ስለምንረዳም ነዉ ኢትዮጵያንና ህዝቧን ከወያኔ መዳፍ ዉስጥ ፈልቅቆ ለማዉጣት መከፈል ያለበት መስዋዕትነት የእያንዳንዱን ኢትዮጵያዊ ቤት ያንኳኳል የምንለዉ።
ወያኔ ወይም ህወሀት በሚባለዉ የዘረኞች ድርጅት ዉስጥ የታቀፉ ሰዎች ስልታዊ አላማ አንድና አንድ ብቻ ነዉ- እሱም ኢትዮጵያ የምትባል ገንዘብና ንብረት የምትታለብ ላም ወተቷ እስኪነጥፍ ድረስ ብቻችንን እንለባት የሚል የስስት አላማ ነዉ። ይህንን የስስት አላማ ተግባራዊ ለማድረግ የነደፉት እስትራቴጂ ደግሞ የአላማችን ዋነኛ ጠላት ነዉ ብለዉ የሚያምኑትን የአማራዉን ህዝብ መግደል፤ ማሰር፤ ማሳደድ፤ ማፋናቀል፤ መደብደብና ማዋረድ ነዉ። ይህንን ከጠላቶቻችን ከነሙሶሊኒና ግራዚያኒ የተማሩትን አማራዉን የማሳነስና የማጥፋት ስልት ደግሞ እግራቸዉ አዲስ አበባን ከረገጠበት ቀን ጀምሮ የአማራዉን ግዛት ቆርሰዉ የራሳቸዉ በማድረግና አማራዉን በመግደል፤ በማሳደድና በማሰር በተግበር አሳይተዉናል ዛሬም እያሳዩን ነዉ።
የወያኔ ዘረኞች የቂም በቀል እርምጃዎች ሁሉ ያነጣጠሩት በአለምነዉ መኮንንና በወገኑ የአማራ ህዝብ ላይ ነዉ፤ ወያኔ ወልቃይት ጠገዴን ቆርሶ የወሰደዉ ከአለምነዉ መኮንንና ከወገኑ ከአማራ ህዝብ ላይ ነዉ፤ ከጉራ ፈርዳና ከቤንሻንጉል አካባቢዎች ሂድ ከዚህ ተብሎ የተፈናቀለዉ ህዝብ አለምነዉ መኮንን እመራዋለሁ የሚለዉ የአማራዉ ህዝብ ነዉ። ታድያ አለምነዉ መኮንን እሱንና የገዛ ወገኖቹን ለዘህ ሁሉ ዉርደትና መከራ የዳረጉትን የወያኔ ዘረኞች ለማስደስት ሲል የተወለደበትን ማህበረሰብ መሳደቡ ምን ይባላል? ወያኔ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያስተማረዉ መጥፎ ነገር ቢኖር ዘረኝነት ነዉ፤ አለምነዉ መኮንን በዚህ መጥፎ የወያኔ ትምህርት ተለከፈ ብለን ብናምን እንኳን ዘረኝነት የራስን ዘር ከሁሉም በላይ እንድናይና ሌሎችን እንድንጠላና እንድንንቅ ያደርገናል እንጂ የራሳችንን ዘር እንድንሰድብና እንድናዋርድ አያደርገንም። ታድያ አለምነዉ መኮንንን የተጠናወተዉ የወያኔ ዘረኝነት ነዉ ወይስ የሚያድኑትን እያስጠላ የሚገድሉትን የሚያስወደድ የታምራት ላይኔ በሽታ ነዉ?
ሌላዉ የአለምነዉ መኮንንና የብአዴን ችግር አለምነዉ ያንን አሳፋሪ ንግግር ካደረገና ንግግሩ የህዝብ ጆሮ ዉስጥ ገብቶ አገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ ብዙ ሰዎችን ካስቆጣ በኋላ ጥፋታቸዉን ተረድተዉ ህዝብን ይቅርታ አለመጠያቃቸዉና ሌላ ቢቀር አስተዳድረዋለሁ የሚለዉን ህዝብ ሙልጭ አድርጎ የሰደበዉን ሰዉ ህዝብን ከመምራት ሀላፊነት ቦታ ላይ እንዲነሳ አለማድረጋቸዉ ነዉ። አለምነዉ መኮንን የአማራን ህዝብ ከተሳደበ በኋላ ወያኔም ሆነ ብአዴን ከመጋረጃ ጀርባ የተባባሉትን ነገር ባናዉቅም ስድቡን አስመልክቶ በግልጽ ህዝብ እንዲያዉቀዉ የወሰዱት ምንም እርምጃ እንደሌለ ግን በሚገባ እናዉቃለን። ይህ የሚያሳየን ወያኔና ብአዴን ለህዝብና ለአገር ምንም ደንታ እንደሌላቸዉ ብቻ ሳይሆን እነዚህ ሁለት ጸረ ህዝብ ድርጅቶች ህዝብን እንዳሻን ረግጥን መግዛት እንችላለን የሚሉ ዕብሪተኞች እንደሆኑ ነዉ። የወያኔ ሹሞችና በየቦታዉ የበተኗቸዉ ሆዳም አፈቀላጤዎቻቸዉ የአለምነዉ መኮንንን መረን የለቀቀ ንግግር ለማስተባበልና እንዲያዉም ተባለ የተባለዉ ንግግር ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሆን ብለዉ ያቀነባበሩት የፈጠራ ስራ ነዉ እያሉ ህዝብን ለማሳመን ብዙ ደክመዉ ነበር፤ ነገርግን ብዙም ሳይቆይ ግለሰቡ በባዕዴን ስብሰባ ላይ የደረገዉ ንግግር በመጀመሪያ በኢሳት ሬድዮና ቴሌቪዥን ከዚያም በማህበራዊ ሜድያዎችና በተለያዩ ድረገጾች ላይ በብዛት መሰራጨት ሲጀምር ወያኔና ቡችሎቹ ማስተባበሉን ትተዉ ሳይወዱ በግድ ዝምታን መርጠዋል።
ወያኔና ብአዴን ህዝብን ሰድበዉና አዋርደዉ ዝምታን ቢመርጡም የተሰደበዉ የኢትዮጵያ ህዝብና መሪ የፖለቲካ ድርጅቶቹ ግን የአማራን ህዝብ አስጸያፊ ስድብ የሰደበዉ አለምነዉ መኮንን ከጥፋቱ ጋር ተመጣጣኝ የሆነ እርምጃ እስካልተወሰደበት ድረስ ዝም እንደማይሉ ለሚመሩት ህዝብም ለወያኔም ይፋ አደረጉ። በተለይ አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲና መላዉ ኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ አለምነዉ መኮንን የሰደበዉ የአማራ ህዝብ በክልሉ ዋና ከተማ ባህር ዳር ዉስጥ በነቂስ ወጥቶ ተቃዉሞዉን እንዲያሰማ የሰላማዊ ሠልፍ ጥሪ አደረጉ። ይህ የተቃዋሚ ፓርቲዎች የሠላማዊ ሠልፍ ጥሪ ለህዝብ ከተላለፈና ህዝቡ ቁጣዉን ከመግለጽ ወደኋላ እንደማይል ከተረዱ በኋላ ነበር እነ አለምነዉ መኮንን ሰድብዉት እንዳሻህ ብለዉ የዘጉትን ህዘብ በፕሬስ መግለጫ ስም እንደገና ማደናገር የጀመሩት። እዚህ ላይ አንድ እጅግ በጣም የሚያናድድና አንጀት የሚያሳርር ነገር ቢኖር ባለፈዉ ሐሙስ አለምነዉ መኮንን በሰጠዉ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በጉጉት ይጠበቅ የነበረዉ ይህ ግለሰብ የሰደበዉን ህዝብ ይቅርታ ይጠይቃል ተብሎ ነበር። ሆኖም አለምነዉ መኮንን፤ብአዴንና ህወሀት ከዕባብ እንቁላል አርግብ እንደማይጠበቅ በግልጽ አሳይተዉናል።
ባለፈዉ ኃሙስ ዬካቲት 13 ቀን 2006 ዓም አለምነዉ መኮንን የአገር ዉስጥ ጋዜጠኞች ያንን መረን የለቀቀ ስድቡን አስመልክተዉ የጠየቁትን ጥያቄ ሲመልስ እዉነትም “ከባዶ ጭንቅላት ባዶ እግር ይሻላል” የሚያሰኝ የቂል መልስ ስጥቷል። ነፃ ሜድያ በሌለባት ኢትዮጵያ ዉስጥ እንዳሰኘዉ መለፍለፍ የለመደዉ አለምነዉ መኮንን “ተቃዋሚዎች አለ ያሉትን ነገር እኔ በፍጹም አላልኩም . . . እኔ ለህዝብ ክብር ያለኝ ሰዉ ነኝ በማለት ነገሩ እየቆየ ሲሄድ እሱ እራሱ የተናገረዉ ንግግር ገርሞት “እኔ እንዴት እንደዚህ ልል እችላለሁ”ሲል ጋዜጠኞች የጠየቁትን ጥያቄ መልሶ እራሱን ጠይቋል። ይህ እፍረተ ቢስ ሰዉ ህዝብን የተሳደበዉ አልበቃ ብሎት ጭራሽ ጥፋቱን በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ ለማላከክ ሲሞክር ተድምጧል። ማንም ሰዉ ተናገር ብሎ ሳያስገድደዉና ቁጭ ብለዉ የሚያዳምጡት ሰዎች እየሳቁ በራሱ አንደበት የተናገረዉን ፀያፍ ንግግር ተቃዋሚዎች መሪዎችን ከህዝብ ለመነጠል ሆን ብለዉ የሰሩትና በቆርጦ ቀጥል የኮምፒተር ዘዴ ያቀነባበሩት ነገር ነዉ እንጂ ዬኔ ንግግር አይደለም ሲል የራሱን ድምፅ ዬኔ አይደለም ሲል ሽምጥጥ አድርጎ ክዷል።
ከአህያ ጋር የዋለች ጊደር ተምራ የምትመጣዉን ነገር እናዉቃለንና ከወያኔ ዘረኞች ጋር ለአመታት የከረመዉ አለምነዉ መኮንን በመዋሸቱ ብዙም ላንፈርድበት እንችላለን፤ ደግሞም ወያኔና ዉሸት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸዉና ወያኔን ባየን ቁጥር ትዝ የሚለን እንደ ሰዉ ቆሞ የሚሄደዉ ዉሸቱ ነዉና የአለምነዉ ዉሸት በፍጹም አይገርመንም። ይልቅ እኛን የገረመን አለምነዉ መኮንን የራሱን ድምጽ ዬኔ አይደለም ማለቱ ነዉ። መቼም አንድ ሰዉ ለይቶለት አማኑኤል ካልገባ በቀር እኔ “እኔ” አይደለሁም ብሎ የመናገር ደረጃ ላይ የሚደርስ አይመስለንም። ደግሞስ አለምነዉ መኮንን የማንሰማዉ መስሎት ባልተገራ አንደበቱ ህዝብን ሲሳደብ በድንገት ሰምተነዉ ነዉ እንጂ እስኪ እግዚአብሄር ያሳያችሁ አለምነዉ መኮንንን ማን ከቁም ነገር ቆጥሮት ነዉ የሱን ተራ ንግግር አየቆረጠ የሚቀጥለዉ? ማንስ ስራ የፈታ ሰዉ ነዉ የራሱንና የኮምፒተሩን ግዜ የአለምነዉ መኮንንን ቆሻሻ ንግግር ቆርጦ በመቀጠል የሚያጠፋ?
ሌላዉ የአለምነዉ መኮንን ጉድ ይህ ሴራ ተቃዋሚ ድርጅቶች መሪዎችን ከህዝብ ለመነጠል የሚያደርጉት ሴራ ነዉ ብሎ መናገሩ ነዉ። ወይ ጉድ . . . “ ወግ ነዉ ሲዳሩ ማልቀስ” ይላል የአገራችን ሰዉ። ለመሆኑ ጭንቅላተ ባዶዎቹ የወያኔና የብአዴን መሪዎች ቀድሞዉኑ ከህዝብ ጋር መች ገጥመዉ ያዉቃሉና ነዉ ተቃዋሚ ድርጅቶች እነሱንና ህዝብን ለመነጣጠል እያሴሩ ነዉ ተብሎ የሚነገረዉ? ወንድምዬ የምትሰማኝ ከሆነ እናንተና ህዝብ ዉኃና ዘይት ናችሁ፤ ተገናኝታችሁም አንድ ላይ ሆናችሁም አታዉቁም። በዚህ ስድባችሁ፤ ክህደታችሁና ዕብሪታችሁ ደግሞ ለወደፊትም ቢሆን ከህዝብ ጋር አትገጥሙም። ከህዝብ የነጠላችሁ ክፉ ስራችሁና መጥፎ ጠባያችሁ ነዉ እንጂ ተቃዋሚዎች አይደሉም።
አለምነዉ መኮንን እሱ እራሱ የአማራ ተወላጅ ነዉ፤ ያንን የመሰለ አስጸያፊ ንግግር የተናገረዉም በአማራ ህዝብ ላይ ነዉ፤ሆኖም በዘለፋዉና በዉርደቱ አንጀቱ ያረረዉ ወይም ዘለፋዉ ያነጣጠረዉ በአማራ ህዝብ ላይ ብቻ ነዉ ብለን የምናስብ ሰዎች ካለን እኛም ዘለፋዉን እንደሰነዘረዉ ሰዉ እራሳችንን ስተናል፤ ወይም ዋነኛዉ የወያኔ ወጥመድ ዉስጥ ገብተናል አለዚያም አርቆ የመመልከት ችሎታችን ከከዳን ቆይቷል ማለት ነዉ። ዘለፋዉና ንቀቱ የተሰነዘረዉ በሁላችን ላይ፤ ነዉ፤ የተዋረድነዉም ሁላችንም ነን፤ ስለሆነም አለምነዉንና አቅፈዉት ከለላ የሰጡትን ሁሉ ለፍርድ ለማቅረብ የሚደረገዉ ትግል የሁላችንም ትግል መሆን አለበት። ባህር ዳር ዉስጥ የታየዉ ህዝባዊ ቁጣ በመላዉ ኢትዮጵያ እንደ ሰደድ እሳት ተቀጣጥሎ ወያኔ የገነባዉን ዘረኛ ስርዐት ለብልቦ ከምድረ ኢትዮጵያ እስኪያጠፋ ድረስ ትግላችን መቀጠል አለበት። በዚህ ትግል ዉስጥ “እኔ” ወይም “አንተ” የሚባል ቃል በፍጹም ሊኖር አይገባም። የትግላችን ብቸኛ መነሻና መድረሻ “እኛ “ ብቻ መሆን አለበት። ወያኔን አጥፍተን እንደ ህዝብና እንደ አገር በሠላም፤ በነፃነትና በብልጽግና መኖር የምንችለዉ ኢትዮጵያዊነታችን “እኛ” በሚለዉ አስተሳሰብ ላይ ሲገነባ ብቻ ነዉ።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

ከአውሮፕላኑ ጠለፋ በኋላ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ም/ሥራ አስኪያጅ ካፒቴን ደስታ ዘሩ ለቀቁ

march2/2014

በአንድ ጎሳ እና ቋንቋ አመራር ስር ወድቋል በሚልና በዘረኝነት ሰራተኞቹን ፍዳቸውን እያሳየ ነው በሚል የሚተቸው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምክትል ስራ አስኪያጅ እና የበረራ ክፍል ሃላፊ የሆኑት ካፒቴን ደስታ ዘሩ ስልጣናቸውን መልቀቃቸውን የኢትዮጵያ የሽግግር ምክር ቤት ምንጮቹን ጠቅሶ ለዘ-ሐበሻ በላከው መረጃ አስታወቀ። እንደ ሽግግር ምክርቤቱ ዘገባ የስልጣን መልቀቂያው ጉዳይ ግልጽ ምን እንደሆነ አይታወቅም።

ሌሎች ምንጮች የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ተጠልፎ ወደ ስዊዘርላንድ በረዳት ካፒቴን ሃይለመድህን አበራ ካረፈ በኋላ በአየር መንገዱ ውስጥ በተነሳው አለመግባባት ሊሆን ይችላል የሚሉ አስተያየቶችን እየሰጡ ይገኛሉ።

ምንጮቹ የአየር መንገዱ አብራሪዎች በቂ እውቀት እና ችሎታ እያላቸው ከውጪ አብራሪዎችን በማስመጣት ለኢትዮጵያውያኑ እድገት እና የበረራ ፍቃድ መከልከል እንዲሁም አላስፈላጊ የሆነ መንግስታዊ የደህንነት ወከባ እና የአይነ ቁራኛ ጥበቃ በአብራሪዎች ላይ ከመደረጉም በላይ የስራ መብቶቻቸው እና የሰብአዊ መብቶቻቸው በዘረኝነት ላይ የተመረኮዘው የአየር መንገዱ ማንጅመንት እንደማያከብርላቸው እነዚሁ ምንጮቹ አክለው የሚገልጹ ሲሆን፤ በወያኔ ፈጠራ ረዳት አብራሪው ሃይለመድህን አበራን “የአእምሮ በሽተኛ ነው” በሚል የተወራው ወሬም በአየር መንገዱ የሚበሩ ሰዎች ቁጥር እንዲቀንስ ምክንያት እየሆነው እንደሆነም ምንጮች ይናገራሉ።

ዘ -ሐበሻ

የህወሓቶች ገመና ሲጋለጥ የካድሬው ወንጀል በማይጨው ሆስፒታል

march1/2014


ብርሃኑ ሃይለስላሴ ይባላል። አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ እያለ ጥናቱን ትቶ በካድሬነት ተግባር የተሰማራ እንደነበር አውቃለሁ። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የምንማር የትግራይ ልጆችን እየሰለለ ነበር የሚውለው።

ተመረቀና በህወሓት አባልነቱ መሰረት የትምህርት ዉጤቱ ግምት ዉስጥ ሳይገባ፣ ሳይወዳደር (ሌሎች ብቁ ሰዎች እያሉ) በእምባ አለጀ ወረዳ የጤና ጥበቃ ሐላፊ ተደርጎ በፓርቲ በመሾሙ ዓዲሽሁ ከተማ ገባ። በዓዲሽሁ ከተማ ብዙ ሴቶችን ደፈረ። ህዝብ ጮሆ። ሰሚ የለም። ምክንያቱም ሐላፊ ነው።

ሴቶችን በመድፈር ወንጀል ከመክሰስ ይልቅ ሌሎች ሰራተኞች ያላገኙት የማስተርስ ትምህርት ዕድል ተሰጠው። ሴቶች ስለደፈረ ተሸለመ ማለት ነው። በጦላይ ለስልጠና ተልኮ እዛም ሌላ ሴት ደፈረ። የተደፈረች ሴት የሕግ ከለላ አጥታ ከሱ ጋር እንድትታረቅና ክስ ላትመሰርት ተገደደች።

ከስልጠና በኋላ ህወሓቶች የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል CEO አድርገው ሾሙት። እነሱ ምን ይሳናቸዋል!? በማይጨው ከአንድ ዓመት ባልበለጠ ግዜ ዉስጥ አስራ አራት ሴቶችን ደፈረ፤ ስልጣኑን ተገን በማድረግ። ሴቶች አቤት ይላሉ። ግን ሰሚ የለም። በማይጨው ሰው በመኪና ገጨ። ራሱ ሰው ገጭቶ ሽፌሩ እንደገጨ ለማስመሰልና ከቅጣት ለመዳን ከሽፌሩ ጋር ተዋዋለ። ክስ ተመስርቶበት፣ በፖሊስ ተይዞ በስድስት ሺ ብር ዋስ ተለቀቀ።

ይህን ሁሉ ግፍ ሲፈፅም የማይጨው ኗሪዎችና የሆስፒታሉ ሰራተኞች ቅሬታ አሰሙ። ረበሹ። ተሰበሰቡ። የሆስፒታሉ ሰራተኞች ተሰብሰበው ከፓርቲ አባልነቱ እንዲወገድ ጠየቁ (ምክንያቱም የገዢው ፓርቲ አባል በመሆኑ ስልጣኑ ተገን አድርጎ ነው ግፍ እየፈፀመ ያለው ከሚል እሳቤ)። ከስራ (ከሐላፊነቱ) ታግዶ በፖሊስ እንዲያዝ ወሰኑ። ቢሮው ታሽጎ ሁለቴ ቁልፍ ሰብሮ መግባቱ ተረጋገጠ። ማንም አልጠየቀውም።

አቶ ብርሃኑ ሃይለስላሴ በሰራተኞቹ ስብሰባ ቀርቦ ሁሉም የተጠቀሱት ወንጀሎች መፈፀሙ አምኖ ይቅርታ ጠየቀ። በተበዳዮቹና ሰራተኞቹ ግፊት በፖሊስ እንዲታሰር ተደረገ። ህዝቡ ተረጋጋ። እኛም “ኮርማው ታሰረ!” ብለን በፌስቡክ ፃፍን። ህወሓቶች ለምን አስራ ስምንት ሴት እስኪደፍር ድረስ ዝም አሉት? ሕግ ለካድሬዎችስ አይሰራም ወይ? ብለን ጠየቅን። የህወሓቶች አድሎአዊ አሰራር ወቀስን። መታሰሩ ግን ጥሩ መሆኑ ጠቆምን።

አቶ ብርሃኑ በፖሊስ ከታሰረ ከሁለት ቀናት በኋላ መለቀቁ ሰማሁ። መለቀቁን አስመልክቼ በፌስቡክ ፃፍኩ። መለቀቁ ግን በሌላ አካል አልተረጋገጠም ነበር።

አሁን ከአስራ ስምንት ሴቶች በላይ የደፈረ ባለስልጣን ምን ቢቀጣ ጥሩ ነው!? አሁን በደረሰኝ መረጃ መሰረት አቶ ብርሃኑ አልታሰረም። ወደ ሌላ የስራ ቦታ ተዛወረ እንጂ። ህወሓቶች አንድ ባለስልጣን ወንጀል ከሰራ ባለስልጣኑ ከመቅጣት ይልቅ ወደ ሌላ የስራ ሐላፊነት ይቀይሩታል። ቅጣት ግን የለም። ሽልማት እንጂ።

አሁን አቶ ብርሃኑ ከዞን (ከማይጨው) ወደ ክልል (መቐለ) የስልጣን እርከን አድጎ በመቐለ የትግራይ ክልል የጤና ቢሮ የHMIS ዲፓርትመንት expert ሁኖ በሙሉ ደሞዝና የተሻለ የሐላፊነት ደረጃ እየሰራ ይገኛል። ይህን ጉዳይ የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል ሐላፊዎች አረጋግጠውታል። ለምን የሚል ጥያቄም አስነስተዋል። አሁን በማይጨው ሆስፒታል ሰራተኞች ጥሩ ስሜት የለም።

አሁን እንደሰማነው ግን ከእሰር የተፈታው በህወሓቶች ነው። በክልል ጤና ቢሮ እንዲሰራ ትእዛዝ ያስተላለፈውም አቶ ሃይሉ አስፈሃ የተባለ የደቡባዊ ዞን ዋና አስተዳድሪና የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል የቦርድ ሰብሳቢ ነው። የሆስፒታሉ ሰራተኞች ይሁኑ የቦርዱ አባላት ሳይሰበሰቡና ምንም መረጃ ሳይኖራቸው አቶ ሃይሉ አስፈሃ (የቦርዱ ሰብሳቢ) ግን የቦርዱ ዉሳኔ እንደሆነ አድርጎ ደብዳቤ በመፃፍ በክልል ጤና ቢሮ እንዲቀጠር ማድረጉ ለማረጋገጥ ተችሏል።

ባሁኑ ሰዓት በማይጨው ከተማ ኗሪዎችና ለምለም ካርል ሆስፒታል ሰራተኞች በከባድ ቀውስ ዉስጥ እንደሚገኙ ለማወቅ ችያለሁ። የማይጨው ህዝብ በዋና አስተዳዳሪው አቶ ሃይሉ አስፈሃ ከፍተኛ ቅሬታ እያነሳ ሲሆን ህወሓቶች ለህዝብ ያላቸው ንቀት እያሳዩን ነው በሚል የተቃውሞ መንፈስ እንዳለ ከማይጨው ኗሪዎች የደረሰኝ መረጃ ያመለክታል።

አይ ህወሓቶች መቼ ነው ለህዝብ ደህንነት የምትቆሙ? በትግራይ የሚፈፀሙ አስተዳደራዊ በደሎች ቢጋለጡኮ ስንት ጉድ በሰማን ነበር! ይህን ጉዳይ እስከመቼ እንችለዋለን?!

በህወሓት እምነት የለኝም። ከዚህ በላይ ምን ሊያደርገን ይችላል!? እናንተስ?

It is so!!!

Saturday, March 1, 2014

በኖርዌይ የሚኖሩትን ኢትዮጵያን ስደተኞችን የአኖኖር ሁኔታ በሚመለከት ህዝባዊ ውይይት እና የኢሳት ምሽት ፕሮግራም በኖርዌይ ኦስሎ ከተማ ተካሄደ (በገዛኸኝ አበበ ኖርዌይ)

March 1/2014

በኖርዌይ ከተማ ኦስሎ በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያኖች በኖርዌይ የሚኖሩትን ኢትዮጵያን  ስደተኞችን የአኖኖር ሁኔታ በሚመለከት   ሐሙስ የካቲት20,2006 ዓ ም  በአንድ ላይ በመሰብሰብ ውይይት እና ምክክር አድርገዋል :: ስብሰባው በኖርዌይ የስደተተኛ ማህበር የተዘጋጀ ሲሆን በስብሰባው  ላይ ከተለያዩ ከተሞች የመጡ እና በኦስሎ ከተማ የሚኖሩ ኢትዮጵያኖች የተሳተፉ ሲሆን የኢሳት ጋዜጠኛ የሆኑት ጋዜጠኛ መታሰቢያ ቀፀላ እና ጋዜጠኛ ደረጀ ሃብተወልድ ጋር በመሆን በኖርዌይ ያሉ የኢትዮጵያውያን ስደተኞችን የአኗኗር ሁኔታ እንዲሁም ለስደት ያበቋቸውን ምክንያቶች በተመለከተ ሰፋ ያለ ውይይት አድርገዋል፥፥

   በስብሰባውም ኢትዮጵያኖች በሀገራቸው እንዳይኖሩ የወያኔ መንግስት በሚያደርስባቸው ጫና እና በደል ሀገራቸውን ጥለው ቢሰደዱም ነገር ግን ኖርዌይ ከገቡ በኋላም የኖርዌይ መንግስት የኢትዮጵያኖችን የፓለቲካ ጥገኝነት በሚገባ እንደማያየው እና እንደማይቀበለው በየጊዜው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ የተለያየ ጫና እንደሚያደርስባቸው በሰፊ ውይይት ያደረጉ ሲሆን  በስብሰባው ላይ ከነበሩት ተሳታፊዎች የተለያዩ አስተያየቶች እና የየእራሳቸውን የህይወት ተሞክሮ እና ኖርዌይ ከገቡ ጀምሮ በሕይወታቸው ያለፈውን እና እየኖሩ ያለው ኑሮ ምን እንደሚመስል እንዲሁም ለስደት ያበቋቸውን ምክንያቶች በተመለከተ ውይይት አድርገዋል  ::

 አንዳንድ ሰዎች በተለያየ ምክንያት ከሀገር እየወጡ  ኖርዌይ ገብተው የፖለቲካ ጥገኝነት በመጠየቅ ወረቀት ካገኙ በኋላ ወይም ፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂ መስለው ትንሽ ጊዜ በመቆየት ካዛም በገዛ ፍቃዳቸው ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመለሱ እና  በኢትዮጵያ መንግስትም ምንም አይነት በደል እንዳልደረሰባቸው የኖርዌይ መንግስት እንደሚያውቅ ከዚህም የተነሳ ሌሎች ኢትዮጵያን ስደተኞ ላይ ወደ የፓለቲካ ጥገኝነት እንደማይቀበል ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱም የኖርዌይ መንግስት የተለያየ ጫና እንደሚያደርስባቸው በስብሰባው ከነበሩ ተሳታፊዎች የተገለጸ ሲሆን ነገር ግን  እንደነዚህ አይነት ሰዎች በመጀመሪያ ወደ ኖርዌይ የሚመጡበት ምክንያት እንዳላቸው እና ምክንያታቸውም  በኖርዌይ የሚኖሩትን እውነተኛ የወያኔ ተቃዋሚዎ ችን ለመሰለል እና ለማደን ሲሆን  እንደነዚህ አይነት ሰዎችን እንዳሉ እና እንደሚያውቆቸው ነገር ግን ኢትዮጵያውን እነዚህ የወያኔ ሰላዮች መፍራት እንደሌለባቸው ይህንንም ለኖርዌይ የስደተኞችን ጉዳይ ለሚመለከተው መስሪያ ቤት utlendingsnemnda (UNE) በተለያየ ጊዜ መሳወቃቸውን በስብሰባው ላይ ተገልጾል ::

በስብሰባው ላይ በመገኛት በኖርዌይ ያሉ የኢትዮጵያውያን ስደተኞችን የአኗኗር ሁኔታ ምን እንደሚመስል ጥያቄ ሲጠይቁት የነበሩት ጋዜጠኛ መታሰቢያ ቀፀላ እና ጋዜጠኛ ደረጀ ሃብተወልድ ኖርዌይ በሚኖሩት ኢትዮጵያኖች በሚያደርጉት ትግል ወይም እንቅስቃሴ በጣም እንደሚደሰቱ እና እንደሚደነቁ በመናገር ማንኛውንም ማድረግ ያለባቸውን እና ማድረግ የሚችሉትን  ነገሮች በማድረግ ከጎናቸው በመቆም አብራቸው እንደሚሰሩ ቃል ገብተውላቸዋል::

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛሬው እለት ቅዳሜ የካቲት 22, 2006 ዓም በዛው በኖርዌይ ኦስሎ ኢሳት የእኔ ነው (ESAT IS MINE) በሚል መሪ ቃል የኢሳት ምሽት ፕሮግራም የተደረገ ሲሆን  የኢሳት ጋዜጠኛ የሆኑት ጋዜጠኛ መታሰቢያ ቀፀላ እና ጋዜጠኛ ደረጀ ሃብተወልድ የዝግጅቱ ተጋባዥ እንግዶች በመሆን በፕሮግራሙ ላይ ተገኝተዋል ::

 በፕሮግራሙ የተለያየ ዝግጅቶች የተደረጉ ሲሆን በተለያዩ ሰዎች የኢትዮጵያን  የፖለቲካ ሁኔታ የሚዳስስ ጹሁፍ የቀረበ ሲሆን  ለኢትዮጵያ ህዝብ ያለምንም ፖለቲካዊ ወገንተኝነት መረጃን በማቅረብ ለኢትዮጵያ ሕዝብ አይን እና ጆሮ የሆነውን  ኢሳትን መርዳት እንደሚገባ በኖርዌይ የሚኖሩ የኢትዩጵያን ኮሚኒቲ ሊቀመንበር አቶ ፋሲል እና  የኢሳት ኖርዌይ ዋና ተወካይ ጋዜጠኛ አበበ ደመቀ  እንዲሁም በኖርዌይ የኢሳት ም/ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ሙባረክ ንግግር አድርገዋል::በተጨማሪም አቶ እንግዳ ታደሰ የኢሳት በኖርዊይ አመሰራረት እና ስለ ኢሳት ባለቤትነት በህዝብ ዘንድ የሚወራው የተሳሰት ወሬ ትክክል እንዳልሆነ ኢሳት የማንም የፖለቲካ ድርጅት ንብረት እንዳልሆነ እና ኢሳት የኢትዮጵያ ሕዝብ ንብረት እንደሆነ ሕዝቡም ኢሳት የእኔ ነው በሚል ስሜት ኢሳትን እንዲረዳ እና እንዲደግፍ የኢሳትም አባል እንዲሆን ጥሪ በማቅረብ ንግግር አድርገዋል::


በፕሮግራሙ ላይ የተለያዩ አስደሳች ግጥሞች እና መነባንቦች በተለያዩ ሰዎች የቀረበ ሲሆን በጋዜጠኛ ደረጀ ሃብተወልድ ኑ ሀገራችንን እንስራ በሚል ርዕስ ኢትዮጵያኖችን ለስደት የዳረገው ወያኔ በሰዎች ላይ የሚያደርሰው ግፍ እና በደል እንደሆነ እና  ስደት በሰው ሀገር  ምንም ቢመችም ደስታን እንደማይሰጥ የስደትን  ህይወት በሚመለከት አስደሳች እና ልብን የሚነካ ግጥም የቀረበ ሲሆን በጋዜጠኛ መታሰቢያ ቀፀላም ሁሉም ሰው የሀገሩ ሁኔታ ግድ እንዲለው እና ስለ ሀገር መቆርቆር ፣ሀገርን በሚመለከት ጉዳይ ላይ መሳተፍ  ፖለቲከኛ መሆን እንዳይደለ ሀገራችን ከወያኔ ስርዓት ነጻ እስከምትሆን ሁሉም ሰው በጽናት መታገል እንደሚገባው አጽንኦት ሰጥታ ንግግር ያደረገች ሲሆን በስብሰባው ላይ ዋናው አላማ የነበረው ማንኛውም ሰው ኢሳት የእኔ ነው በሚል ቃል በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያኖች የኢሳት የባለቤትነት ስሜት ተሰምቷቸው ኢሳትን እንዲረዱ ከመሆኑ አኳያ በፕሮግራሙ ላይ ሲተላለፉ የነበሩት ግጥምም ሆነ ንግግር በዋናነት ኢሳት በመርዳት ላይ ያተኮረ ነበር :: በእለቱ የፕሮግራሙ አላማ የነበረው የገቢ ማሰባሰቢያ የጨረታ ፕሮግራም የተካሄደ ሲሆን በእለቱ ለኢሳት ማጠናከሪያ የሚሆን የተለያዩ ምግቦች ፣መጠጦች፣ ቀለበቶች፣እና ቲሸርቶች ለሽያጭ ቀርበዋል :: በተለያየ ጊዜ ለኢሳት እና ለፖለቲካ ድርጅቶች በሚደረጉ የገንዘብ ገቢ ማሰባሠቢያ ፕሮግራም ላይ በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያኖች ከየትኛውም ሀገር በበለጠ ንቁ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ይታወቃል::

        gezapower@gmail.com

በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙት ዩኒቨርስቲዎች የካድሬዎች መመልመያ እንደሆነ ተጠቆመ

march 1/2014

ዩኒቨርስቲዎች (ጥራት ያለው ሳይንሳዊ ስልጠና የሚሰጥባቸው የትምህርት ማእከላት ሳይሆኑ) ታማኝ ካድሬዎች የሚመረቱባቸው ካምፖች 'የሆኑበት ሁኔታ ነው ያለው'።
ተማሪዎች ለስርዓቱ ታማኝ ካድሬዎች ሁነው ካገለገሉ ሲመረቁ ምርጥ የተባለ ሥራ እንደሚያገኙ ቃል ይገባላቸዋል። እንደውጤቱም ተማሪዎች ጥሩ ውጤት ይዘው ለመመረቅ ጥረት ከማድረግ ይልቅ ታማኝ ካድሬ መሆን ይቀላቸዋል።
ግን በመንግስት መስርያቤት ለመቀጠር የሀገር ዜጋ መሆን በቂ ነው። የሁሉም ሰው መብት ነው። ለማወዳደር ከተፈለገ ደግሞ (የፖለቲካ ታማኝነት ሳይሆን) የትምህርት ማስረጃና ብቃት እንደመስፈርት ሊወሰድ ይችላል።
የመንግስት መስርያቤት በፖለቲካ ኣመለካከት፣ ዝምድና (ባጠቃላይ በሙስና) እየተያዙ ብዙ (በስርዓቱ ደህና ሰው የሌላቸው የዩኒቨርስቲ ሙርቃን) ስራ ኣጥተው እየተንገላቱ ይገኛሉ። ኣብዛኛው የስራ ኣጥነት ሁኔታ በፍትሕ እጦት ምክንያት የተፈጠረ ነው።
ስራ የያዙም ቢሆኑ፡ እድገታቸው (የደመወዝ ጭማሪ ኣክሎ) የሚወሰነው በስራ ገበታቸው ባሳዩት የኣፈፃፀም ብቃት ሳይሆን በፖለቲካ ኣመለካከታቸው ነው። ይህ ተግባር ፍትሕ ያጎድላል፤ ዜጎችም ይጎዳል። ሲል የገለጸው የመቀሌው ዩኒቨርስቲ መምህር እና የአረና የፖለቲካ ፓርቲ ድርጅት አባል የሆነው አብርሃ ደስታ ነው ። ይኅንን  አያይዞ ሲጠቁምፖለቲካዊ ሙስና በሃገሪቱ ላይ መንሰራፋቱን እና መቆም እንደሚገባው ንጹህ ዜጋዎችን ማፍራት ስንችል ለአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ብቻ ሊያጎበድዱ የሚችሉ ፣ሃገራዊ ግዴታም ሆነ ፍቅር የማኖራቸውን እና ሌሎችን የፖለቲካ አቅጣጫ እንዳያዩ የሚያደርጉ እቅድ ይዞ እንደሚንቀሳቀሱ ጠቁሞአል ። ቀድሞ የሃገር ወይንም የፖለቲካ ለውጥ የሚነሳው ከዩንቨርሲቲዎች በሚነሳ አተካሮ የነበረ ቢሆንም አሁን ግን ለጥቅም የተገዛ ወጣት ብቻ የሚፈለፈልበት ጉሮኖ ሆኖአል ሲል ጠቁሞአል ።