Sunday, March 22, 2015

ሠላማዊ ትግላችን ነፃነት እስኪታወጅ እኩልነት እስኪሰፍን ይቀጥላል! – የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ

Marrch 22,2015
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በሃገራችን ኢትዮጵያ አስተማማኝና ዘለቄታዊ ሠላም፣ እኩልነት፣ ፍትህና፣ የፖለቲካ መረጋጋት ይሰፍን ዘንድ ቀና ራዕይ አንግበው በተሰባሰቡ ወጣት ኢትዮጵያውያን የተመሰረተ፤ በሃገራችን ብቸኛው በወጣቶች የተገነባና የሚመራ ንቅናቄ ነው። ንቅናቄአችን ላለፋት አመታት የንቅናቄውን አቅም ለማጐልበት፤ ሰፊና ጠንካራ መሰረት ያለው ሁለገብ ተቋም ለመገንባት፤ የድርጅታዊ መዋቅሩን ጨምሮ ሌሎች ወሳኝ መሰረታዊ የማስፋፋትና የማደራጀት ስራዎችን ሲሰራ ቆይቷል። በመሆኑም ዛሬ ንቅናቄያችን ከአምባገነኑ የህወሓት/ኢህአዴግ የደህንነት መረብ የፀዳ፤ እራሱን ከማንኛውም የውስጥና የውጭ ጥቃት በአስተማማኝ ሁኔታ የመከላከል ብቃት ያለው፤ በርካታ እንቅስቃሴዎችንና ዲሲፕሊኖችን በተቀናጀ መልኩ ማከናወን የሚችል ጠንካራ ተቋም መሆን ችሏል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ ከአጠቃላይ የህዝብ ብዛት ከ75% በላይ የሚሆነው ወጣቱ በመሆኑ፤ ይህ ወሳኝ የህብረተሰብ ክፍል የዲሞክራሲ ሥርዓትን ለመመስረትና ለማጐልበት በሚደረግ ትግል ውስጥ ግንባርቀደም ሚና የመጫወት ትውልዳዊ ሃላፊነት እንዳለበት በፅኑ ያምናል። በመሆኑም ንቅናቄአችን ይህን ፅኑ እምነት መሰረት በማድረግ፤ ወጣቱ ትውልድ ሃላፊነት የመረከብና በብቃት የመወጣት፤ እንዲሁም በተደራጀ መልኩ በጋራ የመሥራትና ለውጤት የመብቃት ሙሉ አቅሙ እንዲኖረው ለማስቻል መጠነ ሰፊ እቅዶችን ነድፎ በመተግበር፤ የወጣቱን እምቅ ችሎታና ብቃት በተግባር አስመስክሯል። ንቅናቄአችን ከተመሰረተበት ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ በርካታ ተግባራትን ያከናወነ ሲሆን፤ በተለይ በሃገር ውስጥና በውጭ ሃገራት የሚኖሩ ወጣቶችን ወደተመሰረተለት ታላቅ ራዕይ ለማምጣት የግንኙነትና የመረጃ ልውውጥ መረብ በመሆን፤ ብሎም በአለም ዙሪያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ወጣቶችን በስሩ በማደራጀትና በማንቃት ለሃገር ተቆርቋሪ ዜጋን በአስተማማኝ ሁኔታ መገንባት ችሏል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በሃገሪቱ ዲሞክራሲያዊ ስርአትን ለማስፈን በሚደረገው ትግል የበኩሉን አስተዋፅኦ ለማበርከትና የተነሳለትን ታላቅ ራዕይ እውን ለማድረግ፤ ከሌሎች የፖለቲካ፣ የሲቪክና፣ የሰባዊ መብቶች ድርጅቶች ጋር በመተባበርና ጠንካራ ስምምነቶችን በመመስረት በስፋት እየሰራ ይገኛል። ንቅናቄአችን በሰላማዊ የትግል ስልት በሃገራችን ለውጥ እንዲመጣ ከሚታገል ማንኛውም ተቋም ጋር በመተባበርና በመደገፍ በርካታ ተግባራትን ያከናወነ ሲሆን፤ በተለይ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ላለፉት ሦስት ተከታታይ አመታት ባካሄዷቸው ሠላማዊ መብትን የመጠየቅና የማስከበር እንቅስቃሴዎች የሚሠማውን ከፍተኛ አድናቆት እያስታወቀ፤ በቀጣይ ለሚያደርጉት ሠላማዊ እንቅስቃሴዎች ሁሉ፤ አባላቱን በማስተባበርና ሙሉ ሃይሉን በመጠቀም ስኬታማ እንዲሆን የሚሰራ መሆኑን ከወዲሁ ቃል በመግባት ያረጋግጣል። ከዚህም በተጨማሪ በወጣቶች የተገነባውን የሰማያዊ ፖርቲን በአዲስና በተቀናጀ መልኩ ድጋፍ ለመስጠት ሰፋ ያለ እቅድ ይዞ ተግባራዊ ለማድረግ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን በሙሉ ልብ ያረጋግጣል።
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ አባላት፤ እንዲሁም መላው የኢትዮጵያ ወጣት ሆይ፤ ዛሬ ሃገር እያለህ እንደሌለህ፤ መስራት እየቻልክ ተመፅዋች፤ ተምረህ ራስክን ማሻሻል እየቻልክ እድሉን ተነፍገህ፤ በችሎታህ ሳይሆን ለገዢው መደብ ባለህ ቀረቤታ ከሃገርህ ማግኘት የምትችላቸው እድሎችህን ሁሉ ተነጥቀህ፤ እጣ ፈንታህ በጥቂት ግለሰቦች በጐ ፈቃድ ስር ብቻ መውደቁን ካንተ በላይ የሚያውቀውና የሚገነዘበው የለም። በመሆኑም ሳትፈልግ የተጫኑብህ ምስቅልቅልና ጥልቅ ችግሮችን አስወግደህ፤ በተሻለ የህይወት ተስፋ የመተካት አቅሙም ጉልበቱም ያንተ ነውና፤ ከዛሬ ጀምሮ ቆርጠህ በመነሳት፤ ብሎም ከሰማያዊ ፓርቲ ጐን በፅናት በመቆምና ሙሉ ድጋፍ በመስጠት፤ እንዲሁም የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ትግልን የሚመራው አካል (ድምፃችን ይሰማ) አመራር ፍፁም ሠላማዊና በሳል መሆኑን ስለምትረዳው፤ በመሆኑም የሚቀርበው የአመራር ብቃት ነፃነትህን ለማስከበር በቂ የትግል ስትራተጂ እንደሆነ ስለሚታመን፤ የሚካሄደውን ትግልና የሚተላለፈውን የትግል መመሪያ በቅርበት በመከታተልና ተግባራዊ በማድረግ፤ ወደ ታሪካዊው የለውጥ ጐዳና በሙሉ ልብ ተቀላቅለህ ታሪካዊ ሃለፊነትህን ትወጣ ዘንድ፤ የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ በአክብሮት ሃገራዊ ጥሪውን ያቀርባል።
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄunnamed

No comments: