Friday, April 3, 2015

የአማራዉ ሕዝብ ሁኔታ፣ ለኢትዮጵያዉያን ሁሉ

April 3, 2015
ለማስታወስ ያህል የዛሬ ሶስት ዓመት “ሞረሽ የአማራ አብሮነት ድርጅት” ብለን እኔ ራሴ፡ አምባሳደር አያሌው ማንደፍሮ፡ አቶ ይስሃቅ ክፍሌና ዶክተር ምስማኩ አስራት ሁነን ግቡ ለአማራዉ እርዳታ ለመስጠት የሆነ ማሃበር አዘጋጅተንና አስመዝገበን ነበር፤ የድርጅቱም አላማ ከማናቸዉም የፖሊቲካ ንቅናቄ ነጻ የሆነ የመረዳጃ ማህበር ብቻ እንዲሆን ነበር።
Amhara Ethnic group members Ethiopia
ይህንን እርምጃ ለመዉሰድ የገፋፋን ባለፉት ዓመታት በተለይ የወያኔ ቡድን የመንግሥት ስልጣን ከያዘ ወዲህ በተለይ በአማራዉ ሕዝብ ላይ የሚያካሂደው ወሰን የለሽ ጭቆናና ግፍ፤ ሕዝቡን ለማጥፋት የምያደርገው ሙከራ በጣም አሳስቦንና አስጭንቆን ነው። በዚህም አንጻር በየቀኑ የሚወርድብት በደል አንሶ የአማራዉ ሕዝብ ቁጥር እስከ ስድስት ሚልዮን ተቀንሷል ይባላል። ይሄም የሕዝቡ ቁጥር ከሃገሪቷ ጠቅላላ እድገት ጋር እየተመዛዘነ እንዲካሄድ፤ እርጉዝናን ለመቆጣጠር በሚሰጠዉ ክትባትና ልዩ ልዩ መድሃኒት ስበብ፤ ሴቶችን ጭርሶ የሚያመክኑትን እንዲሰጥ ተብሎ በተቀናጀ ሴራ መደረጉ የማያጠራጥር ሆኗል።
ከሁሉ አስቀድሞ ይህ ሁሉ ኢሰባዊ በደልና ጥቃት የሚጣልበት የአማራ ወይንም የሃበሻ ሕዝብ ማን ነው፧ በራረጅም የታሪክ ጉዞ ከብዙ ነገዶችና ጎሳዎች ተጋብቷል፤ ተዋልዷል፤ ተዛምዷል፤ በዚህ ታሪካዊ ሂደት አብረን ተጉዘናል፤ ብዙ ችግር በጋራ አሳልፈናል፤ አበርን ደምተን አብረን ሞተን ኢትዮጵያ አገራችንን ነጻነቷንና ክብሯን ጥበቀን አቆይተናል፤ በኢትዮጵያዊነታችን ጸንተን እስካዛሬ ተጉዘናል።
ስለዚህ በቋናቋና በባህል አማራ ነን ስንል፤ በዘር ደግሞ ከልዩ ልዩ ነገድ ስለምንዋለድ የኢትዮጵያ ፍሬዎች ነን እንላልን፤ አማራ ወይም ሃበሻ የሚባለው በአንድ ጎሳ ወይም ባንድ አካባቢ አይተመንም፤ አይከለልም፤ በረጅም ክፍለ ዘመናት ታሪክ የተጥነሰሰ፤ የራሱን ቋንቋ፤ ፊደላትና ድርሰት፤ ፍልስፍናና ጥበባት ያመነጨ፤ የመንግሥት ሕግና ስርዓት የደነገገ፤ ይታላቅ ሃይማኖቶች ባለአደራ የሆነ፤ ከፍተኛ ስልጣኔ ለዓለም ያበረከተ ሕዝብ ነው።
የአማራው ብዛት ከግማሽ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያላነሰ ሲሆን፤ በጉልበትም፤ በችሎታም፤ በእዉቀትም የጎደለው ነገር ሳይኖር፤ ራሱን አዋርዶኖ አጎልብሶ የማንም መሳለቅያ ሁኗል፤ ይደበደባል፤ ይታሰራል፤ ይገደላል፤ ከተወልደበት ቦት እየተፈናቀለ በገዛ አገሩ ስደተኛ ሁኗል፤ የወያኔዎችና የአንድ አንድ ግለሰቦችና ፖሊቲከኞች የልፈፋና የግል አላማ የሚሰበክበት መሳርያ ሁኗል። ስለ አማራው መጎሳቆልና መወገር ብዙ ይወራል ይተቻል ነገር ግን እስካሁን ድረስ ካለበት ችግር ሊያድነው የሚችል አንድም አካል አልተገኘም። እንደዚህ ያለ ተግባር ለማድረግ በተመኮረ ጊዜ ከራሱ ከአማራው መሃል አፍራሽና ተቃራኒ ድርጊት ይፈጠራል፡ በዛሬ ወቅት የወያኔ ቡድን አገርን ቀጥቅጦ የሚገዛው ብቻዉን ሁኖ ወይም የአብዛኛውን ሕዝብ ድግፍ አግኝቶ አይደለም፤ ከአማራዉ ከኦሮሞው ከሌሎች ወገኖች ተባባሪና አብሮ አገብጋቢ ድጋፍ እያገኘ ነው።
በተለይ ባለፉት ስልሳ ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ በችግርና በድህነት እየታረዘ መድህን ይሆኑልኛል ብሎ ደሙን ተፍቶ ያፈራቸው ምሁራን ዛሬ በሚልዮን ይቆጠራሉ፤ በተቀረው የዓልም ክፍል ጊዝያዊና ዘመናዊ ዘዴ እያመነጨ የሕዝቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል አዉራ ሁኖ የሚመራዉ የተማረዉና ያወቀው መደብ ሲሆን፣ በሃገራችን ያለው ምሁር ይህንን ተግባር ለማሟላት አልቻለም። ነጻነትን ለመጎናጸፍ በሚደረግ ተጋድሎ ህብረሰቡ በሙሉ መሳተፍ አለበት፤ ሃብታሙም ደሃዉም በእኩያ የሚካፈሉት ግዴታ ነው፤ ይሄም የፖሊቲካ ወይም የሌላ ወገናዊነትን የሚነካ አይደለም፤ የዚህ ወይም የዝያ ድርጅት አባል ነኝ የሚያሰኝ አይደለም፤ ዛሬ በአማራው ላይ ነገ በኔ ብሎ የሚያሳስብ ነዉ፤ ወንድ ሴት ልጅ ሽማግሌ ሳይለይ የሁሉም የጋራ ትግል ነዉ።
በኢትዮጵያ ሕዝብ ዉስጥ የአማራዉ ህዝብ ቁጥር ከአንድ ሲሶ ይበልጣል እንጂ አያንስም፤ ይሔንን ያህል የሰው ጉልበት አቅፎ፤ በርካታ አዋቂዎችና ባለሃብቶች እያሉት፤ እንደዚህ ያለ ዉርደትና መስቃየት እስከ ጥፋት የሚያመራ ዘመቻ ሲካሄድበት አንገቱን ደፍቶ ሲቀበል ማየት ያሳፍራል፤ይጎመዝዛል፤ አለኝታን ያሳጣል። ያለመስዋእትነት የሚገኝ ነጻነትና ክብር የለም፤ ሁሌም አባቶቻችን እንዳደረጉት ተጋፍጦ መታገል አለ፤ ከንቱ ዛቻና ወሬ ድል አያስገኝም።
በተለይ ወጣቱ ትውልድ፤ የነገ ሰዉ የሆነው፤ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለው፤ የተያዘውን የጎሳ አወቃቀርና ዘመን አመጣሽ የባዕድ ባህልና ፖሊቲካ አሽቀጥሮ ጥሎ አዲሷን ኢትዮጵያ በታሪካዊ ቅርሷ ላይ መገንባት አለበት።
ከማክበር ሰላምታ ጋር፤
ኢምሩ ዘለቀ።

Thursday, April 2, 2015

ስልጣን ላይ አድሮ ለመገኘት ሃገርን መሽጥ፤ ህዝብን መሸፈጥ ለምን? እስከመቼ?

April 2, 2015
እስከ ነጻነት
የህወሃቱ መሪ መለስ ዜናዊ ሰሜን አፍሪቃ የተነሳሳው ህዝባዊ አመጽ በኢትዮጵያኖች ዘንድ መወያያ ርዕስ እንዳይሆንና አመጹም እንዳይዛመት “ዛሬን ስልጣን ላይ አድሮ መገኘት፤ ቀኑን እንዳመጣጡ ለማለፍ ስልት መቀየስ” በሚል እምነቱና ስልጣንን ከህዝብም ከሃገርም በላይ አምላኪነቱ የተነሳ: ለነገ ምን ችግር ያመጣል? ጉዳቱስ መጠኑና ስፋቱ ምን ያህል ይሆናል? ሃገር ሉዓላዊነትና ዘላቂ ብሄራዊ ጥቅም ላይ የሚኖረው አዎነታም ሆነ አሉታ ተጽዕኖ ሳያሳስበው: ብልጭ ባለለት ማምለጫ መንገድ ብቻ የሚንቀሳቀሰው መለስ “አባይን እገድባለሁ” የሚል ቅዥት ይዞ ብቅ እንዳለ ሁላችንም እናስታውሳለን። ይህን ያልታሰበበት፤ ያልተጠና፤ ህዝብ ያላወቀውና መክሮ ያልተስማማበትን ቅዥት በየሙያው ዘርፉ አንቱ የተባሉና የሃገራቸው ጉዳይ የሚያሳስባቸው ተናገረውበታል፤ ጽፈውበታል አስጠንቅቀዋል፡ ህወሃት ግን የዕለት ስልጣንና ከስልጣን የሚገኝ ጥቅም እንጂ የህዝብ ስሜትና ፍላጎት ስለማያስጨንቀው ሊሰማ አልቻለም፡ በምጣኔ ዘርፍ፤ በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ፤ በህግ ዘርፍ፤ በርካታ ባለሙያዎች አስተያየታቸውን ስለሰጡበት እኔ እሱ ላይ አልመለስም።
እኔ ማንሳት የምፈልገው: ከሙያው ቅርበት ካላቸው በስተቀር የኢትዮጵያ ህዝብ አያውቀውም ብዬ የምገምተውን: ማወቅ አለበት፤ አውቆም ለጥፋቱና ለሃገራዊ ሉዓላዊነት መደፈር ከህወሃት እኩል ተጠያቂ መሆኑን ሊያስገነዝብ ይችላል የምለውን አባይ ወንዝ ዙሪያ የተደረጉ ጥናቶችን፤ የቀረቡ ሃሳቦችንና እቅዶችን; ህወሃት የሄደበትን የተቃርኖ መንገድ በተመለከተ ይሆናል።
1.1 በአባይ ወንዝ ዙሪያ የተደረጉ አብይ ጥናቶች
በአባይ ዙሪያ የተደረገው የመጀመሪያ ጥናት በአሜሪካ ጂኦሎጂ ቅየሳ (United States Geological Surfay(USGS)) እ አ አ በ1960ዎቹ የነበረ ሲሆን በዚያን ጊዜ የተመረጡት አራት የግድብ ቦታውች ነበሩ፤ እነዚህም ከጎሃጽዮን-ደጀን አባይ ድልድይ ወደ ሱዳን አቅጣጫ ተከትለን ሲንሄድ በቀደም ተከተል (ካራዶቢ፤ ማቢል፤ መንዳያ እና የግርጌ (Karadobi, Mabil, Mandaia and Border) ናቸው።
ከታች ያለውን ንድፍ ይመልከቱ፡
Proposed dams on Blue Nile
ሁለተኛው ጥናት የተደረገው በ1980ቹ ሲሆን ቼዘን (CESEN) የተባለ የጣያን አማካሪ መሃንዲስ ቡድን ሲሆን የሃገሪቱን ጠቅላላ የሃይል ፍላጎትና አቅርቦት አጥንቶ ነበር፤ ይህም ጥናት እነዚህን አራት የአባይ ግድቦች በጥናቱ አካቶ ነበር።
ሶስተኛው ጥናት ደግሞ በ1990ዎቹ መጨረሻ ላይ የተጠናው የአባይ ተፋሰስ የተቀናጀ የማስተር ፕላን ዝግጅት ነው።
(በነገራችን ላይ ይህን የፕሮጀክት ጥናት ለመስራት በመጀመሪያ አሸናፊ የነበረው የሻውል ኮንሰልት ከውጭ ካሉ ድርጅቶች ጋር ነበር፤ ሻውል ኮንሰልት የኢንጅነር ሃይሉ ድርጅት ነው። ጨረታውን አሸንፈው ለፊርማ መለስ ዜናዊ ጋ ሲቀርብ ጠላቶቻችንን ራሳችን ነን ፋይናንስ የምናደርጋቸው ብሎ በመበሳጨቱና ውሉ እንዲሰረዝ ከመደረጉም በላይ በመንግሰት ወጪ በሚሸፈኑ ፕሮጀክቶች ላይ አገር ውስጥ ያሉአማካሪ መሃንዲስ ድርጅቶች (ኢትዮጵያውያንያቋቋሟቸው ድርጅቶች) በሙሉ ጫረታ ላይ እንዳይሳተፉ ታገዱ: ኢንጅነር ሃይሉ በወቅቱ የመ ኢ አ ድ ምክትል ፕሬዚዳንት ስለነበሩ ነው ጠላቶቻችንን ያለው መለስ ዜናዊ:: ኢንጅነር ሃይሉም በዚህ የተነሳ ከመ ኢ አ ድ ምክትል ፕሬዚዳንትነትም አባልነትም ለቀው፤ አገሪቷንም ለቀው ወጥተው።)
ከዚያም ሌላ ጫረታ ተካሂዶ (BCOEM, French Engineering Consultants) የሚባል የፈረንሳይ ኩባንያ ጨረታውን አሸንፎ ጥናቱን አከናውኗል። ይህም ጥናት አነዚህኑ አራት ግድቦች ያካተተ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ የልማት አማራጮችንም የካተተ ነበር።
1.2 የአባይ ተፋሰስና የደለል ችግር
አባይ ወንዝ በተለይ ከጎጃም፤ ከወሎና ከሸዋ የሚመጡ ገባሮች (እንደ በሽሎ፤ ጀማ፤ ሙገር ጉደር) የመሳሰሉት ከተራቆተው መሬት አፈሩን ጠርገው ስለሚመጡ ከፍተኛ ደለል ይሸከማሉ። አባይ በአማካኝ በአመት ከ140-150 ሚሊየን ቶን ደለል ተሸክሞ ካገርይወጣል፤ ይህም ደለል ለሱዳንና ግብጽ ከፍተኛ ራስ ምታት እየፈጠረባቸው ነው። ለደለል መጥረጊያ ብቻ በአመት በአማካይ $200,000,000 ሁለት መቶ ሚሊየን ዶላር ያወጣሉ።
1.3 ጥናቶቹ የደረሱበት ግኝትና የልማት እቅድ
አባይ እጅግ ከፍተኛ የሃይል ማመንጨት አቅም ያለው ተፋስስ መሆኑን ሁሉም ጥናቶች ይስማሙበታል፡ የአባይ ተፋሰስ ጥናት ላይ የተመሰረተ፤ ህዝብን ያሳተፈ፤ ባለሙያዎችን ያካተተ እቅድና ልማት ቢካሄድበት ኢትዮጵያን በሙሉ በሃይል አቅርቦትና ከአንዲ ሚሊየን በላይ የመስኖ ልማት በስርኣቱ ቢለማ ለሃገሪቱ የምግብ አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ድርሻ እንደሚኖረው ይታመናል: ግንባታው ግን በሚከተሉት ቀደም ተከተል መሆን እንዳለበት ሙያዊ ምክራቸውን አቅርበዋል::
በቅድሚያ አባይ ከፍተኛ ደለል ተሸካሚ ስለሆነ ይህ ደለል ደግሞ ለግድብ መሙላትና አካባቢ ብክለት ስለሚዳርግ መጀመሪያ በጣም ሊተኮርበት የሚገባው ተግባር ተፋሰሱን ማጎልበትና በጎርፍ የመሬት መሸርሸርን መቆጣጠር ነው። እነዚህም ተግባራት የእርከን ስራዎችን፤ የተራቆቱ መሬቶችን በደን መልሶ መሸፈንን፤ በጣም አስጊ የሆኑትን እንሰሳትና ምንጣሮ እንዳይካሄድባቸው መከለልን ያካትታል።
ግድቦቹ መሰራት ያለባቸው በምዕራፍ (phase) ሲሆን ግንባታውም ከላይ ወደታች መኬድ እንዳለበት (upstream to downstream) ነው፡ ለዚህም በቂ ምክንያት አለ፤ 1ኛ፤ የግድቡ ወጪ ቀለል ያለ ይሆናል፤ ሁለተኛ ከላይ ሲቆፈር የተቆፈረው አፈር ወደ ግድብ የመግባት እድል ስለሌለው ለግድብ መሙላት አሰተዋጽኦ አይኖረውም፤ 3ኛ፤ የኤሌክትሪክ ሃይል ካመረተ በሗላ መስኖ የማልማት እድል ይኖረዋል፡ በዚህ መሰረት ቅድሚያ የሚሰጠው የካራዶቢ (Karadobi) ግድብ ሲሆን በቀጣይ ማብል (Mabil) ማንደያ (Mandaia) በመጨረሻም የግርጌ (Border) ግድብ ናቸው፡ እንዚህ ግንባታዎች አቅም እየተገነባ ቀስ በቀስ የሚገነቡ ሲሆን ተፋሰሱ ላይ ደግሞ ከፍተኛና ተከታታይ ስራ መሰራት እንዳለ ሆኖ ነው። ይህ አሰራር አንድን ውሃ በቅብብሎሽ አራት ቦታ ላይ ሃይል ማመንጨት ሰለሚያስችል ከፍተኛ የሃይል ማመንጨት አቅም ከማስገኘቱም በላይ ግንባታውም አቅምን ያገናዘበና የተጠና ይሆናል። በተጨማሪ አባይ ተፋስሰስ ውስጥ ከአንድ ሚሊየን ሄክታር በላይ የሚሆን ለመስኖ ተስማሚ የሆነ መሬት ስላለ፡ የነዚህ ግድቦች ግንባታ ይህን የመስኖ ልማት እንዲያካትት ሆኖ መሰራት እንዳለበት ጥናቶቹ ይመክራሉ።
1.4 የህወሃት የተቃርኖ ተግባር
ኢትዮጵያ ውስጥ የውሃ ሃብት ጥናትን፤ ዲዛይንን፤ ቁጥጥርን በተመለከተ በባለቤትነት የሚመራው የውሃ ሃብት ሚንሰቴር ነው፡ አባይን እንገድባለን የሚባለውን ቃል የሚንስቴር መስሪያ ቤቱ መሃንዲሶች የሰሙት ግን እንደማንኛውም ዜጋ አፍሪካ አዳራሽ ለስብሰባ ተጠርተው ከበረከት ስምዖን አፍ ነው። በወቅቱ ከድንጋጤ የተነሳ ምን መናገር፤ ምን ማለት እንዳለባቸው አንኳ ማስብ በማይችሉበት ደረጃ ተገርመው እንደነበር ይታወቃል።
የግድብ ስራው በጥናቱ እንደተመከረው ከላይ ወደታች እየተሰሩ መሄድ ሲገባቸው የመለስ ግድብ ግን የጀመረው ሱዳንና ኢትዮጵያ ድንበር አቅራቢያ ነው። እንደዚህ አይነት ከሜዳ የተነሳ ግንባታን ለስማቸው የሚጨነቁና በሙያቸው የሚኮሩ የግንባታ ተቋማት በምንም መልኩ ተሳታፊ አይሆኑም ለዚህም ለስሙ ብዙም ለማይጨነቀውና ቀድሞም የጎደፈ ስም ላለው ሳሊኒ (SALINI CONSTRUCTION S.P.A.) ያለምንም ጫረታ የተሰጠውም በዚሁ ምክንያት እንደሆነ መጠራጠር አይቻልም።
1.5 ይህ ግድብ ኢትዮጵያ ላይ የሚያስከትለው መዘዝ
ግድብ ከታች ተሰርቶ ከላይ ቁፋሮ ማድረግ ስለማይቻል ከላይ ያሉት ሶሰቱ ግድቦች ካሁን በሗላ ለግንባታ የሚታሰቡ አይሆኑም፤ እነሱ እስካልተገደቡ ድረስ ደግሞ አንድ ጥማድ ማሳ እንኳ በመስኖ ለማልማት አይቻልም፡ ስለዚህ ከሶሶቱ የሚገኘውን ሃይልና ከሚሊየን በላይ የሆነ የመስኖ ልማት ያሳጣናል ማለት ነው።
ከላይ እንደተጠቀሰው አባይ ከፍተኛ ደለል ተሸካሚ ስለሆነና በተፋሰሱ ላይ ምንም ተግባር ያልተከናወነ በመሆኑ የተሰራው ግድብ ሃይል ከማመንጨት ይልቅ የደለል ማከማቻ ይሆናል ማለት ነው: ከዚህ የተነሳ ግብጽና ሱዳን ከደለል ነጻ የሆነ ውሃ ስለሚያገኙ በያመቱ ለደለል ጠረጋ ያጠፉ የነበረው $200 ሚሊየን ዶለላር በቀላሉ ያተርፋሉ።
በሌላ በኩል ደግሞ ኢትዮጵያ ለመስኖ ውሃ አንድ ባሊ ውሃ እንኳን መጠቀም የማትችልበት ሁኔታ ስለሆነ የአባይን ውሃ ሙሉ ለሙሉ ይቆጣጠሩታል፡ እኛ ኢትዮጵያውን አባይ ወንዝ ላይ ያለን የባለቤትነት መብት እናጣለን የሃገሪቷም ሉዓላዊነት ጥያቄ ውስጥ ይገባል ማለት ነው: ግድቡ ሲጀመር ግብጽም ሆኑ ሱዳን ለይስሙላና ተቃውመዋል ተብሎ ኢትዮጵያውያንን ለማታለል ብቻ እንጂ ጫን ያለ ተቃውሞ ያላሳዩትም ይህንን ጥቅማቸውን ጠንቅቀው ያውቁ ስለነበረ ነው።
እዚህ ላይ ሳይጠቀስ መታለፍ የለለበት መለስ ዜናዊ ገና ስልጣን እንደያዘ ወንበሩ ላይ እንኳ ገና ተስተካክሎ ሳይቀመጥ፤ በሽግግር ላይ እያለ ነበር ካይሮ ድረስ ሄዶ ከግብጽ ጋር መፈራረሙን ነው። ያ ውል የተዘጋጀው በሁለት ቋንቋ ሲሆን በአረብኛና በእንግሊዛኛ ነበር፡ አረብኛ የግብጽ ብሄራዊ ቋንቋ ሲሆን እንግሊዘኛ ምን እንደሆነ መለስና ህወሃቶች ናቸው።
ስምምነቱም ለግብጽ ታዛዥነትን ያመለከተ ከመሆኑ ባሻገር ለ ኢትዮጵያ ታላቅ ኪሳራ ያስከተለ ነበር፤ ያንን ፊርማ ተከትሎ ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ በወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ላይ የነበራትን ፍጹም የግዛት ሉዓላዊነት አቋም ለውጦ ምንነቱ እንኳ በውል መተርጎም ያልተቻለበትን (equitable utilization and non appreciable harm) ነው የምንከተለው ተባለ። ግብጽ ግንጥንት ጀምሮ ስትከተል የነበረውን ኣቋም ቅንጣት አልቀየረችም: አሁንም አልቀየረችም።
የህወሃት ባለስልጣናት ግድቡ የታቀደው የሰሜን አፍሪቃን ህዝባዊ አመጽ ትኩረት እንዳይስብ የኢትዮጵያን ህዝብ ትኩረት አቅጣጫ ለማስቀየር እንጂ ታስቦበትና ታቅዶ የተጀመረ አለመሆኑን ቢያውቁም ከህዝብ የሚሰበሰበው ገንዘብ ደግሞ የኤፈርትንና የህወሃት ባለስልጣናትን ኪስ እያደለበ በመሆኑ ሊያስቆሙት አልፈለጉም: የሚያመጣውም ጣጣ አልታያቸውም እንዳውም ይባስ ብለው ሌላ ውል እየተዋዋልን ነው አሉን።
1.6 ግድቡ ለግብጽና ለሱዳን ጠቃሚ ከሆነ ያሁኑ ስምምነት ፊርማ ለምን መጣ?
ከላይ ከላይ የሚታየው ስምምነቱን በፓርላሜንት አስጸድቀው ህጋዊ እውቅና ያገኘ ሰነድ በእጃቸው ለመጨበጥና ወደፊት ለሚነስ የይገባኛል ጥያቄዎች ማስረጃ ለመያዝ መስሎ ሊታይ ይችላል፡ ህጋዊ ሆነም አልሆነ አሁን ያለው ግድብ በዚሁ ካለቀ ሁሌም አገልግሎቱ ለግርጌ ተፋስስ ሃገሮች ሲሆን ኢትዮጵያ ግን ባዶ እጇን አጨብጭባ ዜጎችም በጉልበት ገንዘባቸው ከመበዝበዝ ያለፈ ጠብ የሚል ነገር አለመኖሩን በርግጠኝነት መናገር እችላለሁ።
ይህ ከላይ የተጠቀሰው ውጫዊና ማስመሰያ ሲሆን ዋናው አላማ ግን፡ ግድቡ እንደተባለው ለተቃውሞ ማስተንፈሻ፤ አቅጣጫ ማስቀየሪያ እንጂ ለእውነተኛ ልማት የታቀደ ባለመሆኑ መካተት ያለባቸው ጥናቶች አልተካተቱም፤ የአባይ የውሃ መቋጠሪያ ውሃው የሚጠራቀምበት፤ ሃይቅ የሚፈጥርበት ሸለቆ (Reservoir area) እሳተገሞራ ወለድ አለት በመሆኑ (volcanic rock) ስለሆነ ስንጥቅጥቅና ስብርባሪ (fractures and fissures) ይበዛበታል፡ ውሃ በነዚህ ስንጥቆች ውስጥ በቀላሉ ሊሰርግ ይችላል፡ ውሃ ሰርጎ ከገባ ደግሞ አለቱን የመፈንቀል፤ አፈሩን የመሸርሸር ከፍተኛ አቅም (uplift/pore pressure and piping) ስላለው ግድቡን እስከማፍረስ ሊደርስ ይችላል፤ ግብጽና ሱዳን ይህንን ጠንቅቀው ያውቁታል፡ ግድቡ ሲፈርስ ሊደርስባቸው የሚችለውን አደጋ ያሰሉታል: ስለሆነም ዋሰትና ይፈልጋሉ፤ እነሱ ከአባይ ጥቅሙን እንጂ ጉዳቱን መጋራት አይፈልጉም። አጋጣሚ ሆኖ ግድቡ ቢፈርስና ጉዳት ቢደርስባቸው ካሳ ይፈልጋሉ ለዚህም ነው የካሳን ነገር ስምምነቱ ውስጥ የሸነቀሩት። ህወሃት ደግሞ ዛሬን ስልጣን ላይ አድሮ መገኘቱን እንጀ ነገ የሚመጣውን ማሰብም ሆነ ማቀድ አይፈልግም፤ አቅሙም ፍላጎቱም የለውም። የተፈራው ደርሶ ግድቡ ቢናድና ሱዳንና ግበጽ ላይ አደጋ ቢደርስ ኢትዮጵያ የምትከፍለው ካሳ ምን ያህል ነው? ካሳውስ ከየት ነው የሚሰበሰበው? ያው ከህዝብ አደል?
1.7 አሁን ከህዝብ ምን ይጠበቃል?
ይህ ቀላል ጉዳይ አደለም፤ ለእለት ስልጣን ተብሎ የትውልድ ዘላቂ የተፈጥሮ ሃብትና የሃገር ሉዓላዊነትን አሳልፎ መስጠት ቀልድ አይደለም፤ እንኳን ሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ቀርቶ የህወሃት አባላትና ባለስልጣናት በእጅጉ ሊያስቡበት የሚገባ ጉዳይ ነው። ሃገሪቷን ምን አይነት ውስብስብ ችግር ውስጥ ሊከቷት እንደሆነ ሊገነዘቡ ይገባል።
ከዚሁ ጋር ለግድቡ ግንባታ እርዳታ አደረግን፤ ቦንድ ገዛን የምትሉ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ልማትን እየደገፋችሁ ሳይሆን የሃገርን ሉዓላዊነት አደጋ ላይ እየጣላችሁ፤ ለትውልድ መተላለፍ ያለበትን የተፈጥሮ ሃብት ለባዕድ ሃገር አሳልፋችሁ እየሰጣችሁ መሆኑን ልትገነዘቡ ይገባል፤ ሃገሪቷ ለሚደርስባት ማንኛውም ውድቀት ተሳታፊ መሆናችሁን መገንዘብ አለባችሁ።
ለዘለቄታው የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፎ ላለመስጠትና ሉዓላዊነቷን አደጋ ላይ ላለመጣል ግድቡ ለወፊት ሊቀጥል በሚቻልበት ደረጃ ተዘጋጅቶ መቆም አለበት (The construction of the dam should be halted right away with a condition to resume when the time is right.) ግንባታው አሁን ባለበት ቆሞ፤ ህዝብንና ባለሙያዎችን ያሳተፈ ጥናትና እቅድ ተይዞለት ለሃይል ማመንጫ ብቻ ሳይሆን የውሃ ሃብቱንም ለመስኖ መጠቀም በሚቻልበት መንገድ መሰራተ አለበት። ግንባታው ከጠረፍ ሳይሆን ከካራዶቢ (KIaradobi) መጀመር አለበት። ይህን ስል ለግድቡ እስካሁን የወጣውን ወጭ ግምት ውስጥ ማስገባት ተስኖኝ አደለም ግን ሃገርንና የተፈጥሮ ሃብትን ጨርሶ ከማጣትና ተተኪ ትውልድን ድህነትና ውርደትን ከማስረከብ እዚሁ ላይ ቢቆም ይበጃል ከሚል ግንዛቤ ነው።
እኔ የታየኝን፤ ያማውቀውን፤ የማምንበትን፤ የሚያስጨንቀኝን እንደ አንድ ዜጋ መልዕክቴን አስተላልፌያለሁ። እያንዳንዱ የዜግነት ድርሻውን ይወጣ፤ በተለይ ለዚህ ግድብ ግንባታ ቦንድ የምትገዙ፤ እርዳታ የምትሰጡ፤ አባይ አባይ እያላችሁ የምትጮሁ አርቲስቶች ሃቁን ተረድታችሁ የህሊናችሁን እንድታደርጉ ጥሪዬን አቀርባለሁ።
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይጠብቅ
እስከ ነጻነት

ከኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ ንቅናቄ ለኢትዮጵያ ወጣቶች የተላለፈ ማሳሰቢያ!!!

March 2,2015
ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሚገነዘበው በጥቂት ጠባብ አምባገነኖች የሚመራው የህወሓት/ኢ ህአዴግ ሥርዓት ላለፉት 23 አመታት በህዝብ መካከል የጥላቻና የጥርጣሬ መርዙን እየረጨ፤ ለዘመናት ተፋቅሮና ተከባብሮ የኖረውን ጠንካራ ህዝብ በተለያዩ ጐራዎች በመከፋፈል፤ እምቅ ጉልበቱን በማዳከም፤ ብሎም ትውልድ የማምከን ሰይጣናዊ አላማውን ለማሳካት ነጥሎ በማጥቃት፤ በሃገርና በህዝብ ላይ እጅግ ዘግናኝ ጭካኔዎችንና በደሎችን አየፈፀመና፣ ለከፍተኛ ስቃይና መከራ እየዳረገ እንደሚገኝ ይታወቃል። ይህ አርቆ ማየት የተሳነው ሥርዓት በተለይ ወጣቱ ትውልድ በራስ የመተማመንና አርቆ የማሰብ እምቅ ችሎታው እንዲዳከምና ባክኖ እንዲቀር፤ ብሄራዊ ስሜቱ ጨርሶ እንዲጠፋና ከግለኝነትና ከጐጠኝነት የማያልፍ ጠባብ አስተሳሰብ ውስጥ ሰጥሞ እንዲቀር፤ ብሎም ትውልድን የማምከንና ሃገር የማጥፋት እኩይ አላማውን ለማሳካት፤ በትምህርት ካሪኩለሙ ላይ ሳይቀር መርዙን ለመርጨት ሌት ከቀን እየኳተነ ይገኛል። በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማህበራዊ ሚዲያዎች አማካኝነት በጥቂት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል እያየን የምንገኘው አላስፈላጊና ዋጋቢስ ንትርክ፤ የሥርአቱ ትውልድን የማምከን እኩይ አላማ መገለጫ ተብሎ የሚገለፅ ቢመስልም፤ እውነታው ግን ሥርአቱ አላማውን ለማሳካት ቀጥሮም ሆነ አሳስቶ፤ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ፤ የተፅዕኖው ሰለባ በማድረግ እየተጠቀመባቸው ባሉ ጥቂት ወጣቶች አማካኝነት የሚካሄዱ መሰሪ ተግባራት ናቸው። ይሁንና ዛሬ ይህ ትዕይንት መረን እየለቀቀ የመጣበት ደረጃ ላይ ይገኛል።
EYNM New Logo
ሃገራችን ኢትዮጵያ ከ85 ያላነሱ ብሄር ብሄረሰቦችና ጐሳዎች የሚኖሩባት፤ የ92 ሚሊዮን ህዝብ መኖሪያ ውብ ሀገር ነች። ኢትዮጵያ ከ3000 ዓመት በላይ ታሪክ ያላት ሀገር ስትሆን፤ በአለም ላይ ከታየና ከተመዘገበ ታሪክ ሁሉ፤ ልዩ በሆነ መልኩ የተለያዩ ጎሳ/ዘር፣ ኃይማኖት፣ እምነት፣ አመለካከት ያላቸው ዜጐች የሚኖሩባት ቢሆንም፤ ለዘመናት ተከባብረው፣ ተቻችለውና፣ ተዋደው፤ በፍቅርና በአንድነት በመኖር እንደምሳሌ የሚጠቀሱና የሚወደሱ ናቸው። ልዩነቶች ኖሮባቸው እንኳን ጠላት በመጣ ጊዜ በኢትዮጵያዊነታቸው አንድ ላይ በጽናት በመቆም፤ ጠላትን አሳፍሮ በመመከትና ድባቅ በመምታት፤ የሀገር ሉዓላዊነትን ጠብቀው፤ ህዝባቸውን ከጠላት ጥቃት ለመከላከል ደማቸውን አፍስሰው አጥንታቸውን አድቅቀው መስዕዋትነትን በመክፈል፤ የምንወዳትና የምንመካባት ኢትዮጵያን በክብር አስረክበውናል።
ይህን ማለት ግን ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋና ሰላማዊ ነበር ማለት አይደለም። እውነታው በተለያዩ ጊዜአት የመጡ ስርዓቶች በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ በደል በመፈፀም የታሪክ አሸራ ጥለው አልፈዋል። እዚህ ጋር ግልፅ ሊሆንልን የሚገባው፤የተፈፀመው በደል በወቅቱ የነበሩት ገዢዎች ተግባር እንጂ፤በሃገራችን ኢትዮጵያ ታሪክ አንድም ጐሳ በምንም ሁኔታ በሌላው ላይ ለማጥቃት ተነስቶ አያውቅም። ይህ ታሪካችን በሃገራችን ኢትዮጵያ ዜጐች በፍቅርና በአንድነት ለዘመናት ተቻችለው ሊቆዩ የቻሉበት ዋንኛ ሚስጢር ከመሆኑም በላይ፤ ልንሸሽገው የማይቻለን፤ለአንድነታችን አይነተኛ ማረጋገጫ የሆነ እውነት ነው።
በመሆኑም በወጣትነታችን የዚህ ትውልድ ፈርጥ መሆናችንን አውቀን፤ አእምሮአችንን አስፍተን ታሪካችንን በጥልቀት በመመርመርና በመረዳት፤ብሎም እውነታውን ለይተን በማገናዘብ፤ በታሪክ የነበሩ ችግሮቻችንን አሶግደን፤ የተሻሉ መፍትሄዎችን በሰከነ ውይይት በማፍለቅ፤ አባቶቻችን በክብርና በአንድነት ያስረከቡንን ታላቅ ሃገር በክብር ለመጪው ትውልድ የማስረከብ ታሪካዊ ግዴታችንን እንድንወጣ ሲል፤ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በአብሮት ጥሪውን እያቀረበ የወያኔ መሳሪያም እንዳይሆን ያሳስባል።
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ

Wednesday, April 1, 2015

የቴድሮስ አድሃኖም ዋና አማካሪ የሃሰት ፕሮፌሰር መሆናቸውን አበበ ገላው አጋለጠ

April 1,2015
አዲስ ቮይስ– የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤትና የሚኒስትሩ ዋና አማካሪ እንዲሁም የፖሊሲ ጥናትና ትንተና የበላይ ሃላፊ የሆኑት “ፕሮፌሰር” መኮንን ሃዲስ የሃሰት ፕሮፌሰር እደሆኑ አዲስ ቮይስ ባካሄደው እረዘም ያለ ምርመራ ማረጋገጥ ችሏል።። ግለሰቡ ለ15 አመታት በፕሮፌሰርነት አገልግየዋለሁ የሚሉት አንድ የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ እንደማያውቃቸው የገለጸ ሲሆን የዶክትሬት ዲግሪ ያገኙበት ተቋምም በአሜሪካ ህግ መወሰኛ ምክር ቤት “የዲፕሎማ ወፍጮ” (diploma mill) ተብሎ የተፈረጀ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።
Mekonnen Haddis
“ፕሮፌሰር” መኮንን ሃዲስ ከኦክቶበር 2010 ጀምሮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋና አማካሪ ሆነው በመንግስት የተሾሙ ሲሆን አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በነበሩ ወቅት ዋና አማካሪያቸው ሆነው ያገለገሉት እኚሁ ግለሰብ በአሁኑ ግዜ የዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ዋና አማካሪ እንዲሁም የፖሊሲ ጥናትና ትንተና ክፍል የበላይ ሃላፈ ሆነው በመስራት ላይ ይገኛሉ።
“ፕሮፌሰር” መኮንን ለረጅም አመታት በአሜሪካን አገር ሜሪላንድ ውስጥ የኖሩ ሲሆን በዚሁ ግዛት ውስጥ በሚገኘው ባዊ ስቴት ዩኒቨርሲቲ (Bowie State University) ለ15 አመታት ያህል በፕሮፌሰርነት ማገልገላቸውን በይፋ ሲናገሩ ቆይተዋል። ከዚህም በተጨማሪ በካሊፎርኒያ ፓስፊክ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ በሚል ስም ይንቀሳቀስ ከነበረ ተቋም የዶክትሬት ዲግሪ ማገኘታቸውን በተለያየ ግዚያት ሲገልጹ የነበረ ቢሆንም ዩኒቨሲቲው ዲግሪ ያለ ምንም ትምህርት እንደሚሸጥ በአሜሪካ ሴነት ትእዛዝ በተካሄደ ስምንት ወራት በፈጀ ምርመራ ከተረጋገጠበትና “የዲፕሎማ ወፍጮ” በሚል ስያሜ ከተፈረጀ በሁዋላ እአአ 2005 መዘጋቱን ለማወቅ ተችሏል። ምርመራው በተጨማሪም ኬኔዲ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ፣ ሃሚልተን ዩኒቨርሲቲ እና ካሊፎርንያ ኮስት ዩኒቨርሲቲዎች ዲግሪ ያለ ትምህርት የሚቸበችቡ ወፍጮ ቤቶች መሆናቸውን ይፋ አድርጎ እንደነበር እጃችን የገቡ መረጃዎች አረጋግጠዋል።
ይሄው በካሊፎኒያ ግዛት ይንቀሳቀስ የነበረውና የተዘጋው ዩኒቨርሲቲ የባችለር ዲግሪ በ $2295፣ የማስተርስ ዲግሪ $2395፣ እንዲሁም የዶክትሬት ዲግሪ 2595 ዶላር ይሸጥ እንደነበር ለህግ መወሰኛው ም/ቤት በልዩ ምርመራ ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር በነበሩት ሮበርት ክሬመር የቀረበው ሪፖርት አረጋግጧል።
ለአስራ አምስት አመታት በፕሮፈሰርነት አገለገልኩት የሚሉት ባዊ ስቴት ዩኒቨርሲቲ የግለሰቡን ፕሮፌሰርነትም ይሁን ቅጥር ጉዳይ እንደማያውቅ ለአዲስ ቮይስ ገልጿል። አዲስ ቮይስ በጉዳዩ ላይ መረጃ ከዩኒቨርሲቲው ለማግኝት በጠየቀው መሰረት የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ከፍተኛ ዳይሬክተር የሆኑት ሼይላ ሆብሰን በሰጡት ምላሽ ዩኒቨሲቲው በአሁኑ ወቅትም ይሁን ቀደም ባሉ አመታት መኮንን ሃዲስ የሚባል የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር እንደማያውቅ አስታውቀዋል።
አዲስ ቮይስ በጉዳዩ ላይ መረጃ ከዩኒቨርሲቲው ለማግኝት በጽሁፍና በስልክ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ከፍተኛ ዳይሬክተር የሆኑት ሼይላ ሆብሰን በሰጡት ምላሽ ዩኒቨሲቲው አሁንም ይሁን ባለፉ አመታት በፕሮፌሰርነት ይሁን በሌላ ደረጃ መቀጠራቸውን የሚያሳይ ምንም መረጃ መግኘት አለመቻሉን በኢሜይል በላኩት ምላሽ አሳውቀዋል። ዳይረክተሯ የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ክፍል ከኮምፒውተር ሰነዶች በተጨማሪ በወረቀት የያዛቸውን የመረጃ ክምችቶች ፈትሸው መኮንን ሃዲስ የሚባል ሰው የፕሮፌሰርነት ሹመትም ይሁን የቅጥር ማስረጃ ማግኘት አለመቻላቸውን አስረድተዋል።
አዲስ ቮይስ ባቀረበረበው ተጨማሪ የስልክ ጥያቄ መሰረት ፕሮፌሰሩ የተለያዩ ኮርሶችን አስተምርበት ነበር ያሉትን የታሪክና የስነ መንግስት የትምህርት ክፍል ሊቀመንበር የሆኑትን ፕሮፌሰር ሳሚ ሚለርን ዳይሬክተሯ ጠይቀው የተሩዱት መኮንን ሃዲስ አንድ ወይንም ሁለት ሴሜስተር ለሚሆን ግዜ ከረጅም አመታት በፊት በረዳትነት ማስተማራቸውን ብቻ እንደሚያውቁ አረጋግጠውላቸዋል። ዳይሬክተሯ ዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተለያዩ ግዚያት ለአጭር ግዚያት በረዳትነት የሚያስተምር ማንኛውንም ግለሰብ እንደ ዩኒቨርሲቲው ተቀጣሪ እንደማይቆጥር ገልጸዋል። በትምህርት ክፍሉ እንደ ፕሮፌሰር ሚለር ከሰላሳ አመታት በላይ ያገለገሉት ፕሮፌሰር ዊሊያም ሌውስ በበኩላቸው መኮንን በዩኒቨርሲቲው የማስተርስ ዲግሪ ተማሪ እንደነበር አስታውሰው ትምህርቱን ካጠናቀቀ በሁዋላ ለጥቂት ግዚያት ብቻ የተወሰኑ ኮርሶችን በረዳትነት ማስተማሩን አስታውሳለሁ በማለት የመኮንን ሃዲስን ለአስራ አምስት አመታት የዘለቀ የፕሮፌሰርነት አገልግሎት ትክክል አለመሆኑን አረጋግጠዋል።
ፕሮፈሰሩ ለጉዳዩ ምላሽ እንዲሰጡ ያደረግነው ሙከራ ሳይሳካ የቀረ ሲሆን በስራ ላይ መጠመዳቸውን ካስረዱ በሁዋላ “Leave me alone!” በማለት ስልኩን ዘግተዋል። ወደ ኢትዮጵያ በኤክስፐርት ደረጃ ግብረገብ፣ ዴሞክራሲ፣ የግጭት ማስወደድና ተዛማጅ ጉዳዮችን በተመለከተ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና፣ መንግስታዊ ድርጅቶች እየተዘዋወሩ እውቀት ለማካፈል በ2007 ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት መኮንንን ሃዲስ አለም አቀፍ የገጣሚያን ማህበር በአለፉት መቶ አመታት ውስጥ በአለማችን ከተገኘኑ ምርጥ አንድ መቶ ገጣሚዎች አንዱ ነህ ብሎ አክብሮኛል በማለት በይፋ ተናግረው እንደነበር በጋዜጦች ተዘግቦ ነበር። በ ኦክቶበር 2007 የወጣው “ዴይሊ ሞኒተር” ጋዜጣ ፕሮፌሰሩ በበርካታ መቶዎች በሚቆጠሩ ግጥሞቻቸው እንደሚታወቁ መናገራቸውን ከመጥቀስ አልፎ በአለፉት መቶ አመታት ውስጥ ከተከሰቱ ”100 ምርጥ የአለማችን ገጣሚያን አንዱ” በማለት የአለም አቀፍ የገጣሚያን ማህበር የሚባል ድርጅት እንደሰየማቸው ዘግቧል።
ይሁንና ጉዳዩን ለማጣራት ባደረግነው ጥረት በአሁኑ ግዜ የተዘጋው ይህ ድርጅት ሃሰተኛ የሆኑ የግጥም ውድድሮችን በማኪያሄድ አብዛኛውን ተወዳዳሪ በማጭበርበር በርካታ አቤቱታ ቀርቦበት የነበረ ሲሆነ ድርጅቱም ሌላ የንግድ ተቋም መሸጡ ታውቋል።
—-
ጥቆማና ጠቃሚ መረጃ ለመላክ ይህን ኢሜይል ይጠቀሙ editor@addisvoice.com

ተያያዥ መረጃዎች
Related links
Professor Mekonnen Haddis: Chief Advisor of the Ministry (MoFA biography)
http://www.mfa.gov.et/abtMnstrMore.php?pg=20
Biography: Screenshot
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/bio.png
Ethiopia: Media Behavior During Election 2005 ‘Shameful’ U.S. Scholar (Copy)
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/All-africa-monitor.pdf
Report on Degree Mills, U.S. Senate, Robert J. Cramer, Director Office of Special Investigations
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/Pacific-Western-Univesity.pdf
The Contester: Poetry.com Struggles for Legitimacy
http://www.pw.org/content/contester_poetrycom_struggles_legitimacy
Political Snapshots (Mekonnen Haddis’ blog)
http://addisvoice.com/wp-content/uploads/2015/03/Mekonnen-Haddis-Blog-screenshot.pdf

Tuesday, March 31, 2015

በየመን ኢትዮጵያውያኖች በጭንቅ ላይ ናቸው

March 31,2015

ግሩም ተ/ሀይማኖት (ከየመን)
ISIS_organsረቡዕ ሌሊት 8፡30 ላይ የተጀመረው የአየር ድብደባ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ የመን ነዋሪ የሆነ ሁሉ በፍርሃት ርዷል፡፡ በተለይ በትላንትናው ሌሊት የነበረው የአየር ድብደባ ከፍተኛ ስለሆነ ህዝቡ ላይ የጣለው ፍርሃት ከወትሮው የተለየ ነው፡፡ “በሁቲይን አማጽያን ሚሊሻ ላይ የተጀመረው የአየርጥቃት አሁንም በድርድሩ ካልተስማሙ ወይ ሰነዓ ከተማን ለቀው እስካወጡ አያቆምም!” ሲሉ የሳዑዲ አረቢያ ንጉስ ሰልማን ቢን አብድልአዚዝ ገልጸዋል፡፡ ይህን አባባላቸውን ተከትሎ እግረኛ ሰራዊትም ሊንቀሳቀስ መሆኑ እየተገለጸ ነው፡፡ 20.000 እግረኛ ወታደር ተዘጋጅቶ ድንበር ላይ መሆኑን የየመን መገናኛ ብዙሀን እየዘገቡ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ተጀምሮ የነበረውን ድርድር እንዲቀበሉ ለሁቲይን አማጺዎች ከትላንት ወዲያ የ3 ቀን እድሜ ቢሰጣቸውም አልተቀበሉትም፡፡

በሳዑዲ ሰብሳቢነት የአረብ ሊግ ሀገራት መንግስታት በየመን ጉዳይ ለመመከር ግብጽ ሻርማ ሸኸ ተሰብስበው ነው ያሉት። በዚህ ስብሰባ ላይ የአየር ጥቃቱ የዘመቻ መሪ ሀገር የሳዑዲ አረቢ ንጉስ ሰልማን ሀቲይን የተባሉት አማጽያን ለቀው እስኪወጡና የመን እስክትረጋጋ ድረስ የተጀመረው ጥቃት ቀጣይ እንደሆነ ገልጸዋል በማለት የየመኑ ቶውራ ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይ የየመኑ መሪ አብድረቡ መንሱር ሀዴ ተገኝተዋል፡፡ ህዝቡ ግን ሀገራችንን እያስደበደበ ያለው ፕሬዘዳንታችን ነው በማለት ጥስ እየነከሰባቸው ነው፡፡ የቀድሞው ፕሬዘዳንት አሊ አብደላ ሳላ ድርድሩን እንደሚቀበሉ ቢገልጹም ተቀባይነት ያገኙ አይመስልም፡፡

ዛሬ ሌሊት በሳውዲ የተመራው የአስሩ ሀገራት ህብረት ጦር በሰንዓ ፈጂ አጣን የተባለው ቦታ ጋራ ላይ የሚገኘው ወታደራዊ ካምፕ ውስጥ ያለ የብላስቲክ ሚሳየል ክምችት ማውደሙ ታውቋል፡፡ ይህ የመሳሪያ ክምችት በተመታበት ወቅት መላ ከተማው የተርገደገደበት የመሬት መንቀጥቀጥ አይነት ሁኔታ ነበር፡፡ አንዳንድ ህንጻዎች መስታዎታቸው ሁሉ ርግፏል፡፡ ነዋሪው ሲነጋ እንቅልፍ አጥቶ መደሩ ዋነኛው ርዕስ ነበር፡፡ በተለይ ስደተኛ ኢትዮጵያዊን ከፍተኛ ፍርሃት ተውጠን እንዳለን በርካታ ያናገርኳቸው ወገኖቼ ገልጸውልኛል፡፡ በእርግጥ ሌላውስ ወገን የመን ያሉ ኢትዮጵያዊያንን እንዴት እያሰባቸው ይሆን?

የተመታው ካምፕ ላይ የሚቃጠለው መሳሪያ ፍንዳታም ከፍተኛ ነበር፡፡ ከሌሊቱ 8፡20 ጀምሮ ጠዋት ድረስ እሳቱን ለማጥፋት ርብርብ ነበር፡፡ የሁቲይን አማጺያን ድብደባውን በዝምታ እያዩት አይደለም፡፡ ከየአቅጣጫው በአየር መቃወሚያ ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ 
እንደ አባባላቸው ከሆነ የአየር ጥቃቱን ከሚያደርሱት ጀቶች እስካሁን ሁለት መምታታቸውን ተናግረዋል፡፡ በዛሬው ሌሊት ሰነዓ ላይ ድብደባው ቀነስ ቢልም ሁዴዳና ሌሎች ደቡባዊ የመን ላይ ጠንከር ያለ እንደነበር መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ሁቲይኖቹም ከየአቅጣጫው የሚደረገውን ጥቃት ለመከላከል ሙከራቸው በዛሬው ሌሊት ቀንሶ ታይቷል፡፡ ሰነዓ ያለ ኢትዮጵያዊ በጭንቅ ውስጥ ሲሆን አደን የተባለው ሁለተኛ ከተማ ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያዊን በከፍተኛ ሁኔታ እያነቡ ነው፡፡

Monday, March 30, 2015

መለሰ ዜናዊ ናፈቁኝ – የለቅሶ አየር ሰዓት አማረኝ

March30,2015

meles funeral3

ሰላም ወገኖቼ!! ተጠፋፋን። ግን አንለያይም። ድሮ የዘፈን ምርጫ ክፍለ ጊዜ ነበር። እሁድ እሁድ ወታደሮች ከደጀን፣ እናትና አባት፣ ቤተሰብ ከቤት ሆነው ይኮሞክሙት ነበር። አሁን ግን ለምን ተከለከለ? ባድመ፣ ሽራሮ፣ ዛላምበሳ፣ ገመሃሎ፣ ላከ ኤርትራም አሉ፤ ዘላበድኩ መሰለኝ … ብቻ የዘፈን ምርጫ ክፍለ ጊዜው ትዝ ብሎኝ ነው። ቀጭኑ ዘ-ቄራ ነኝ!!
“የለቅሶ ማስተላለፊያ የአየር ሰዓት/ክፍለ ጊዜ ቢጀመር ጥሩ ነው። ምርጫውን ያደምቀዋል” የሚል አስተያየት ሟርተኞች ያቀርባሉ። ግን ምን አለበት የከፋቸው ቢያለቅሱ። በየጓዳው እያለቀሱ ነው። አደባባይ ወጥተው ቢያለቅሱ ምን ነውር አለው? ለመለስ ደረት እየተመታ ሲለቀስ የአየር ሰዓት ተፈቅዶ የለ? ለሞተ ሰው ከተፈቀደ በህይወት ላለው፣ ግብር ለማያጓድለው ለምን ይከለካል? ወይስ ነዋሪው በሟች ተበልጧል?
ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲባል የመለስ ለቅሶ በጊነስ ቡክ አለመመዝገቡ አያስገርምም። አማራ ደረት ሲደቃ፣ ደቡብ በዜማ ሲናባ፣ ትግሬ በለቅሶ ሲያዜም፣ ኦሮሞ እንባውን “ያ አባ ኮ” እያለ ሲያንዘቀዥቅ፣ ማን ቀረ? ሃይሌ ገ/ስላሴ ሲቃ ይዞት የእንባ “ቫት” ሲገብር … ድፍን አገር ሃዘን ሰብሮት፣ መሪው በድንገት እንደ ቡሽ ተስፈንጥረው ሲሄዱበት፣ ራዕያቸው ሲተንበት፣ ህልማቸው እንደ ጉም በድንገት ሲበተነበት፣ ጉሮሮው በድንገት ሲዘጋበት፣ ኑሮ ወደ ጎዳና ተዳዳሪነት ሲለወጥ፣ “የመጪው ጊዜ ብሩህነት” ሲደበዝዝ፣ እንዴት አያነባ? ጎበዝ ለመለሰ ዜናዊ ማን ያላነባ አለ?
መለስ አማረረን ብለው የተሰደዱ፣ በስደት ካምፕ የመለስን ፎቶ ሰቅለው ለቅሶ ተቀምጠዋል። ጠጅ ቤት፣ ጫት ቤት፣ … ምርጫ ሲመጣ ቀጭኑን ያመዋል። ምርጫ የግል ነው። የምርጫ ሰሞን ወሬ ለቃሚዎች ሲሳይ ይሆንላቸዋል። እገሌ ይህን አለ እያሉ በጀት ያስጨምራሉ። ወሬ ለመልቀም ይከንፋሉ። በየጫት ቤቱ ይራወጣሉ። ተናግሮ ማናገርና መልቀም። ጓደኞቻቸውን ማስበላት። አሳልፎ መስጠት። በህወሃት የባህር መዝገብ ማስመዝገብ።
OLYMPUS DIGITAL CAMERAአቶ መለስ አፈር አይክበዳቸውና (ለነገሩ አፈር ውስጥ አልገቡም) 99.6 በመቶ ምርጫን በማሸነፍ “ታሪክ መሰራቱን” ሲያበስሩ 96 በመቶ እንዲያሸንፉ ያደረጓቸው ወዳጆቻቸው ፊት ሰክረው ነበር። አራዳው መለስ በደስታ ቢሰክሩም መስታወት ቤት ውስጥ ሆነው መናገርን ግን አይረሱትም። ደስታ እየደቃቸው መስታዋት ቤት ውስጥ ሆነው “ኮራሁባችሁ” ሲሉ ከሲኤምሲ በ200 አውቶቡሶች ተጭነው መስቀል አደባባይ የደረሱ የኮብል ድንጋይ አንጣፊዎች አጨበጨቡ። በፉጨት አስተጋቡ። መለስ ደስታቸውን ሳያጣጥሙ ሾለኩ … ከመስታወት ቤት ወደ ግራውንድ ሲቀነስ ወረዱ። እዛ ወከባ የለም። ጭብጨባና ፉጨት የለም። ራዕይ፣ ቅዠት፣ “ሌጋሲ”፣ አብዮታዊ ዲሞክራሲ፣ ህዳሴ፣ ኪራይ ሰብሳቢ፣ ኒዎሊበራል፣ ምናምን የለም። የዘላለም እረፍት … ቀጭኑ እንባ ባይረጭም ሃዘን ገባው።
የዜናዊ ልጅ ምነው ሞትን ሞተው በነበር? ቀጭኑ ጠየቀ። ሞት ያለ ሳይመስላቸው እንዲሁ በትዕቢት ማማ ላይ እንዳሉ ኮበለሉ። ቢያንስ ህዝብ የመምረጥና የመሻር ወሳኝ ሃይል እንዳለው አይተውና አሳይተው ቢነጉዱ ኖሮ እስከዛሬ ባነባን ነበር – ለነገሩ አይተዋል ማሳየት አቃታቸው እንጂ። ቀጭኑ መለስን የሚወቅሰው በዚህ ነው። ነጻ ትውልድ እንዲፈጠር አድርገው ቢያልፉስ ምን ነበር? የሚገርመው አሁንም ትምህርት የሚወስድ የለም። አዲሱ ጠ/ሚኒስትር ኦቦ ሃይለማርያም ማለቴ ነው። ከ96 ወደ 100 በመቶ ለማሳደግና ሲሞቱ ደቡብ ሱዳን፣ ፑንትላንድ፣ ሩዋንዳና ኡጋንዳ የዘለቀ ሃዘን እንዲታወጅላቸው የሚተጉ ይመስላሉ። ሃይሌ ዕዳቸው ብዙ ነው፤ ለነገሩ የአገር መሪዎች ባለብዙ ዕዳ ናቸው፤ የሃይሌ ግን የበዛ ይመስለኛል፤ የራዕዩ፣ የሕዳሴው፣ የውዳሴው፣ የሌጋሲው፣ … ኧረ ስንቱ?! ራዕያቸውን፣ ሌጋሲያቸውን፣ … ተግባራዊ እናደርጋለን፤ እያሉ ስለ መለስ እንደሚናገሩት አንድ ቀን “ሞታቸውንም ተግባራዊ እናደርገዋለን” ብለው ንግግር ቢያደርጉስ? ለነገሩ ምን ይተገበራል? ለመሆኑ ስንቶቻችን ነን ህያዋን የሆንን? ወደ ጉዳዬ ልመለስ …meles in box1
“እኒህ ፖለቲከኞች ነፍስ የላቸውም እንዴ” ስትል ማይሟ እናቴ ሁሌም ትጠይቃለች። ደግ ስራ ሰርቶና ተወድዶ መሞት ለምን እንደማይወዱ አይገባትም። ለመለስ ለቅሶ አልሄደችም። ለዚህ ነው መሰል የቀበሌው ሊቀመንበር አሁን ድረስ ይገላምጣታል። በነገራችን ላይ ያንዱ ቀበሌ ሊቀመንበር ባልደረባዬ ነበር። የመለስን ለቅሶ ቀበሌ ድንኳን አስተክሎ ሲያከናውን ወደ ጓሮ እየጠራሁ ጫት አጎርሰው ነበር። ድንገት ስናወራ “ለመለስ ለቅሶ ከልብህ አላዘንክም፣ መልፈስፈስ አሳይተሃል፣ ቁርጠኝነት አይታይብህም፤ …” ተብሎ መገምገሙንና 40 ሳይደግስ መሰናበቱን ነግሮኛል። አይ ግም-ገማ!!
አሁን ማን ይሙት እነዚያ ጎንደር ላይ አበል ከፍለው ደሃውን ሲያላቅሱትና በግምገማ ደረት ሲያስመቷቸው የነበሩት ሴቶች መለስን ያውቋቸዋል? ጋምቤላ አኙዋክ ምድር ለመለስ የሚያነባ ሰው ይገኛል? ፊልም የሚሰራ ደፋር ጠፋ እንጂ ከዚህ በላይ ምን ፊልም አለ? ኤርትራ ቤተ መንግስት ውስጥ አንድ ክፍል በድብቅ ሃዘን ተካሂዶ ነበር ብሎ የፈተለ ሰው አጋጥሞኛል። የኤርትራ ባንዲራ ዝቅ ስለማለቱ ግን መረጃ የለውም። የስምዖን ልጅ ሲሽቀነጠር እናያዋለን።
ባገራችን ምርጫ ያለ ፈቃድ ማልቀስና ደረት መምታት ነው። ባገራችን ምርጫ የራስ ሳይሆን የሌሎችን ምርጫ ማጽደቅ ነው። ባገራችን ምርጫ የራስን መብት ለሌሎች በህጋዊ ሰነድ ስም ማስረከብ ነው። ምርጫ!! በወሳኝ ጉዳዮች ላይ ምርጫ ብሎ ነገር የለም። አለመስማማት ተፈጥሯዊ ነው። አለመቀበልና አለመስማማት ግላዊ ነው። ልዩነት ያለ፣ የነበረ፣ የሚኖር እውነት ነው። ምርጫ በነዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ይገኛል። ከዚህ ውጪ ያለ የጫና ምርጫ የሰውን ልጅ አሻንጉሊት አድርጎ የማሳነስ ያህል ነው። የሰው ልጅ ክቡር ነው። ምርጫውን ያውቃል። ግን የእኛን አገር አይመለከትም።
ምርጫ በመጣ ቁጥር አየሩ ሁሉ ይከረፋል። ምርጫ በመጣ ቁጥር የህወሃትና ኢህአዴግ እብደት ይገንናል። እነሱ ሰማይና ምድሩን አፍነው የፈጣሪ ያህል የሆኑ ይመስላቸዋል። ቅጠሉና ዛፉ እንኳ አይታመንም። ወይ አንደኛውኑ ምርጫውን ቢዘጉት አይሻልም? ቀጭኑ ይህንን ሃሳብ ያቀርባል። ምርጫ የሚኖረው ምርጫና የመምርጥ መብት ሲከበር ነው። አስመራጩ ባንዳ፣ አስፈጻሚው ባንዳ፣ የበላዩ ባንዳ፣ የበታቹ ተላላኪ፣ መቃወም፣ መተንፈስ፣ ማስተማር፣ መናገር፣ መዝለፍ፣ ማጋለጥ፣ ነጻ ሚዲያ፣ ነጻ የመጫወቻ ሜዳ ሳይኖር ምርጫ? ይቀፍፋል። መቼ እንደምንሰለጥን አይታወቅም። ሁሉም ጋር ችግር አለ። የዜናዊ ልጅ ግን ናፍቀውኛል። መልካም ነገር አስተምረውን አለፉ፣ ተፈተለኩ፣ ተነቀሉ፣ ተደለቱ፣ አሁንም ለሳቸው ማልቀስ የሚፈልጉ አሉ። የማልቀሻ የአየር ሰዓት ይፈቀድ ብለው የሚጠይቁ አሉ። ለመለስ የለቅሶ ምርጫ ክፍለ ጊዜ ይመደብልን። ከየብሔሩ እያፈራረቅን መስማት የምንፈልግ ቧልተኞችም አለን። ቀጭኑ የምርጫ እድል ቢሰጠው “ያ አባ ኮ” በሚል የኦሮሞ አርሶ አደሮች ያነቡበትን ለቅሶ ቀዳሚ ክሊፕ አድርጎ ይመርጠዋል። ከዚያም “ሰለሜ ሰለሜ” የሚለውን በለቅሶኛ ያስከትላል። ቸር እንሰንብት!! ቀጭኑ ዘ-ቄራ!!

Friday, March 27, 2015

የግብፅ እና የኢትዮጵያ የጸጥታ ኃይሎች ተወዛገቡ

March 27,2015

የኢትዮጵያ እና የግብፅ የንግድ የንግድ ማህበረሰብ ልዑካን አባላት ስብሰባ ትላንት በሸራተን አዲስ ሆቴል ሲካሄድ  የሁለቱም ሃገራት የጸጥታ ሠራተኞች ጋዜጠኞችን በማስገባት ባለመስማማታቸው ተወዛገቡ፡፡ 
በግምት ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ገደማ የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የግብጹ ፕሬዚደንት አብዱልፈታህ አልሲሲ በተገኙበት በግምት ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ገደማ የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የግብጹ ፕሬዚደንት አብዱልፈታህ አልሲሲ በተገኙበት የሁለቱ ሀገራት የንግድ ማህበረሰብ አባላት ባሰተፈው ስብሰባ ላይ ለመዘገብ የሄዱ የኢትዮጽያ ጋዜጠኞች በግብጽ የጸጥታ ኃይሎች ገብተው እንዳይዘግቡ የተከለከሉ ሲሆን የኢትዮጽያ የጸጥታ ኃይሎች በተቃራኒው ጋዜጠኞቹ ገብተው እንዲዘግቡ በመወሰናቸው ለጥቂት ደቂቃዎች አለመግባባትና ግርግር ተፈጥሯል፡፡  
ሆኖም ጋዜጠኞቹ እንዲገቡ በመፈቀዱ አለመግባባቱ ረግቧል፡፡
     በዚህ ስብሰባ ላይ የኢትዮጵያ እና ግብፅ የንግድ ግንኙነት በየዓመቱ ለውጥ እያመጣ ቢሆንም አመታዊ የንግድ ልውውጡ መድረስ ይገባል ተብሎ ከተገመተው የአምስት ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር አንፃር ሲታይ ግን ዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተገምግሟል።
     በኢትዮጵያ ለሚሰማሩ የግብፅ ባለሃብቶች ተገቢውን ድጋፍ እንደሚያገኙ ነው ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በውይይቱ ላይ ማረጋገጫ ሰጥተዋል፡፡

     በውይይቱ ላይ የግብፅ ፕሬዝዳን አብዱልፋታህ አል ሲሲ ሃገራቱ በዲፕሎማሲ መስክ እያሳዩት ያለውን ግንኙነት በኢኮኖሚ መስክም እንዲጠናከር ግብፅ ፍላጎቷ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ጉዞአችን ወደ ነፃነት ነው!! መዳረሻችንም የነፃነት አደባባይ ብቻ ነው!!

March 27,2015
pg7-logoአለማችን አንባገነን ስታስተናግድ ወያኔ የመጀመሪያው አይደለም። ዘረኛንም እንዲሁ …….. እኛም ስለነፃነት ብለን ለትግል ሰንነሳ የመጀመሪያዎቹ አይደለንም …… አለማችን እንደየዘመኑና እንደ የወቅቱ አንባገነኖች ያለ የሌለ የመሳሪያና ወታደራዊ ሀይላቸውን በመጠቀም ህዝብን በፍርሀት አሸማቀውና ረግጠው ለመግዛት ሲውተረተሩ በተደጋጋሚ ታይተዋል። በዚያው ልክ ህዝባዊ ሀይልና መመከት ተስኗቸው ሲንኮታኮቱ በተደጋጋሚ የታየ ወደፊትም አናባገነኖች እስከተከሰቱ ድረስ በህዝባዊ ሀይል ተጠራርገው መቀመቅ ሲወርዱ መታየቱ አይቀሬ ነው ። ህዝብ የወደደውን አስተዳዳሪ እንጂ ረግጦ ሊገዛው የሚፈልገውና አንባገነን ተቀብሎ አያውቅም ፤ዛሬም አልተቀበለም ፤ ነገም አይቀበልም ። ይህን በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ በተደጋጋሚና በጉልህ የሚታይ ግዙፍ እውነት መቼም ተቀብለውና ከታሪክ ተምረው ስለማያውቁ አሳፋሪው ውድቀታቸው በተደጋጋሚ ሲታይ አለ።
ሀገራችን የአለማችን አካል እንደመሆኗ አንባገነኖች ተፈራርቀውባታል። አንባገነኖችም በህዝባዊ ሀይል ተጠራርገውባ ታል። ከደቡብ አፍሪካ ቀጥሎ ትልቅ ወታደራዊ ሀይል የነበረው የትናንቱ ደርግ እንደ እንቧይ ካብ ሲናድ ተመልክተናል። አንባገነኖችመናገር እንጂ መስማት የማ ችሉ፤ ማየት እንጂ ማስተዋል የተሳናቸው በመሆናቸው እነሆ ዛሬም የወያኔ ዘረኛው ቡድን ህዝባ ላነሳው የነፃነትና የፍትህ ጥያቄ ያለ የሌለውን ወታደራዊ ሀይል በጠራራ ጸሀይ በማሰለፍ መቼውንም ያልተቻለ ውን ህዝብን በሀይል አሸማቆ ለመግዛት መከራውን ሲያይ ይስተዋላል። ለዚህም ነው ….. ከሌላው የሀገራችን ክልሎች ከፍ ባለ ሁኔታ የህዝባዊ እንቢተኝነት እየታየ ባለበት ጎንደርና አካባቢው በሰራዊት ማጥለቅለቅ የተያያዘው።
ለሚነሱ ህዝባዊ ተቃውሞዎችና ህዝባዊ የመብት ጥያቄዎች የሚሰጡት ምላሾች እስር፤ አፈናና ግድያ ከሆነ ህዝባዊ እንቢተኝነትን ማስከተሉ አይቀሬ ነው። በእስር ፤በአፈናና በግድያ እንዲሁም በሰራዊት ሀይል ህዝብን በማሸማቀቅ በስልጣን መቆየት የሚቻል ቢሆን ደርግም ከቤተ-መንግስት ባልወጣ፤ ወያኔም ዛሬ ከቤተ-መንግስቱ ባልተንፈልለሰ ነበር። ይህ ደግሞ ሊያስተምር በተገባ ነበር።
እስከ ዛሬ የትኛውም አንባገነን ስርአት በሚተማመንበት የወታደራዊ ሀይል አማካይነት የመንኮታኮቻቸውን ሰአት በአንድ ሰኮንድ ማዘግየት የቻለ እንደሌለ ሁሉ ወያኔም ያለ የሌለውን ወታደራዊ ሀይል ሲያርመሰምስ ውሎ ቢያድር ውድ ቀቱን በአንድ ሰኮንድ ማዘግየት እንደማይችል በተለይ እንቢ ለነፃነቴ፤ እንቢ ለሀገሬ… ብለን ለትግል የተነሳን ሀይሎች በመረ ዳት፤ ይበልጡኑ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተቀጣጠለ ያለውን ህዝባዊ እንቢተኝነት ይበልጥ እያሰፋን የጀመርነውን የነፃነት ጉዞ ከነፃነታችን አደባባይ ለማድረስ ሌት ተቀን የመስራት ሀላፊነታችናና መወጣት ይገባናል።
በጎንደር የሚታየውን የአልገዛም ባይነት ትንቅንቅ በሌሎች ክልሎችም በማቀጣጠል፤ በደብረወርቅ የታየውን የመምህራን የስራ ማቆም አድማ ወደ ሌሎች አካባቢዎች በማስፋት፤ እንደ ድምፃችን ይሰማ ሁሉ ተቃውሞን ወደ እንቢተኝነት በማሸጋ ገር …… ወዘተ የነፃነታችንን ቀን ለማቅረብ መከፈል የሚገባውን መክፈል ይገባናል።
በደርግ ል የተነሳው እንቢተኝነት እያየለ ሲመጣ ያሰለፈው ሰራዊት ወያኔን አጅቦ የደርግን ቀብር እንደቆፈረለት ሁሉ ዛሬም በወያኔ ላይ እየተቀጣጠለ የሚገኘው ህዝባዊ እንቢተኝነት እየጠነከረ በመጣ ቁጥር የደረደረው ሰራዊት የወያኔን ቀብር ቆፋሪ ከመሆኑ እንደማኢመለስ ከቅርብ ጊዜ ታሪካችን በመማር ነፃነታችንን ለማስከበር የጀመርነውን የእንቢተኝነት ትግል በ መ ላው የሀገራችን ክፍሎች በማስፋትና በማቀጣጠል አይቀሬውን የወ ኔ ቀብር ለማቅረብ በአንድነት የነፃነት ጉዞውን እንቀ ላቀል። የጀመርነው የነፃነት ጉዞ መቆሚያው የነፃነታችን አደባባይ መሆኑን በተግባር ከምናሳይበት ወቅት ላይ እንገኛለንና በአንድነት እንነሳ!!!!!
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!!

Thursday, March 26, 2015

መንግሥት ለምን ጩኸት ይወዳል?

March 26, 2015
ከኤልያስ ገብሩ ጎዳና
የየትኛውም ሀገር መንግሥት፣ ለሚመራው ህዝብ፣ እየሰራ ስለሚገኛቸው ሥራዎች የማሳወቅ ኃላፊነት እና ግዴታ ስላለበት ይናገራል፡፡ የአገላላጽ ደረጃ እና መጠኑ እንደየመንሥታቶቹ ባህሪ የሚወሰን ነው፡፡ መንግሥታት ሥለሚያከናውኗቸው ሥራዎች ለህዝቡ በግልጽ ዕውነቱን ሊናገሩ እንደሚችሉ ሁሉ፣ ለፖለቲካ ትርፋቸው ሲሉ ቀናንሰው እና ውሸትን አቀላቅለው ሊገልጹም ይችላሉ፡፡Elias Gibru
ይሄም ብቻ አይደለም፣ ከተሰራው በላይ በማጋነን፣ የፕሮፖጋንዳ ሥራን በፈጆታነት ይጠቀማሉ፡፡ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ይሆናል ብዬ የማስበው ገዥው መንግሥት ኢህአዴግ ነው፡፡ መንግሥታችን ትልቅም ሆነ ትንሽ ሥራ ሲሳራ በግንነት መግለጽ አንዱ መለያው ማድረጉን ምርጫው ያደረገ ይመስላል፡፡
ከወራቶች በፊት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በጋዜጠኝነት የሙያ ዘርፍ ተመራቂ ተማሪዎች እኔን እና ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪን ሀሳብን ከመግለጽ ነጻነት አኳያ እንግዳ አድርገው ከተማሪዎች ጋር በጥያቄ እና መልስ አወያይተውን ነበር፡፡ በዚህ ደስ የሚል ፕሮግራም ላይ ልማታዊ ጋዜጠኝነትን በተመለከተ በነበረው ገለጻ ላይ አናንያ የሚያስቅ ነገር ግን ቁም ነገር አዘል አስተያየቱን ሰንዝሮም ነበር፡፡ ‹‹ኢህአዴግ ለአባይ ግድብ ግንባታም ሆነ ሰፈር ውስጥ የቦኖ ውሃ እንዲወጣ አድርጎ ኅብረተሰቡን እኩል ድቤ ያስመታል›› ነበር ያለው አናንያ፡፡ ከዚህ ለመረዳት እንደሚቻለው ለትንሹም ሆነ ለትልቁ ‹‹ልማት›› ጩኸት ከመፈለጉም ባሻገር ውዳሴም መሻቱን ነው፡፡
ካነሳሁት ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ አንድ ምሳሌ ልጥቀስ፡-
ግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም አመሻሽ ላይ የፌዴራል የጸረ ሙስና እና የሥነ-ምግባር ኮሚሽን ከብሔራዊ የመረጃ ደኅንነት ተቋም ጋር በመተባበር የፌዴራል ገቢዎች እና ጉምሩክ ባለሥልጣን መ/ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ እና ምክትላቸው አቶ ገብረህዋድ ገ/ጊዮርጊስን ጨምሮ 13 ሰዎችን በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው መታሰር በአዲስ አበባ እና በሌሎችም የአገሪቱ ከተሞች ሰበር ዜና ሆኖ የመረጃ ቅብብሎሹ በፍጥነት ተዛምቶ ነበር፡፡ በተጨማሪም በሂደት ተጠርጥረው የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ50 በላይ ደረሱ፡፡
ይህንንም እስር ተንተርሶ ጠ/ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ ትልቅ ሥራ እንደሰሩ ተደርጎ ‹‹በርቱ ተበራቱ፣ በዚሁ ቀጥሉበት፣ አሁን ሥራ መስራት ጀመሩ!›› ተብለው ሲመሰገኑ እና ሲወደሱ ነበር፡፡
በዚያ ሰሞን በሀገሪቱ ላይ ትልቅ ተዓምር የተፈጠረ ይመስል፣ የመንግሥት እና የተወሰኑ የግሉ ሚዲያዎች ጉዳዩን ከልክ በላይ ዘገቡት፡፡ የኅብረተሰቡም ዋነኛ የመወያያ ርዕሰ ጉዳይ ይሄ ሆነ፡፡ ነገር ግን፣ ጉዳዩን በሰከነ መንገድ ማስተዋል ቢቻል ጉዳዩ ይን ያህል አስገራሚ አልነበረም፡፡ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የሥራ ኃላፊዎችና ታዋቂ ባለሃብቶች በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥራ መዋላቸውና መከሰሳቸው አይደለም፡፡ ከዚያ ቀደም የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ታምራት ላይኔ እና የመከለከያ ሚኒስትሩ አቶ ስዬ አብርሃም በመሰል ወንጀል ተጠርጥረው ከተከሰሱ በኋላ ተፈርዶባቸው ከእስር ወጥተዋል፡፡ ግን ሥርዓቱ ከእንደዚህ ዓይነት ተጠንተው በታቀዱ ክስተቶች ጩኸትን ይሻል፡፡ ለምን ለሚለው በጽሑፌ መደምደሚያ ላይ እመለስበታለሁ፡፡
የአባይ ግድብን የወሰድን እንደሆነም፣ መሰል ነገር እናስተውላለን፡፡ የአባይን መገደብ የደገፉት ብዙዎች እንዳሉ ሁሉ በምክንያታዊነት የፕሮጀክቱን ዓላማ የሚተቹ ወገኖችም መኖራቸው እሙን ነው፡፡ …የግድቡን ሥራ በቅንነት ካየነው፣ የዐባይ መገደብ አንድ ትልቅ ሀገራዊ የልማት ተግባር አድርጎ መውሰድ ይቻላል፡፡ ሆኖም በዐባይ ግድብ ስም ያለማቋረጥ እየተሰራ ያለው ፕሮፖጋንዳ ቀላል አይደለም፡፡ ስለፕሮጅክቱ ዝርዝር ነገር በመንግሥት ኃላፊዎች፣ በመንግሥት፣ በግሉና በውጭ ሀገራት ሚዲያዎች ለረዥም ጊዜ በተደጋጋሚ ተዘግቧል፡፡ በዚህ መሰረት፣ ሰፊው ሕዝብ ሥለግድቡ ጥሩ ግንዛቤ አግኝቷል ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡ ግን በሳምንት ለሰባት ቀናት እና 24 ሠዓታት ሙሉ በሚያስብል መልኩ ‹‹አባይ …አባይ›› ማለት ግድቡን ለፖለቲካ ፍጆታነት መጠቀም መሆኑን በግልጽ የሚያሳይ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በኩል አባይ በሶስት ብር እንደሚገደብ አድርጎ የተለያዩ ማስታወቂያዎችን እስኪሰለቹ ድረስ ማቅረብም ጩኸትን መሻት አድርጌ እወስደዋለሁ፡፡ እንዲሁም ህዝብ ለግድቡ በግሉ ማድረግ ያለበትን ድጋፍ ከልቡ ፈቀዶ እንጂ በማስታወቂያ ጋጋታ ተሰላችቶ መሆን የለበትም፡፡
ሌላኛው ጩኸት የበዛበት ነገር፣ የህወሃት 40ኛ ዓመት ምስረታ በዓል ነው፡፡ ክብር ለሚገባቸው ታጋዮች ክብር መስጠት ተገቢ ሆኖ ሳላ፣ በዓሉን አስመልክቶ፣ ለረዥም ቀናት፣ እጅግ በተጋነነ መልኩ ጉዳዩን ማስጮህ አግባብ አይደለም፡፡ ለኦህዴድ 25ኛ ዓመት የምስረታ በዓልም ሌላ ግነት የበዛበት ጩኸት እየሰማን ነው፡፡
የርዕሰ ጉዳዬ ሀሳብ፣ ‹‹መንግሥት ለምን ጩኸት ይወዳል?›› የሚል ነው፡፡ በተለያዩ የልማት ሥራዎች እና መንግሥታዊ እርምጃች ውስጥ ጩኸትን መፈለግ እና መሻት ተገቢነት አለው ብዬ አላምንም፡፡ ለምን? ሥራውን በአግባቡ የሚሰራ መንግሥት ጩኸት አይፈልግም፤ አያሻውምም፡፡ ብዙ አያወራም፤ እንዲወራለትም አይፈልግም፡፡ ሥራው በራሱ ታሪካዊ ምስክሩ ነውና፡፡
ነገር ግን ኢህአዴግ የመንግሥት፣ የግሉን ሚዲያ የኅብረተሰቡን የሀሳብ በአቅጣጫ በተለያዩ ጊዜያት የማስቀየር የማስጮህ ልምድ አለው፡፡ በዚህ ረገድ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ማንሳት አስፈላጊ ነው፡፡ አቶ መለስ ወቅት እየጠበቁ የሚዲያውን እና የኅብረተሰቡን ሀሳብ ለተወሰኑ ጊዜያቶች በ‹‹አዳዲስ›› የተቀመሩ አጀንዳዎች (አነጋጋሪ ንግግሮችንና ቃላትን ይጨምራል) መስረቅ እና መጥለፍ የተካኑ ነበሩ ብል ያጋነንኩ አይለመስለኝም፡፡ ሚዲያው (አጠቃላይ ለማለት አይቻልም) እና ኅብረተሰቡ ‹‹አዲሱ››ን ርዕሰ ጉዳይ በመዘገብ፣ ትንታኔ በመስጠትና የመነጋገሪያ አጀንዳ እና ወሬ በማድረግ ለተወሰነ ጊዜ ሌላ ሐሳቡን በመጠኑ እንዲረሳ እና እንዲዘነጋ የቤት ሥራ ይሰጡት ነበር፡፡ ከዚያም ቀን እና ጊዜ ጠብቆ ሌሎች አጀንዳዎች እና የጩኸት ዜማዎች ይመጣሉ፡፡
በዚህ ቀመራዊ አካሄድ ሥርዓቱ ህዝብን ግራ እና ቀኝ እያወዛወዘ ‹‹ህዝብ የተሰጠን …ኮንትራት›› በሚል 24 ዓመታትን ሲገዛ ኖራል፡፡ ተጨማሪ ዓመታትንም ይፈልጋል፡፡ በዋነኝነት ጩኸት መውደዱም ለዚሁ ነው – ለሥልጣኑ!!!

ትጥቅ ትግል ፣ ሰላማዊ ትግል ፣ ሁለገብ ትግል

March 26,2015
(አቶ ዮናታን ተስፋዬ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ ናቸው። ይህ ጽሁፍም ፓርቲን ወክለው ሳይሆን ራሳቸውን ወክለው የጻፉት ነው)
ወቅታዊ አጀንዳ እና በቁንፅል የሚተው ባይሆንኝ ነው – በትግስት አንቡልኝyonatan
ጭቆና ሲበዛ ሰዎች ብዙ መንገድን ተጠቅመው መታገል ይሻሉ፡፡ የጭቆናውን ቀንበር ለመስበር ጨቋኙን ከመግደል አንስቶ ራስን እስከማቃጠል ድረስ የሚደርሱ በርካታ መንገዶችን ሊጠቀሙ ይችላሉ፡፡ ከአገዛዝ ሰንሰለት ራስን ነፃ ለማድረግ ብዙዎች ተጨንቀው ማሰብም አይፈልጉም፡፡ በቃ ገዢውን ወዲያ አሽቀንጥሮ ጥሎ ነፃ መሆን (end of the story end of the oppression)! በተፈጥሮ ነፃ ሆኖ የተፈጠረ ሰው በሂደት እጅግ በተወሳሰበ የህይወት መስተጋብር ውስጥ ቢኖርም የጭቆናው ለከት ሲያልፍ ግን ቀስቃሽ ሳያሻው እንደቡድንም ይሁን በግል በነሲብ ወደ ነፃነት ትግል መግባቱ አይቀርም፡፡ ነፃነት ከብዙ ምክንያታዊነትም በላይ የስሜት ሀይሉ ከፍተኛ ገፊ በመሆኑ ለነፃነት የሚደረገውም እንቅስቃሴ በራሱ ድንገታዊነት ይበዛዋል፡፡ ‘መቼ’ እና ‘እንዴት’ን አያጠይቅም፤ ‘ለምን’ የሚለው ብቻ በቂው ነው፡፡
እንግዲህ እዚህ ጋር ነው የነፃነት ትግል መሪዎች ሚና ወሳኝ የሚሆነው፡፡ ጭቆናን ከምክንያታዊነት በላይ በስሜቱ ተፀይፎ ነፃነቱን ሊቀዳጅ የተነሳን ሰው መንገዱን ማመላከት የመሪዎቹ ሚና ነው፡፡ መሪው የትግሉን ‘እንዴትነት’ ‘መቼ’ ምን መደረግ እንዳለበት አፍታቶ ማሳየት እና እምቅ የሆነውን የነፃነት ፍላጎት ሀይል በተጠናና በተገቢው ቦታ ጥቅም ላይ እንዲውል ማስቻል፤ በዚህም አኳኋን ታጋዮችን አስተባብሮ መምራት አለበት፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥም የነፃነት ትግል መሪ ከስሜት በላይ እጅግ ምክንያታዊ እና በአስቸጋሪ ሁናቴዎች ውስጥም ለታለመው ግብ ሲባል በርካታ ፈታኝ ውሳኔዎችንም እንዲያሳልፍ ይጠበቅበታል፡፡
የዛሬን መጨቆን ሳይሆን የነገን የተጨበጠ ውጤት ቀድሞ ማለም ለዛም የሚከፈለውን መስዋእትነት ሁሉ መክፈል ግዴታው ነው፡፡ ከተራ ውሳኔ አንስቶ በሰዎች ህልውና ላይ እስከመወሰን የሚያደርስ ጠንካራ የዲሲፕሊን ሰው የመሆን ኃላፊነቱ የትግሉ መሪ ላይ ይወድቃል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ሂደቱ ከየት ተነስቶ የት እንደሚደርስ በጠራ ሁናቴ የሚያልም፤ ከግቡም ለመድረስ የቆረጠ፤ ተግባራዊ እና ለዛም ሁነኛ መላ ቀያሽ ብልሃተኛ መሪ ትግሉን ከጫፍ ለማድረስ ይቻለዋል፡፡
ትግል ተፈጥሯዊ ነው – በብልሃት ማስተባበር እና መምራት ደግሞ ትግልን ከፍሬ የሚያደርሱ ነገሮች ናቸው፡፡ ከዚህ ተነስተን በኢትዮጵያ ውስጥ ስለሚካሄዱት የነፃነት ትግሎች እንፈትሽ፡፡ አዋጪነታቸውንና ኪሳራቸውን እንመዝን፡፡
NOTHING PERSONAL NOR DESTRUCTIVE!
ትጥቅ ትግል በኢትዮጵያ?
———————-
* በ21ኛው ክ/ዘመን የትጥቅ ትግል አለማቀፋዊ አንደምታው እጅግ የተወሳሰበና ከፍተኛ የሰው እና የሉዓላዊነት ዋጋ የሚያስከፍል ነው፡፡ ለነፃነት እሞታለሁ ብሎ የወጣን ሰው አስተባብረህ ከምታስጣጥቀው መሳሪያ ጀምሮ የተለያዩ ሎጀስቲክና ዲፕሎማሲያዊ ድጋፎችን ማግኘት ግድ ይላል (ከመጋረጃ ጀርባ ያለውን የዓለም ሴራ ቀመስ ፖለቲካ ትተን)፡፡ እነዚህን ድጋፎች ለማግኘት ደግሞ በዓለም ላይ ከሚገኙ ታላላቅ መንግስታት ጀምሮ ገዢ መሬት ከሚሰጡህ አካላት ጋር በበርካታ ጉዳዮች ላይ ውል መፈፀሙ አይቀርም፡፡
ህወሃት ትጥቅ ትግሉን ድል አድረጎ ስልጣኑን ለመቆናጠጥ በሀገር እና በህዝብ ላይ እስከመደራደር ደርሷል፡፡ ለትጥቅ ትግሉ ስኬት ሲባልም ብዙ ታሪካዊ ስህተቶችም መፈፀማቸው ያልሻረ ቁስል ነው፡፡
በዚህ ዘመን ደግሞ በትጥቅ ትግል ኢህአዲግን ከስልጣን ማውረድ ከዓለም ነባራዊ ስርዓት አንፃር እጅግ አስቸጋሪ እና በአደጋ የተሞላ ነው (at this point there is no near-safe deal)፡፡ ስለዚህ ጥያቄው አህአዴግን ለማስወገድ ከተለያዩ ሀይሎች ጋር የሚደረጉት ስምምነቶች በእውነት ሚዛን ይደፋሉ ወይ? የሚፈፀሙት ስምምነቶች ህወሓት (ሊያውም በዘመነ ጦርነት) ካስከፈለን ዋጋ ምን ያህል ቢሻሉ፤ ምን ያህልስ የህዝባችንን እና የሀገራችንን ጥቅም ያስቀደሙ ወይም ከግምት አስገብተው የተፈፀሙ/ሊፈፀሙ ያሉ ናቸው? እነዚህ እና መሰል ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ እስካላገኙ ድረስ በዚህ ዘመን የሚደረገው የትጥቅ ትግል ለኢትዮጵያ የሚኖረው ፋይዳ ‘ከድጡ ወደማጡ’ ከመሆን ያለፈ አይሆንም!
* ከዚሁ ጋር በተዛመደ የኢትዮጵያ ታጣቂ ሀይሎች የመረጡት ገዢ መሬት የሙግቱ ዋና ማጠንጠኛ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ የሻቢያ ግዛት ኤርትራ፡፡ እዚህ ላይ ስለ ሻቢያ እና ወያኔ ፍቅርና ጠብ – አንድነት እና ልዩነት አሁን ስላላቸው ለክፉም ለደጉም የእርስ በእርስ መጠባበቅ ማውራቱ ‘አውቆ የተኛን . . .’ ካልሆነ በስተቀር ለማንም ምስጢር አይደለም፡፡ ምንአልባትም እነዚህ ሁለት ሀይሎች በኢትዮጵያም ይሁን በቀጠናው ጉዳይ ላይ የራሳቸው ቁማር እየተጫወቱ ስልጣናቸውን ለማስቀጠል ምንም ሊያደርጉ እንደሚችሉም ለሁሉም ሰው ግልፅ ነው፡፡
ይህን ካልን ዘንዳ ኢትዮጵያ ውስጥ በትጥቅ ትግል ለውጥ እናመጣለን የሚሉ ሃይሎች ከሻቢያ ጋር በምን መልኩ ሰምምነት አካሂደው ገዢ መሬት አገኙ? በዚህ ትግል ውስጥ የሻቢያ ጥቅም ምንድን ነው? በየትኛው ስሌት የኢትዮጵያ ታጣቂ ሀይሎች ከሻቢያ ድጋፍ አግኝተው የኢትዮጵያን ጥቅም ያስጠብቃሉ? (በቀደም ለት የኤርትራው ፕሬዘዳንት ስለኤርትራ እና ኢትዮጵያ ስላለፈውና መሆን ስላለበት ሲያብራሩ እነዚህ ጥያቄዎች ይበልጡኑ አወዛጋቢና በትጥቅ ትግሉ የተሰማሩ ሀይሎች ግልፅ ሊያደርጓቸው እንደሚገቡም ጭምር ተገንዝቤያለሁ!)
ስለሆነም እነዚህ መሰረታዊ ነጥቦች ምላሽ ባላገኙበት ሁናቴ ኢትዮጵያ ልጆቿን ዳግም ወደ እርስ በእርስ ጦርነት የምትከትበት አሳማኝ ምክንያት አይኖርም (ምሬት እና ጭቆና ብቻውን ለውጥ ሊያመጣ እደማይችል ከላይ በመግቢያዬ ያሰፈርኩትን ልብ ይሏል) – የጦረኞቹ የፖለቲካ ሰዎች ይህን መሰሉን ጉዳይ አፍታተው መዳረሻውን፣ ጥቅምና ጉዳቱን እስካሁን ማሳመንም ሆነ ደፍረው ለውይይት ሊያቀርቡት አለመቻላቸው በራሱ የትጥቅ ትግሉ አዋጪ እንዳልሆነ አመላካች ነው (there is something fishy behind the silence)፡፡ (እንዲህ አይነቱ ነገር መገለፅ የለበትም የሚል መከራከሪያ እኔ አልቀበልም – ሁላችንም በሀገራችን ጉዳይ ያገባናል!)
* እዚህ ጋር አብሮ መነሳት ያለበት ነገር ደግሞ – ይህን ትግል ለመቀላቀል የሚፈልጉ ሰዎች የሚከፍሉት አላስፈላጊ መስዋእትነት ነው፡፡ ገና ሳይጀመር በባዶ ሜዳ፤ በጉዞ ላይ እየተለቀሙ ዘብጥያ የወረዱትን እግዜር ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ ያም ብቻ ሳይሆን ከምትታገልለት ህዝብ ውጪ ሆነህ ልታገኘው የምትችለው የሎጀስቲክና ሌላም መሰረታዊ ድጋፍ አናሳ ነው፤ ከናካቴውም ላይኖር ይችላል፡፡ ለምሳሌ ያህል አሁን በኤርትራ ምድር ከሌላ ሀይል ጋር ውህደት የፈፀመው የአርበኞች ግንባር በተለይ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ከፍተኛ ድጋፍን ማግኘት የቻለና በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ተስፋ ተጥሎበት ነበር፡፡ ምከንያቱ ደግሞ ይታገል የነበረው በዛው በህዝቡ መሃከል ሆኖ መሆኑ ነው (ያ አደጋ የለውም እያልኩኝ አይደለም ቢያንስ ግን ከባህሩ የወጣ አሳ አለመሆን ያለው ጠቀሜታ ከጉዳቱ ይበልጣል)፡፡ በየትኛው መልኩ ጭቆናው በቃኝ ብሎ ለሚያስብ ሰው ‘መንገዱም ጨርቅ’ ለመቀላቀልም ቀና የነበረ ግንባር ነበር፡፡ አሁንስ?
* እርግጥ የህዝባችን ስነ ልቡና ለትጥቅ ትግል የቀረበ መሆኑ አይካድም፡፡ ታሪካችንም ቢሆን ስልጣን በጦረኞች እንጂ በሰላማዊ መንገድ ተቀይሮ አያውቅም፡፡ ያም ሆኖ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁናቴ የዚህን መሰሉን የህዝብ ስነ ልቡናዊ ዝግጁነት ጥቅም ላይ ሊያውል የሚችል አስማሚ አጀንዳም የለም፡፡ ለዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ ራሱ በትጥቅ ትግል ያሉት የተበታተኑ ሀይሎች ናቸው፡፡ ይህ ችግርም ባልሆነ ነበር ግና ለነፃነት ዋጋ የሰጠና ለዛም ለመሞት የቆረጠው ምን ያህል ነው? አምናለሁ ነገርን የሚለውጡት ሚሊዮኖች ሳይሆኑ ጥቂቶች ናቸው – ቢሆንም በኔ እምነት እነሱም ከላይ በዘረዘርኳቸው ምክንያቶች ሌላ አማራጭ እንዲጠቀሙ ይገፏቸዋል (ለዚህ ነው ብዙዎች ተስፋ ቢያስቆርጥ እንኳን ለሰላማዊው ትግል ቅድሚያ የሚሰጡት)፡፡ ወጣም ወረደ በዚህ ጉዳይ ላይ የማነሳው መሰረታዊ ጥያቄ ግን በጣም ግልፅ ነው – ይህን ታሪክ እና ባህል ይዘን እንቀጥል ወይስ እንቀይረው? እውን ትጥቅ ትግል በትጥቅ ትግል የሚቀያየርን የስልጣን አዙሪት መስበር ይችላል? የጦረኛን ህዝብ ስነ ልቡና በጦረኛ መቀየር ይቻላልን?
* ሌላው ደግሞ ጦርነት ለሰብዓዊነት ቦታ አለመስጠቱ ነው፡፡ የሰው ልጅ አንድ ጊዜ ከገደለ በኋላ – ደም ካየ በኋላ ለሌላ ሰብዓዊ መብቶች ሊቆረቆር የሚችልበት ሩህሩህነት አይኖረውም፡፡ መግደልን የተለማመደ አንድ ሰው ጭካኔን እየተለማመደ መሆኑን ማንም አይክደውም፡፡ በዚህ ሁናቴ ስብእናው የሚገነባ ግለሰብም ሆነ ቡድን ደግሞ ለወደፊቱ ህልማችን አደጋ ነው፡፡ ሰው መጨከን የለበትም እያልኩኝ አይደለም (there may come critical times in life)- ሁሉም ነገር ግን የሚቃኝበት መንፈስ እንደ ነገሩ ተጨባጭ ሁናቴ መሆን አለበት፡፡ አሁን ላይ ይህን ያህል ርቀት መሄድ ይቻላል ወይም አለብን? መቀበል ይቸግረኛል!
ይህን የበለጠ ለማብራራት ሩቅ ሳንሄድ የሀገራችንን የትናንት ታሪክ እናንሳ፡፡ የህወሓት እና ኢህአፓ ታጋዮች ብረቱን እስኪጨብጡት ድረስ እንደሁላችን ሰዋዊ ባህሪያቸው እንዳልተለያቸው ምንም አጠያያቂ አይደለም – አንዴ ሞትን ተኩሰው ከተፉ በኋላ ግን የማያባራ እልቂት ሆነ፡፡ ሰብዓዊነታቸው ተሟጦ ግፉ ለኛም ተረፈ! ትጥቅ ትግል ይህ እንዳይሆን የሚሰጠን አንድም ዋስትና የለውም! በደም የታጠበ እጅ ህሊናው ለመፅዳት ትልቅ ፈተና አለበት፡፡ እረግጥ ሰብዓዊነት በፖለቲካ አውድ ውስጥ አሻሚ ትንታኔ ቢሰጥበትም በጥቅል ግን ከትጥቅ ትግል የፖለቲካ ትርፍ በላይ በማህበረስብ ስነ ልቦና ላይ የሚኖረውን ጠባሳ ከኛ በላይ ህያው ምስክር ያለ አይመስለኝም፡፡ የከፋ የሚያደርገው ደግሞ አሁንም የአንድ አገር ሰው ወንድም በወንድሙ ላይ እጁን ማንሳቱ ነው፡፡
ሰላማዊ ትግል በኢትዮጵያ?
————————
* ዓለም ዛሬ የምትመራበት መርህ እና ሴራው እየረቀቀ ቢመጣም አንድ እውነት ግን መቼም ሊሻር አይችልም! በሰላማዊ ትግል ውስጥ ማናቸውንም ሀይል ከጎን ለማሰለፍ ትለቁ ነገር አገዛዝን በህግ የበላይነት እና የሞራል ልዕልና ማጠየቅ ነው፡፡ መሳሪያ ደግኖ ሲመጣ ደረትህን ነፍተህ መጋፈጥ የመሳሪያውን ብረት በእቶን እሳት ከማቅለጥ ያነሰ አይደለም፡፡ ዛሬ አንተን ቢገድል፣ ነገ ጓድህን ቢደግመው – ቀጥሎ ቃታውን የመሰብ አቅም አይኖረውም – ምክያቱም ጓዶችህ በባዶ እጅ ገጥመው እየወደቁ ህሊናውን አሸንፈውታል፡፡ ገዳይህ ብቻም ሳይሆን ሌላውም ሀይል ይህን ቆራጥነትህን ከመቀበል እና ከመተባበር ውጪ አማራጭ የላቸውም፡፡
እርግጥ ጨካኞች የሞቀ ቤታቸው ውስጥ ናቸው፣ ይህን ቆራጥነትህን አያዩትም አይረዱትም ስሜትም አይሰጣቸውም – መጠቀሚያቸው ግን የሚልኩት ወታደርና ፖሊስ ነው፡፡
በሰላማዊ ትግልም የምታሸንፈው ይህንኑ ሀይል እንጂ ጨቋኞቹን አለመሆኑ እሙን ነው፡፡ አፈሙዙን አዙሮ ጨካኞችን ወደ ዘብጥያ እንዲያወርድ የሚገደድበት የትግል ስልት ቢኖር ሰላማዊ ትግል ብቻ ነው፡፡ ልትገድለው ሳይሆን ሞትን ደፍረህ ለነፃነት ከምታደርገው ትግል በላይ ልቡን አቅልጦ ከጎንህ የሚያሰልፍው ሌላ መንገድም የለም፡፡ እንግዲህ ይህ የትግል ስልት በርካታ ጨቋኞችን ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፍ ስርዓቱን ጭምር እየተፈታተነ ያለ የትግል አይነት ነው፡፡
* በሌላ በኩል ይህ የትግል ስልት በኢትዮጵያ ያልተሞከረ በተግባርም እምብዛም ያልታወቀ ነው፡፡ የህዝባችን ስነ ልቡና በራሱ ለዚህ የትግል ስልት ዝግጁ አይደለም፡፡ ለዚህም ነው ኢህአዴግን በሰለማዊ ትግል ከማስጨነቅ ይልቅ ገና ከጅምሩ እዚህም እዚያም ትጥቅ ትግል የተጀመረው፡፡ ለዚህም ማሳያው ከ1998 በኋላ ከተፈጠረው ቡድን ውጪ ያሉት ታጣቂዎች ከጅምሩም በረሃ ወርደው የነበሩ መሆናቸው ነው (እርግጥ አንዳንዶቹ ከህወሓት ጋርም አብረው የገቡ ናቸው)፡፡ ከ1998 በኋላ ትጥቅ ትግልን የመረጠው ቡድንም ቢሆን ሰላማዊ ትግል ለማካሄድ እምብዛም አልጣረም፡፡ ኢህአዴግ እንከን የለሽ ምርጫ አደርጋለሁ አለ፤ ፓርቲዎች ተሰባሰቡ፤ እስካሁን ተፅዕኖ መፍጠር የቻለ ቅንጅት ፈጠሩ፤ እንከን የለሽ ምርጫ ተካሄደ፡፡ ውጤቱ ግን ብዙዎችን ተስፋ አስቆረጠ፡፡ የዘመነ የምርጫ ፖለቲካም አበቃለት! ቀጠለና አንድነት ፓርቲ ሰላማዊ ትግል አካሂዳለሁ፤ ህዝብን የስልጣን ባለቤት አደርጋለሁ ብሎ ትግል ሲጀምር – ሌሎች ደግሞ አይ ህዝቡ የሰጠንን ድምፅ በመሳሪያ እናስመልሳለን ብለው ጦርነት አወጁ፡፡ በኔ እምነት ሰላማዊ ትግል በኢትዮጵያ ምድር ላይ አለመጀመሩን ብቻ ሳይሆን ለመጀመርም ያለውን ችግር ይህ ኩነት ሁነኛ ማሳያ ነው፡፡
ምናልባትም የዚህ የትግል ስልት ትልቁ ተግዳሮት በህዝቡ ዘንድ አዲስ መሆኑና ለመቀበል እና ለመተግበርም እጅግ ድካምን የሚጠይቅ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ነፍጥ አልባ ትግል ለመምራት የሚነሱ መሪዎችም መጥፋት ነው፡፡ አንዱ ወደ እስር ሲጓዝ ሌላው በስሩ ተተክቶ ትግሉን ማስቀጠል ግድ የሚል የትግል ስልት መሆኑን ብዙዎች ይዘነጉታል መሰል አንዱ ሲነካ አስሩ ወይ ቤቱ ይቀመጣል ወይ ይሰደዳል ወይ ጦር ያነሳል፡፡ ይህ ትግል በቅብብሎሽ እንጂ በአንድ ትውልድ ብቻ የሚያበቃም ላይሆን ይችላል፡፡ እስክንድር ሲታሰር ተመስገን ይተካል ተመስገን ሲታሰር ሌላው ይቀጥላል እንጂ አለቀቀ ደቀቀ ሰላማዊ ትግል አይሰራም ሊባል አይችልም፡፡ አንዷለም ሲታሰር ሃብታሙ ይተካል ሃብታሙ ሲታሰር እኛ እንቀጥላልን እኛ ስንገባ ሌላው ይከተላል፡፡ አንድነት ፈረሰ ሰማያዊ ይቀጥላል – ሰማያዊ ሲፈርስ ወይ ሌላ ፓርቲ ወይ በሌላ መልክ ትግሉ ይቀጥላል፡፡ መሪ ብቻ አያሳጣ!
* ነፍጥ አልባ ትግል በመውጣትና በመውረድ ውስጥ፤ በአድካሚና ተስፋ አስቆራች ጉዞ ዘላቂነት ያለው ድል ያስገኛል፡፡ በነፍጥ አልባ ትግል ብዙዎቻችን ሙሴን እንጂ ኢያሱን ልንሆን አንታደልም (የህወሓቶቹን ሳይሆን የቅዱስ መፅሃፎቹን)፡፡ እንቅፋቶችም ብዙ ናቸው – በመንገድ ተንጠባጥበው የሚቀሩ – በተስፋ መቁረጥ ውስጥ የሚሰናከሉ በርካቶች ለትግሉ በጠላትነት ሊነሱበት ሁሉ ይችላሉ፡፡ ካዛም አልፎ በሌላው ዓለም እንደታየው ዘለግ ያለ ጊዜ መውሰዱ አሰልችነት ቢኖረውም ውጤቱ ግን በሂደቱ ሁሉ የተረጋገጠ ነውና ተመራጭ ያደርገዋል፡፡ ህዝብን የስልጣን ባለቤት እንዲሆን ማስቻል ብቻ ሳይሆን አመለካከቱንና ሌሎች በርካታ ጉዳዮችንም በሂደቱ እየታገለና መልክ እያስያዘ ከግቡ ይደርሳል፡፡
አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ይህን አድካሚ ጉዞ የሚያቃልል እና መንገዱንም የሚያሳጥር ምቹ ሁኔታ አለ፡፡ ላለፉት 40 እና 50 ዓመታት በደም መፋሰስ ውስጥ ያለፈ ህዝብ በስነ ልቦና ረገድ ያን ጊዜ ዳግም ለማየት ፍፁም አይሻም፡፡ ከዛም ሲያልፍ አዲሱ ትውልድና በእርስ በርስ ጦርነቱ ያልነበረው የህበረተሰብ ክፍል አሁን ላለው ዓለምአቀፍ ስርዓት ቀረቤታ ያላቸው መሆኑ ለአዲስ የትግል ስልት ዝግጁነታቸው ከፍተኛ የመሆን እድሉ ቀላል አይደለም (የድምፃችን ይሰማን እንቅስቃሴ ልብ ይሏል)፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ጨቋኞቻችን ዘመኑን የማይመጥኑ በአዲሱም ትውልድ በዓለምም ዘንድ መቀይር እንዳለባቸው፣ በእድሜ መግፋትም ቢያንስ ጡረታ መውጣት እንዳለባቸው የጋራ ግንዛቤ መኖሩ የሰላማዊ ትግሉን የሚያፋጥን ነባራዊ እውነታ ነው፡፡
* ሰላማዊ ትግል በምርጫ ፖለቲካ የሚገደብ አይደለም፡፡ እርግጥ ምርጫን እንደ ጥሩ አጋጣሚ ሊጠቀም ይችላል፡፡ ሂደቱ በራሱ ከአነስተኛ ነገሮች በመጀመር እያደገና እየረቀቀ ይሄዳል፡፡ በትግሉ ውስጥ በተጠና መልኩ የሚንቀሳቀሱ ሰዎችን ብቻ ሳይሆን በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን የማቀፍ ባህሪም አለው፡፡ አውቀው ከሚተገብሩት ባልተናነሰ መልኩ ሳይሰማቸውና ሳያውቁት በትግሉ የሚሳተፉም እንዲኖሩ እድል ይሰጣል፡፡ በሕቡ እና በግላጭም ሊካሄድ ይችላል፡፡ ሰላማዊ ሆነው ህግን መጣስ ድረስም መሄድ ይቻላል – ለምሳሌ ያህልም በሩሲያ Pussy Riot (የሴቶች መብት ተሟጋቾች እንቅስቃሴ – በተከለከሉ ቦታዎች እና ነውር በሆነ ሁናቴ ጭምር ተቃውሞን ማሰማት)፣ በኢትዮጵያ በቅርቡ እየተደረገ ያለው በመገልገያ ብር ኖት ላይ ተቃውሞን በማስፈር ማሰራጨት . . . የመሳሰሉት . . .
* ሰላማዊ ትግል መነሻው እና መዳረሻው የታወቀ ነው፡፡ ጊዜው ምን ያህል ቢረዝም እንኳን ውጤቱ ግን ዘላቂነት ያለው ነው፡፡ ስልጣንን ከጨቋኞች የማውረጃ ትግል ብቻ ሳይሆን – የጦረኝነትን ባህልንና የህዝብ ስነልቦና መቀየር የሚችል ትግል ነው፡፡ ያለመሳሪያ ጨቋኞችን ከስልጣናቻው ማውረድ የቻለ ህዝብ በራስ የመተማመኑ መጠን ከፍተኛ ይሆናል፡፡ ማንም መጣ ማን ያለምንም ስጋት የፈለገውን የመሻር የፈለገውን የመሾም አቅም እንዳለው – እንደሚችልም የሚተማመን ህዝብ ሊኖር የሚችለው በሰላማዊ ትግል በሚመጣ ለውጥ ብቻ ነው፡፡ በተለይ እንደኢትዮጵያ በበርካታ ታሪካዊ ትብታብ እና ግጭቶች ውስጥ ላለፉ ሀገራት ሰላማዊ ትግል የቱንም ያህል ተስፋ አስቆራጭ እና አድካሚ ቢሆንም አማራጭ ግን ሊቀርብበት የሚችል አይመስለኝም!
* ሰላማዊ ትግል ጭቆናን ከማስወገድ ባለፈም በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ የመተማመን፣ የመተሳሰብና የመዋደድን ባህል ያሳድጋል፡፡ ሰብዓዊነትን ያጎለብታል፤ ለዓላማ መሞት እንጂ መግደልን ስለማያበረታታ ሰዋዊ የሆኑ እሴቶቻችንን ጠብቀን ስነምግባር ያለው ህብረተሰብ እንድንፈጥር ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል፡፡
ሁለገብ ትግል በኢትዮጵያ?
———————–
* ይህ አይነት ትግል በተለያዩ ሀገራት ተሞክሮ ስኬታማ ሆኗል፡፡ በጥቅል ሲታይም ህዝባዊ እምቢተኝነትን (የነፍጥ አልባ ትግል አካል) እና ህዝባዊ አመፅ (የትጥቅ ትግል ደጋፊ ‘hot spot for armed struggle’) አቀላቅሎ የሚሄድ የትግል ስልት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁናቴ ሲቃኝ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚበዛ – የጨቋኞች አፈና እንዲጠናከር ሰፊ እድል የሚሰጥ ነው፡፡
* በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁናቴ የዚህ አይነት ትግል ዋነኛ እንቅፋት ደግሞ የቆሸሸው ፖለቲካ ባህላችን ነው፡፡ መተማመን የጠፋበት፣ አንዱ አንዱን ማጥፋት የሚፈልግበት፣ ሴራ የበዛበት እና በተጠና መልኩ መንቀሳቀስ ማናናቅ አዋቂ በሚያሰኝበት የፖለቲካ ባህል ውስጥ ውስብስብነት ያለውን ሁለገብ የትግል ስልት እንጠቀም ማለት ኢህአዴግ እድሜ ልኩን ሲገዛ ይኑር ከማለት አይተናነስም፡፡ ይህ ብቻ ቢሆን ደህና፤ ነገር ግን ሁለገብ ትግልን በሀገራችን ወቅታዊ ሁናቴ ለመተግበር አስቸጋሪ የሚያደርገው ሌላ መሰረታዊ ጉዳይ “የየትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው” አይነት ለውጤቱ ብቻ ትኩርት የመስጠት ዝንባሌ ነው፡፡ እንዲህ አይነቱ ግድ የለሽ ለሂደቱ ደንታ የሌለው አካሄድ በሁለገብ የትግል ስልት ከሚያስገኘው ውጤት በላይ ኪሳራው የትየለሌ ነው፡፡ ስለዚህ በዚሁ ዘግተነው ወደ ማጠቃለያችን እናሳልጥ!
ማጠቃለያ
———-
በዚህ ሀቲት ውስጥ ለማመላከት እንደተሞከረው ሀገራችን አሁን ባለችበት ሁናቴ ከሁሉም የትግል ስልት ይልቅ ሰላማዊ የትግል ስልት ውጤታማነቱ የሚያሻማ አይደለም፡፡ እርግጥ ማናቸውም መንገድ የራሱ የሆነ መጥፎና ጥሩ ነገሮች ቢኖሩትም ከሌሎች የትግል አይነቶች በተሻለ የተመጠነ ኪሳራ ነገር ግን ዘላቂና የሚጨበጥ ውጤት ያለው የትግል ስልት መሆኑም አያከራክርም፡፡ ትልቁ ኃይልም ህዝብ ብቻ መሆኑ ከተቀሩት በቀጠናው ላይ አይናቸውን ከጣሉ ዓለምአቀፍ ሀይሎች ጋር ሰጥቶ መቀበል ወይም በሌላ ሴራ የመጠለፍ አደጋው በእጅጉ የቀነሰ ነው፡፡
ነፍጥ አልባ የትግል ስልት በሀገራችን አዲስ ከመሆኑ አንፃር ገና ዳዴ በማለት ላይ ቢሆንም በጥቂት ጀምሮ እየሰፋና ከዳር ዳር እንደሰደድ በመስፋፋት ለሀገራችን ዘላቂ ለውጥን ለማምጣት ሰፊ እድል ያለው ነው፡፡
ባጠቃላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ (በሀገር ቤትም ሆነ በውጪም) እነዚህን የተለያዩ የትግል ስልት አይነቶች ትርፍና ኪሳራ በመመርመር እና በማገናዘብ ለኢትዮጵያ የሚበጀውን መንገድ እንዲመርጥ እና እንዲደግፍ መልእክቴ ነው፡፡ ከመነሻዬም እንዳሰፈርኩት የትግል ፍላጎት፣ የነፃነት ስሜት ገፊ ሀይል እና ጭቆና ብቻውን ለለውጥ አያበቃምና ሀገራችን በተያያዘችው ከአገዛዝ ወደ ነፃነት የሚደረግ ትግልን የምትመሩ ቡድኖችና ግለሰቦች ቆም ብላችሁ መንገዳችሁን ብትመረምሩ መልካም ነው፡፡ ከታናሽ ወንድማችሁ በሚሆን ምክርም ፅሁፌን ላብቃ – ብቻ ምንም እንወስን ለውሳኔያችን ቆራጥ፣ የተግባር ሰው እና ለሀገራችን እና ለህዝባችን ስንል ከተራ ሴራ፣ በከንቱ ውዳሴ ከመኮፈስ የፀዳን እንሁን!
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

Tuesday, March 24, 2015

የጦማርያንና ጋዜጠኞቹ አቤቱታዎች ውድቅ ተደረጉ

March 24,2015
በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው የሚገኙት የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ሦስቱ ወዳጅ ጋዜጠኞች መጋቢት 15/2007 ዓ.ም ከሰዓት 8፡00 የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡
 
መዝገቡ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሾች ባቀረቧቸው ሁለት አቤቱታዎች ላይ ፍርድ ቤቱ መርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህም አንደኛ አቃቤ ህግ በተከሳሾች ላይ አለኝ ካለው ማስረጃ ዝርዝር ውስጥ 12 የኦዲዮ-ቪዲዮ ሲዲዎች አያይዞ ያቀረበ ቢሆንም፣ ሲዲዎቹ ለተከሳሾች እስካሁን ባለመድረሳቸው ተከሳሾች የቀረበባቸውን ማስረጃ ተመልክተው መልስ ለማዘጋጀት ሲዲዎቹ እንዲሰጧቸው ያቀረቡት አቤቱታ ሲሆን፣ ሁለተኛው ጉዳይ ደግሞ 4ኛ ተከሳሽ ማህሌት ፋንታሁን እና 9ኛ ተከሳሽ ኤዶም ካሳዬ በቃሊቲ እስር ቤት አስተዳደር ላይ ከጎብኝዎቻቸው መከልከል ጋር በተያያዘ አቅርበውት በነበረው አቤቱታ ላይ ብይን መስጠት ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱም ሁለቱንም አቤቱታዎች ውድቅ አድርጓል፡፡

የሲዲ ማስረጃውን በተመለከተ አቃቤ ህግ ማስረጃዎችን ኢግዚቪት ብሎ ስላስመዘገበ አሁን በዚህ ደረጃ ሲዲዎቹ ለተከሳሾች የሚደርሱበት አግባብ የለም በሚል ፍርድ ቤቱ የተከሳሾችን አቤቱታ እንዳልተቀበለው ገልጹዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሾች ማስረጃ በመስማት ሂደት ወቅት ማስረጃዎችን እየተመለከቱ መልስ እንዲሰጡ እንጂ ቀድሞ እጃቸው የሚደርስበት አሰራር የለም ብሏል ፍርድ ቤቱ፡፡


ፍርድ ቤቱ የቃሊቲ እስር ቤት አስተዳደር ላይ በሁለቱ ሴት ተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታም ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ እና የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰጠውን መልስ መመልከቱን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ ‹‹ለቀረበው አቤቱታ ማስረጃ ተያይዞ ያልቀረበ በመሆኑ…›› በሚል አቤቱታውን ቅድቅ አድርጓል፡፡ ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞች ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች ከሰኞ መጋቢት 21/2007 ጀምሮ ለሦሰት ቀናት ይሰማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Monday, March 23, 2015

ህዳሴም ሆነ ዉዳሴ ክህዝብ የሚደበቅ ምንም ነገር የለም!

March 23,2015
pg7-logoከሰሞኑ አገራችን ኢትዮጵያን በተለይም ብሄራዊ ጥቅሟንና ደህንነቷን በተመለከተ ሁለት አቢይ ዜናዎች የአገራቸን የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ጉዳዮች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚመለከታቸዉን አገሮች የአየር ሞገደች ተቆጣጥረዉት ነበር። ከእነዚህ ዜናዎች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ ኢትዮጵያ፤ ሱዳንና ግብፅ የህዳሴዉን ግድብ አስመልክቶ ስምምነት ላይ ደረሱ የሚል ዜና ሲሆን ሁለተኛዉ ደግሞ አለም አቀፍ ጋዜጠኞች የህዳሴዉ ግድብ የሚሰራበት ቦታ ድረስ ሄደዉ ባካሄዱት ጥናት መሠረት የህዳሴዉ ግድብ ፕሮጀክት ባጋጠመዉ ከፍተኛ የገንዘብ እጥረት የተነሳ እንዲዘገይ መወሰኑን የሚያወሳ ዜና ነዉ። አርበኞች ግንቦት ሰባት ለአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ኢትዮጵያ ዉስጥ ለሚሰሩ ምንም አይነት ስራዎችና በኢትዮጵያ ህዝብ ስም ከየትኛዉም አገር መንግስትና መንግስታዊ ካልሆነ ተቋም ጋር ለሚደረጉ ስምምነቶችና ዉሎች ሁሉ ባለቤቱ የኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ ነዉ ብሎ ያምናል፤ ስለሆነም አርበኞች ግንቦት ሰባት የኢትዮጵያን ህዝብ ብሄራዊ ጥቅምና ደህንነት ከሚመለከቱና በሚስጢር መጠበቅ አለባቸዉ ተብሎ ከሚታመኑ አንዳንድ ጉዳዮች ዉጭ ሌላ ምንም ስራ ወይም አለም አቀፍ ስምምነትና ዉል የኢትዮጵያ ህዝብ ሳያዉቀዉና ሳይሰማዉ በድብቅ መደረግ የለበትም የሚል የጸና እምነት አለዉ። ሆኖም ዛሬ ኢትዮጵያ ዉስጥ ያለዉ አገዛዝ ኢትዮጵያን ከቅኝ ገዢዎች በከፋ መልኩ የሚገዛ የጥቁር ፋሺስቶች አገዛዝ በመሆኑ የሚሰራቸዉ ስራዎችና በአለም አቀፍ ደረጃ የሚፈርማቸዉ ዉሎችና ስምምነቶች የኢትዮጵያን ህዝብ ብሄራዊ ጥቅም የሚጻረሩና የሚጋፉ ድብቅ ስምምነቶች ናቸዉ።
ይህ የወያኔ መሪዎች ከኢትዮጵያ ህዝብ ጀርባ ላይ ተሸሽገዉ የሚሸርቡት የድብብቆሽ ሴራ ዛሬ የተጀመረ አዲስ ክስተት አይደለም። ባለራዕዩ መሪ የሚል አላስፈላጊ የቅጽል ስም የተሰጠዉ መለስ ዜናዊ በ2004 ዓም ሐምሌ ላይ ከዚህ አለም በሞት ሲለይ ዜናዉ ለኢትዮጵያ ህዝብ የተነገረዉ በነኀሴ ወር ማለቂያ ላይ ነበር እሱም ቢሆን ሞትን ያክል ነገር ደብቆ ማቆየት ስለማይቻል ነዉ እንጂ አይነግሩንም ነበር። ከዚህ በተጨማሪ በሰሜናዊዉ የአገራችን ከፍል ወያኔ ከጎረቤት አገር ጋር የተዋዋለዉ መሬት ቆርሶ የመስጠት ዉል የኢትዮጵያ ህዝብ ሳያዉቀዉና ሳይሰማዉ የተደረገ ዉል ወይም ስምምነት ነዉ።
አርበኞች ግንቦት ሰባት አገራችን ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ብቻ ሳይሆን ከግዛቷ ተነስተዉ ወደ ጎረቤት አገሮች በሚፈሱ አለም አቀፍ ወንዞቿና በሌሎችም የአገር ዉስጥ ወንዞቿ ላይ ግደብ የመስራት ማንም ሊጋፋዉ የማይገባ የተፈጥሮ መብት አላት ብሎ ያምናል። በሌላ በኩል ደግሞ አባይን በመሳሰሉ ድንበር ዘለል ወንዞች ላይ የሚሰሩ ምንም አይነት የልማት ፕሮጀክቶች በዛቻና በማንአለብኝነት ሳይሆን በመግባባት፤ በመመካከርና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችን በሚያዳብሩ መልኩ መሰራት አለባቸዉ ብሎም ያምናል። አርበኞች ግንቦት ሰባት ይህንን የሚለዉ ደግሞ መሠረታዊ ኑሯቸዉ በአባይ ወንዝ ላይ አገሮች ሊያደርሱ የሚችሉትን የፖለቲካና የዲፕሎማሲ ጫና በመፍራት ሳይሆን ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶች ከመጀመራቸዉ በፊት ፕሮጀክቶቹን አስመልክቶ ሊነሱ የሚችሉ ዋና ዋና ልዩነቶች መወገድ አለባቸዉ፤ ልዩነቶችን ለማስወገድ ደግሞ የተሻለና አዋጭ የሆነዉ አማራጭ ዲፕሎማሲ ነዉ የሚል ጽኑ አምነት ስላለን በቻ ነዉ።
የወያኔ አገዛዝ እንደ ፈረንጆቹ ዘመን አቆጣጠር በ2011 ዓም የህዳሴዉን ግድብ ስራ ሲጀምር ከአራት ነጥብ ስምንት ቢሊዮን ዶላር ወይም 96 ቢሊዮን ብር በላይ የተገመተዉ ግዙፍ ግድብ ስራ ሙሉ በሙሉ ከአገር ዉስጥ የገንዘብ ምንጮች በሚገኝ ገንዘብ እንደሚሰራና አገዛዙ ግድቡንና የግድቡን ስራ አስመልክቶ ምንም አይነት ድርድር ከማንም አገር ጋር እንደማያደርግ ለለህዝብ ቃል ገብቶ ነበር። የግድቡ ስራ በተጀመረ በጥቂት አመታት ዉስጥ የግድቡ ግንባታ የአገሪቱን የካፒታል ጥሪት ሙጢጥ አድርጎ በመብላቱና በሌሎች በተጀመሩና ሊጀመሩ በእቅድ በተያዙ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ በግልጽ የሚታይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማድረግ በመጀመሩ አለም ባንክ፤ አለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅትና አያሌ ኢትዮጵያዉያን ምሁራን የግድቡ ስራና ግድቡ ላይ የሚፈሰዉ የካፒታል ብዛት እንደገና እንዲታሰብበት ምክር ለግሰዉ ነበር፤ ሆኖም ምክሩ የተሰጠዉ የሚሰማ ጆሮ ለሌለዉ ለወያኔ ነበርና ሰሚ ታጣ። ዛሬ ግድቡ ከተጀመረና ወያኔም በህዳሴዉ ግድብ ላይ ከምንም ከማንም አልደራደርም ካለ ከአራት አመታት በኋላ አንደኛ የግድቡ ፕሮጀክት ስራ በገንዘብ እጥረት የተነሳ እንዲዘገይ ተደርጓል፤ ሁለተኛ ወያኔ የህዳሴዉን ገድብ አስመልክቶ ከግብፅና ከሱዳን መንግስታት ጋር ስምምነት ላይ ደርሶ የፊታችን መጋቢት 14 ቀን ስምምነቱን ለመፈረም ጎንበስ ቀና እያለ ነዉ።
ለመሆኑ ይህ ወያኔ ከሱዳንና ከግብፅ ጋር የህዳሴዉን ግድብ አስመልክቶ የሚፈራረመዉ የስምምነት ዉሳኔ ይዘት ምንድነዉ? ዉሳኔዉ በሦስቱ አገር መሪዎች ፊርማ ከመፅደቁ በፊት ለምንድነዉ የዉሳኔዉ ባለቤት የሆነዉ የኢትዮጳያ ህዝብ እንዲያዉቀዉ ያልተደረገዉ? ባለፉት አራት አመታት ኢትዮጵያ ዉስጥ ምንም አይነት ገቢ ከሌላቸዉ ከተማሪዎችና ከአረጋዉያን ጀምሮ እስከ ቀን ሰራተኛዉ ድረስ ለህዳሴዉ ግድብ ግንባታ ገንዘብ አዋጣ ወይም ቦንድ ግዛ እየተባለ በሩ ያልተንኳኳ ኢትዮጵያዊ የለም። ታዲያ ይህ የኢትዮጵያ ህዝብ በራሱ ገንዘብ ለዕድገቴና ለብልፅግናዬ መሠረት ይሆነኛል ብሎ የሚያሰራዉ ግድብ ስራዉ በገንዘብ እጥረት ሲተጓጎልና በዚሁ ግድብ ዙሪያ ከዉጭ መንግስታት ጋር አለም አቀፍ ስምምነቶች ሲደረጉ ምንም የማይነገረዉ ለምንድነዉ?
የወያኔ መሪዎች ከሱዳንና ከግብጽ መሪዎች ጋር የህዳሴዉን ግድብ አስመልክቶ የተዋዋሉትን ዉል እንመራዋለን ብለዉ ከሚናገሩት ህዝብ ቢደብቁም ካርቱምና ካይሮ ወስጥ ሾልከዉ የወጡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ግብፅ የህዳሴዉ ግደብ ፕሮጀክት ላይ የቁጥጥርና የማነጅመንት ድርሻ አንደሚኖራት እየተነገረ ነዉ።እንደዚህ አይነቶቹ ከዚህ ቀደም በፍጹም የማይሞከሩ ወይም የማይታሰቡ ናቸዉ ተብለዉ ሲነገሩ የነበሩ ስምምነቶችና ዉሎች ዛሬ ተደርገዉና የሶስትዮሽ ስምምነት ተደርሶባቸዉ በፊርማ የሚጸድቁት ግድቡን ሰርቶ ለመጨረስ የሚያስፈልግ ገንዘብ ለማግኘት ነዉ ወይስ ሌላ ድብቅ አላማ አለዉ? ደግሞስ ግድቡ የሚሰራዉ ለህዝብ ግድቡን የሚሰራዉም ህዝብ ሆኖ ሳለ ለምንድነዉ ይህ በዉድም በግድም ገንዘብ ካላዋጣህ ወይም ቦንድ ካልገዛህ እየተባለ ቀንና ማታ ሲጠየቅ የኖረ ህዝብ በዚህ ግድብ ዙሪያ የሚደረጉ ዉሎችንና ስምምነቶችን እንዳያዉቅና ጭራሽ እንዳይሰማ የተደረገዉ? ካይሮና ካርቱም ዉስጥ እንደሚነገረዉ ግብፅ በህዳሴዉ ግድብ ግንባታ ዙሪያ የማነጅመንትና የቁጥጥር ሚና ይኖራታል የተባለዉ ዜና እዉነት ከሆነ እኛ እራሳችን አገራችን ዉስጥ በምንሰራዉ ግድብ ግብፅ ሊኖራት የሚችለዉ የማነጅመንትና ቁጥጥር ድርሻ ዬት ድረስ ነዉ የሚሆነዉ …ለምንስ እንዲህ አይነት ሚና እንዲኖራት ተደረገ?
አርበኞች ግንቦት ሰባት የሶስቱ አገሮ መሪዎች ስምምነቱን በፊርማ ከማጽደቃቸዉ በፊት የኢትዮጵያ ህዝብ ለእንደነዚህ አይነት ቁለፍ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት አለበት ብሎ ያምናል። የኢትዮጵያ ህዝብ ኢትዮጵያን አስመልከቶ የሚደረጉ ምንም አይነት ዉሎችና ስምምነቶች ብቸኛዉ ባለቤት ነዉና ከዚህ ህዝብ ተደብቆ የሚደርግ ምንም አይነት ስምምነት ሊኖር አይገባም።ስለዚህም የኢትዮጵያ ህዝብ እነዚህ ከዚህ በላይ ያነሳናቸዉ ጥያቄዎች ጥርት ባለ መልኩ እንዲመለሱለት የወያኔን አገዛዝ ማስጨነቅ አለበት፤ አለዚያ ይህ ጉዳይ ዉሎ ካደረ በኋላ የሚደረገዉ ሩጫ ሁሉ “ቁጭ ብለዉ የሰቀሉትን ቆሞ ማዉረድ ያቅታል” እንደሚባለዉ ይሆናል።
ግብፅና ሱዳን የረጂም አመታት ወዳጅነትና አመታት ያስቆጠረ ወተዳራዊ ስምምነት ያላቸዉ ተጎራባች አገሮች ናቸዉ። እነዚህ ሁለት አገሮች በቅርቡ ከወያኔ ጋር የደረሱበትን ስምምነት “የግብፅን ፍላጎት የሚያረካ” ስምምነት ነዉ እያሉ ካርቱምና ካይሮ ዉስጥ አስተያየት በመስጠት ላይ ሲሆኑ ኢትዮጵያ ዉስጥ ግን ሁሉም ነገር ህዝብ እንዳያዉቀዉ በሚስጢር መያዙ እየታወቀ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መ/ቤት “አዲስ ምዕራፍ” ተከፈተ እያለ የፈረደበትን የኢትዮጵያ ህዝብ መሸንገል ጀምሯል። በሌላ በኩል ደግሞ ወያኔ ሱዳንና ግብፅ በቅርቡ ካርቱም ላይ የደረሱበት ስምምነት እዚያዉ ካርቱም ዉስጥ የፊታችን ሰኞ በሦስቱ አገሮች መሪዎች ፊርማ ይጸድቃል ተብሎ በሚጠበቅበት በአሁኑ ወቅት የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታ አል ሲሲ የዉጭ ጉዳይና የዉኃ ኃብት ልማት ሚኒስተራቸዉን አስጠርተዉ ሦስቱ አገሮች የደረሱበትን ሰነድ መርምረዉ ሪፖርት እንዲያቀርቡላቸዉ ማዘዛቸዉ ከወደ ካይሮ ተደምጧል። እንግዲህ ይታያችሁ እኛ ኢትዮጵያዉያን የሦስቱ አገሮች ስምምነት ምን እንደሆነ እንኳን ሳናዉቅ ግብፅ እሷ እራሷ የደረሰችበት ስምምነት አልጥም ብሏት ተጨማሪ ማብራሪያ እንዲሰጣት ጠይቃለች። ይህ የሚያሳየን አገሮች ለብሄራዊ ጥቅማቸዉና ደህንነታቸዉ ምን ያህል እንደሚጨነቁና አርቀዉ የሚመለከቱ አስተዋይ መሪዎች ደግሞ የሚጨንቃቸዉና የሚያሳስባቸዉ ይህ አሁን የሚመሩት ህዝብ ብቻ ሳይሆን ወደፊት በተከታታይ የሚመጣዉ ትዉልድ ጭምር መሆኑን ነዉ።እኛ ኢትዮጵያዉያን ግን ለእንደዚህ አይነት መሪዎች አልታደልንም። የኛ መሪዎች እንኳን ለሚመጣዉ ትዉልድ ሊጨነቁ ለዛሬዉም ትዉልድ “እኛ ከሞትን ሠርዶ አይበቀል” የሚሉ ስግብግቦች ናቸዉ።
ወያኔ ከራሱ ዉጭ ማንንም የማይሰማ፤ልዩነትን የማያስተናግድና የሌሎችን ሃሳብ ከሱ ሀሳብ የተሻለ መሆኑን እያወቀም ቢሆን የማይቀበል ችኮ መሆኑን በተደጋጋሚ አሳይቶናል። ዛሬ ላይ ቆመን ወደ ኋላ ዞር ብለን የትናንቱን ስንመለከት ወያኔ በህዳሴዉ ግድብ ዙሪያም ገና ከጥንስሱ ጀምሮ ያሳየን ይህንኑ ችኮነቱንና “እኔን ብቻ ስሙ” ባይነት ዕብሪቱን ነዉ። በተለይ የህዳሴዉን ግደብ በተመለከተ አባይ ወንዝ ላይ የሚገነባዉ ግድብ ከዚህ ቀደም በማንም ኢትዮጵያዊ ያልታሰበና የልተወጠነ ፍጹም አዲስ የሆነ ወያኔ ለኢትዮጵያ ያበረከተዉ ገጸ በረከት መሆኑን ለማሳየት ብዙ ጥሯል፤ አንዳንድ የዋሆችን ደግሞ አሳምኗል።ወያኔ ሁሌም ቢሆን ጥረቱና ፍላጎቱ እራሱን ከብጤዉ ከደርግ ጋር እያወዳደረ የተሻለ ሆኖ ለመታየት መሞከር ነዉ እንጂ የተሻለ ስራ መስራት ስላልሆነ በህዳሴዉ ግድብ ላይም አብዛኛዉን ግዜ ያጠፋዉ “አባይን የደፈረ” ተብሎ ለመጠራት ስለሆነ ዛሬ ግድቡ ግንባታዉ አልቆ አገልግሎት መስጠት በሚጀምርበት ወቅት የግድቡ ስራ ከመጀመሩ በፊት ተሰርተዉ ማለቅ የነበረባቸዉን ስራዎች እየሰራ ነዉ።
በቅርቡ አንድ አለም አቀፍ የጋዜጠኞች ቡድን ግድቡ የሚሰረባት ቦታ ድረስ በመሄድ የፕሮጀክቱን እንቅስቃሴ በተመለከተ ጥናት አትንቶ የግድቡ ስራ በከፍተኛ የገንዘብ እጥረት የተነሳ ይዘገያል ብሎ ሪፖርት ማቅረቡ የሚታወስ ነዉ። ጉዳዩን በቅርብ ለምናዉቀዉ ለኛ ለኢትዮጵያዉያን ግን እዉነቱ ከዚህ በላይ ነዉ። የህዳሴዉ ግደብ የሚዘገየዉ በገንዘብ እጥረት ብቻ አይደለም። የዚህ ትልቅ ፕሮጀክት ድህረ ጥናት ሁኔታዎችን የላጤነና ቅደም ተከተሎችን ያላገናዘበ ጎደሎ ጥናት ነበር፤ ከዚህ በተጨማሪ ሩጫዉና ግርግሩ የተጀመረዉ የህዳሴዉን ግደብ የመሰለ ግዙፍ የ96 ቢሊዮን ብር ፕሮጀክት በይድረስ ይድረስ ሰርቶ ለመጨረስ ነበር።
የብዙ አለም አቀፍና የአገር ዉስጥ ኤክስፐርቶች ግምት በግልጽ እንደሚጠቀመዉ የህዳሴዉን ገድብ ግንባታ ጨርሶ አግልግሎት የሚሰጥበት ደረጃ ላይ ለማድረስ ፕሮጀክቱ በዕቅድ ከተያዘለት በጀት ከሃምሳ በመቶ በላይ ሊያስፈልገዉ ይችላል። ይህ ደግሞ ዛሬ ወያኔን ስለምንቃወም የምናወራዉ ተራ የፕሮፓጋናዳ ጨዋታ ሳይሆን የዛሬ አራት አመት ወያኔ ከበቂ ጥናትና ዝግጅት ዉጭ አባይን እገድባለሁ ብሎ ሲፎክር የዛሬዋ ቀን እንደምትመጣ አዉቀን በተከታታይ ያስጠነቀቅነዉ ማስጠንቀቂያ ስለሆነ ነዉ። ይህ ሁሉ የሚያሳየን ወያኔ አስቀያሚ መልኩን ለማሳመር ሲል ብቻ በኢትዮጵያ ህዝብ ገንዝብና ጉልበት የህፃን ጨዋታ መጫወቱን ነዉ። ሆኖም ዛሬ የሚያስፈራን ይህ ወያኔ የተጫወተበት መጠነ ብዙ የህዝብ ገንዘብ ብቻ ሳይሆን ግድቡን ሰርቶ ለመጨረስ ተጨማሪ ገንዘብ ለማግኘት የሚያደርገዉ አጉል መቅበዝበዝ ነዉ። በእኛ እምነት የህዳሴዉ ግደብ ተሰርቶ ሲያልቅ ኢትዮጵያን ከጥገኝነት ነፃ ማዉጣት ነዉ ያለበት እንጂ ሌላ አላስፈላጊ የሆነ የፖለቲካ ጥገኝነት ዉስጥ ይዞን መግባት የለበትም። ለዚህም ነዉ አርበኞች ግንቦት ሰባት ወያኔ፤ ግብፅና ሱዳን በአባይ ወንዛችን ላይ የሚሰራዉን ግድብ አስመልክቶ ደረስን የሚሉትን ስምምነት ምኑም ሳይደበቅ ለኢትዮጵያ ህዝብ በግልጽ መነገር አለበት እያለ ህዝብንም ወያኔንም የሚያስጠነቅቀዉ። የግብፅና የሱዳን መንግሰታት አገራቸዉ ዉስጥ ህዝብ የሚወዳቸዉ ወይም የሚጠላቸዉ መንግስታት ሊሆኑ ይችላሉ፤ ሆኖም ከዉጭ መንግሰታት ጋር በሚያደርጉት ምንም አይነት ድርድርና ዉይይት ሽንጣቸዉን ገትረዉ የሚቆሙት ለአገራቸዉ ጥቅም ብቻ ነዉ እንጂ ሌላ ከህዝብና ከአገር የተለየ አጀንዳ የላቸዉም። ኢትዮጵያ ዉስጥ ያለዉ አገዛዝ በተለይ ባለፉት ሃያ አራት አመታት ብቻዉን ስልጣን ተቆጣጥሮ የኖረዉ ህወሓት ግን ከኢትዮጵያ ህዝብ ዘለቄታዊ ጥቅም የተለየ የራሱ የሆነ አጀንዳ አለዉ። አርበኞች ግንባት 7 ህወሓትንና ይህንን ከህዝብና ከአገር የተለየ አጀንዳዉን የማቆሚያዉ ግዜ ዛሬ ነዉና ጉልበት ያለህ በጉልበትህ፤ ገንዘብ ያለህ በገንዘብህ፤ እዉቀት ያለህ ደገሞ በእዉቀትህ ነገ ሳይሆን ዛሬ ህዝባዊዉን ትግል ተቀላቀል እያለ አገራዊ ጥሪ ያስተላልፋል።

የሕወሓት መንግስት በኤርትራ ላይ የአየር ጥቃት ፈጸምኩ የሚለው ቅዠት ነው ተባለ * “እንኳን የአየር ድብደባ ይቅርና ሞቅ ያለ ጭብጨባም አልተሰማም

March 23,2015
ዘ-ሐበሻ) የሕወሓት መንግስት በኤርትራ በማይ እዳጋ የሚገኘው የሚሻዕ ወርቅ ማዕድን ካምፓኒ ላይ የአየር ጥቃት አደረስኩ ብሎ ከገለጸ በኋላ የኤርትራ መንግስት በኢትዮጵያ ምንም አይነት ጥቃት እንደደረሰበት የገለጸው ነገር አልነበረም:: አስመራ የሚገኙ የዘ-ሐበሻ ምንጮች እንደሚሉት ከሆነ በማይ እደጋ እንኳን የአየር ድብደባ ይቅርና ሞቅ ያለ ጭብጨባም አልተሰማም::
Vandalism
በኤርትራ ይህን የወርቅ ማዕድን የሚያወጣው የካናዳው የማዕድን አውጪ ድርጅት (NEVSUN RESOURCES LTD) ማምሻውን በድረገጹ (www.nevsun.com) ባወጣው መግለጫ የአየር ጥቃት እንደደረሰበት አልገለጸም:: ድርጅቱ ማርች 13 ቀን 2015 ልክ በማንኛውም መስሪያ ቤት እንደሚደርስ አደጋ መጠነኛ መሰባበር የደረሰበት ቢሆንም ጥገና አድርጎ ወደ ስራ እንደሚመለስ ገልጿል:: ይህ ጉዳት የደረሰበት የሕወሓት መንግስት እንደሚለው በአየር ጥቃት እንደሆነ ካምፓኒው ያስቀመጠው ነገር የለም::
የሕወሃት መንግስት ለምን ይህ ዜናን ማሰማት ፈለገ? የሚለውን ዘ-ሐበሻ ወደ አስመራ ምንጮቿ ጋር ደውላ የነበረ ሲሆን ምንጮቹም “የሕወሓት መንግስት ይህን ዜና ማሰራጨት የፈለገው ከፍራቻ የተነሳ ነው:: በዚህ በሚሻዕ የወርቅ ማዕድን ማውጫ በማንኛውም ድርጅት ውስጥ እንደሚፈጠር መጠነኛ የማሽኖች መሰባበር አደጋ መፈጠሩን የወያኔ ደህነንቶች መረጃ አላቸው:: የዚህ ድርጅት አካባቢ ደግሞ የኢትዮጵያ ነፃነት ታጋዮች የሚገኙበት ወታደራዊ ካምፖች አሉ:: አደጋው ከደረሰ ከአንድ ሳምንት በኋላ የሕወሓት መንግስት በኤርትራ ላይ የአየር ጥቃት እንደፈጸመ ማውራቱ ከገባበት ውጥረት የሕዝቡን አመለካከት ለመቀየር ነው” ብለዋል::
በተለይም በጎንደር አካባቢ በሕወሓት ወታደሮች እና በጎንደር ሕዝብ መካከል በተፈጠረው ውጥረት በዛሬው ዕለት 4 ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎና ሰሞኑንም ሕዝቡ ጠመንጃ እየያዘ ጫካ እየገባ በመሆኑ ይህን ለማስቀየስ የሕወሓት መንግስት የቀየሰው የፕሮፓጋንዳ ስልት ነው ሲሉ እነዚሁ ወታደራዊ ምንጮች ለዘ-ሐበሻ ገልጸዋል::

Sunday, March 22, 2015

ማንኛውም ተቃዋሚ ድርጅት ስርዓት ከሌለው ከርቸሌ እንከተዋለን የሚል ማስፈራርያ ኃይለማርያም ደሳለኝ አሰሙ

March 22,2015
ማንኛውም ተቃዋሚ ድርጅት ስርዓት ከሌለው  ከርቸሌ እንከተዋለን ይህንንም ለማድረግ አቅም አለን የሚል ማስፈራርያ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ አሰምተዋል

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ትናንትና በጅማ ከተማ ተገኝተው ይህን አድርገን ነጻነት አመጣን ዲሞክራሲን እየቀዳን ለህዝቡ አከፋፈልን አሉ። የጅማ ዩኒቨርስቲ ተማሪወች እንዳደረሱኝ መረጃ ከሆነ ሚኒ ኃይለማርያም ኔትወርክ አዘግተው በጅማ ዩኒቨርስቲ ውስጥ አድረዋል ።

ከንግግራቸው ውስጥ ፈገግ ካሰኘኝ ልለፍ ፣ሚኒ ኃይሌ እንዲህ አሉ ማንኛውም ተቃዋሚ ድርጅት ስርዓት ከለለው አቅም አለን ከርቸሌ እንከተዋለን አቤት አቤት ወግ መዓረጉ እንዳይቀር እኮ ነው የትኛው አቅም ነው ? ትልቅ መስኮት የሌለው ቤት ሰርቶ እስረኛ ማጠራቀሜውን ነው ፣ሠላማዊ ሰልፍ ሲወጣ ንጹህን ህዝብ በፖሊስ ማስደብደቡን ነው ?? ድንቄም አቅም አያ!!!!! ባዶ እጁን ከሚታገል ህዝብ ጋር መሳሪያ ታጥቆ አቅም አለን ሲል ከአንድ መሪ ተብሎ ከተወከለ አሻንጉሊት የማይጠብቅ የቂል ንግግር ።
የዩኒቨርስቲ ተማሪወችን ስብሠባ እንዳይካፈሉ አግደዋቸዋል ።

አቅማችሁን ለኤርትራ መንግስት አሳዩ እንጅ ከእኛ ላይ ቦተሊካችሁን አትንፉብን ።

ለማንኛውም በተያየዘ ዜና ላይ በኤርትራ የጦር ማካማች ሎጀስቲካ ላይ ያአደረሱት የአየር ጥቃት መግለጫው ጅማ ላይ ሳይሆን ቢቢሲ ወይም አልጀዚራ ላይ ቢሆን አሸናፊነትን አልያ ውድቀትን ሊያመጣ ይችላል እንላለን።

ሠላማዊ ትግላችን ነፃነት እስኪታወጅ እኩልነት እስኪሰፍን ይቀጥላል! – የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ

Marrch 22,2015
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በሃገራችን ኢትዮጵያ አስተማማኝና ዘለቄታዊ ሠላም፣ እኩልነት፣ ፍትህና፣ የፖለቲካ መረጋጋት ይሰፍን ዘንድ ቀና ራዕይ አንግበው በተሰባሰቡ ወጣት ኢትዮጵያውያን የተመሰረተ፤ በሃገራችን ብቸኛው በወጣቶች የተገነባና የሚመራ ንቅናቄ ነው። ንቅናቄአችን ላለፋት አመታት የንቅናቄውን አቅም ለማጐልበት፤ ሰፊና ጠንካራ መሰረት ያለው ሁለገብ ተቋም ለመገንባት፤ የድርጅታዊ መዋቅሩን ጨምሮ ሌሎች ወሳኝ መሰረታዊ የማስፋፋትና የማደራጀት ስራዎችን ሲሰራ ቆይቷል። በመሆኑም ዛሬ ንቅናቄያችን ከአምባገነኑ የህወሓት/ኢህአዴግ የደህንነት መረብ የፀዳ፤ እራሱን ከማንኛውም የውስጥና የውጭ ጥቃት በአስተማማኝ ሁኔታ የመከላከል ብቃት ያለው፤ በርካታ እንቅስቃሴዎችንና ዲሲፕሊኖችን በተቀናጀ መልኩ ማከናወን የሚችል ጠንካራ ተቋም መሆን ችሏል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ ከአጠቃላይ የህዝብ ብዛት ከ75% በላይ የሚሆነው ወጣቱ በመሆኑ፤ ይህ ወሳኝ የህብረተሰብ ክፍል የዲሞክራሲ ሥርዓትን ለመመስረትና ለማጐልበት በሚደረግ ትግል ውስጥ ግንባርቀደም ሚና የመጫወት ትውልዳዊ ሃላፊነት እንዳለበት በፅኑ ያምናል። በመሆኑም ንቅናቄአችን ይህን ፅኑ እምነት መሰረት በማድረግ፤ ወጣቱ ትውልድ ሃላፊነት የመረከብና በብቃት የመወጣት፤ እንዲሁም በተደራጀ መልኩ በጋራ የመሥራትና ለውጤት የመብቃት ሙሉ አቅሙ እንዲኖረው ለማስቻል መጠነ ሰፊ እቅዶችን ነድፎ በመተግበር፤ የወጣቱን እምቅ ችሎታና ብቃት በተግባር አስመስክሯል። ንቅናቄአችን ከተመሰረተበት ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ በርካታ ተግባራትን ያከናወነ ሲሆን፤ በተለይ በሃገር ውስጥና በውጭ ሃገራት የሚኖሩ ወጣቶችን ወደተመሰረተለት ታላቅ ራዕይ ለማምጣት የግንኙነትና የመረጃ ልውውጥ መረብ በመሆን፤ ብሎም በአለም ዙሪያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ወጣቶችን በስሩ በማደራጀትና በማንቃት ለሃገር ተቆርቋሪ ዜጋን በአስተማማኝ ሁኔታ መገንባት ችሏል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በሃገሪቱ ዲሞክራሲያዊ ስርአትን ለማስፈን በሚደረገው ትግል የበኩሉን አስተዋፅኦ ለማበርከትና የተነሳለትን ታላቅ ራዕይ እውን ለማድረግ፤ ከሌሎች የፖለቲካ፣ የሲቪክና፣ የሰባዊ መብቶች ድርጅቶች ጋር በመተባበርና ጠንካራ ስምምነቶችን በመመስረት በስፋት እየሰራ ይገኛል። ንቅናቄአችን በሰላማዊ የትግል ስልት በሃገራችን ለውጥ እንዲመጣ ከሚታገል ማንኛውም ተቋም ጋር በመተባበርና በመደገፍ በርካታ ተግባራትን ያከናወነ ሲሆን፤ በተለይ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ላለፉት ሦስት ተከታታይ አመታት ባካሄዷቸው ሠላማዊ መብትን የመጠየቅና የማስከበር እንቅስቃሴዎች የሚሠማውን ከፍተኛ አድናቆት እያስታወቀ፤ በቀጣይ ለሚያደርጉት ሠላማዊ እንቅስቃሴዎች ሁሉ፤ አባላቱን በማስተባበርና ሙሉ ሃይሉን በመጠቀም ስኬታማ እንዲሆን የሚሰራ መሆኑን ከወዲሁ ቃል በመግባት ያረጋግጣል። ከዚህም በተጨማሪ በወጣቶች የተገነባውን የሰማያዊ ፖርቲን በአዲስና በተቀናጀ መልኩ ድጋፍ ለመስጠት ሰፋ ያለ እቅድ ይዞ ተግባራዊ ለማድረግ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን በሙሉ ልብ ያረጋግጣል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ አባላት፤ እንዲሁም መላው የኢትዮጵያ ወጣት ሆይ፤ ዛሬ ሃገር እያለህ እንደሌለህ፤ መስራት እየቻልክ ተመፅዋች፤ ተምረህ ራስክን ማሻሻል እየቻልክ እድሉን ተነፍገህ፤ በችሎታህ ሳይሆን ለገዢው መደብ ባለህ ቀረቤታ ከሃገርህ ማግኘት የምትችላቸው እድሎችህን ሁሉ ተነጥቀህ፤ እጣ ፈንታህ በጥቂት ግለሰቦች በጐ ፈቃድ ስር ብቻ መውደቁን ካንተ በላይ የሚያውቀውና የሚገነዘበው የለም። በመሆኑም ሳትፈልግ የተጫኑብህ ምስቅልቅልና ጥልቅ ችግሮችን አስወግደህ፤ በተሻለ የህይወት ተስፋ የመተካት አቅሙም ጉልበቱም ያንተ ነውና፤ ከዛሬ ጀምሮ ቆርጠህ በመነሳት፤ ብሎም ከሰማያዊ ፓርቲ ጐን በፅናት በመቆምና ሙሉ ድጋፍ በመስጠት፤ እንዲሁም የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ትግልን የሚመራው አካል (ድምፃችን ይሰማ) አመራር ፍፁም ሠላማዊና በሳል መሆኑን ስለምትረዳው፤ በመሆኑም የሚቀርበው የአመራር ብቃት ነፃነትህን ለማስከበር በቂ የትግል ስትራተጂ እንደሆነ ስለሚታመን፤ የሚካሄደውን ትግልና የሚተላለፈውን የትግል መመሪያ በቅርበት በመከታተልና ተግባራዊ በማድረግ፤ ወደ ታሪካዊው የለውጥ ጐዳና በሙሉ ልብ ተቀላቅለህ ታሪካዊ ሃለፊነትህን ትወጣ ዘንድ፤ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በአክብሮት ሃገራዊ ጥሪውን ያቀርባል።
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄunnamed

ሦስት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ድንበር ሊያቋርጡ ሲሉ መያዛቸው ተሰማ

March 22,2015
‹‹ቤተሰቦቻቸው ምግብና ልብስ ማስገባታቸውን ሰምተናል›› ሰማያዊ ፓርቲ
semayawi63-300x252የሰማያዊ ፓርቲ የአደረጃጀት ጉዳይ ምክትል ኃላፊ የነበሩት አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ፣ የምክር ቤት አባል የነበረችው ወ/ሪት ኢየሩሳሌም ተስፋውና የሕዝብ ግንኙነት ኮሚቴ አባል አቶ ፍቅረ ማርያም አስማማው ትክክለኛ ቀኑ ባይታወቅም፣ ከሁለት ሳምንታት በፊት ድንበር አቋርጠው ኤርትራ በመግባት ግንቦት ሰባትን ሊቀላቀሉ ሲሉ መያዛቸው ተሰማ፡፡
የፓርቲው አባላት በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበው የ28 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ የተጠየቀባቸው መሆኑ እየተነገረ ቢሆንም መቼ፣ እንዴትና በማን ተይዘው የትኛው ፍርድ ቤት እንደቀረቡ ሪፖርተር ለማጣራት ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
በቁጥጥር ሥር ውለዋል ስለተባሉት ሦስቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጉዳይ ማብራሪያ እንዲሰጡ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የፓርቲው የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ የፓርቲያቸውን አባላት መታሰር የሰሙ ቢሆንም በቂ መረጃ እንደሌላቸው ገልጸዋል፡፡ የተጨበጠ ነገር ማግኘት እንደተሳናቸው የሚናገሩት አቶ ዮናታን፣ ቤተሰቦቻቸው ምግብና ልብስ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል (ማዕከላዊ) እንደወሰዱላቸው መስማታቸውን ጠቁመው፣ በአካል ያግኟቸው አያግኟቸው ግን እንዳላወቁ አስረድተዋል፡፡
እሳቸው ግን መቼ እንደታሰሩና የት እንደታሰሩ አለማወቃቸውንና ከ15 ቀናት በፊት ሌላ የፓርቲው ተወዳዳሪ ዕጩ መታሰሩን አስታውሰው፣ ምናልባት በዚያን ጊዜ ታስረው ሊሆን እንደሚችል ገምተዋል፡፡ በቁጥጥር ሥር የዋሉት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት የሁዳዴን ፆም በጸሎት ለማሳለፍ እንደሄዱ የሚናገሩት አቶ ዮናታን፣ የትና መቼ እንደሄዱ ግን ግልጽ አላደረጉም፡፡ በቁጥጥር ሥር ውለዋል የተባሉት አባላት ቀደም ባሉት ጊዜያት ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉና በፓርቲው ውስጥ ኃላፊነት የነበራቸው ቢሆንም፣ በአሁኑ ጊዜ ግን ከኃላፊነት ተነስተው አባል ብቻ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
አቶ ፍቅረ ማርያም ግን እስካለፈው ሳምንት ድረስ ሥራ ላይ እንደነበሩ አቶ ዮናታን ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ብዙ ሰዎች በየድረ ገጹ ብዙ ነገር ይጽፋሉ፡፡ ትክክለኛውን ነገር ግን ማግኘት አቅቶናል፤›› የሚሉት አቶ ዮናታን፣ ማዕከላዊ ምርመራ ሄደውም ሆነ ሰው ልከው ምንም ያገኙት ምላሽ ባለመኖሩ፣ እስከሚጣራ ድረስ አስተያየት መስጠት እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡
ጊዜው የምርጫ ወቅት በመሆኑ በጣም ሥራ እንደሚበዛባቸው ገልጸው፣ አሁን መናገር ባይችሉም ወደፊት ሁኔታውን ተከታትለው ይፋ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡
ምንም እንኳ ሦስቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በጎንደር በኩል አድርገው ወደ ኤርትራ ለመሻገር ሲንቀሳቀሱ ድንበር አካባቢ በፀጥታ ኃይሎች መያዛቸውን ፓርቲው ቢያውቀውም፣ የተፈጠረውን ጉዳይ ለምን ይፋ አያደርግም ተብሎ በማኅበራዊ ድረ ገጾች ወቀሳ እየቀረበበት ነው፡፡ በተለይ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች በቁጥጥር ሥር የዋሉትን የአባላቱን ጉዳይ በተመለከተ ወቅታዊ መረጃ አለመስጠታቸው ያበሳጫቸው የተለያዩ ግለሰቦች በተደጋጋሚ ጥያቄ ቢያቀርቡም፣ እስካለፈው ዓርብ ሌሊት ድረስ ምንም ዓይነት ምላሽ አላገኙም፡፡
ኤርትራ በመግባት ግንቦት ሰባት የተባለውን ድርጅት ለመቀላቀል ድንበር አካባቢ ተይዘዋል ስለተባሉት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በመንግሥት በኩልም እስከ ዓርብ ሌሊት ድረስ ምንም የወጣ መረጃ አልነበረም፡፡ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል ከተባሉ የመንግሥት ተቋማትም መረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡ ግንቦት ሰባት የተባለው ድርጅት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከሌሎች የአገር ውስጥና የውጭ ድርጅቶች ጋር በአሸባሪነት መሰየሙ አይዘነጋም፡፡