Thursday, December 17, 2015

“ፕሮፌሰር፣ ጄኔራል” ሳሞራ

December 17,2015
የቻይና ደም-መላሽ!
samoray
ረቡዕ በተሰማው ዜና መሠረት የቻይናው ቲያንጂን የቴክኖሎጂና ትምህርት ዩኒቨርሲቲ ለሳሞራ የኑስ የክብር ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ሰጥቷል፡፡
ሚያዚያ 1999 የዖጋዴን ብሔራዊ ነጻ አውጪ ግምባር በክልሉ በሚገኝ የነዳጅ ፍለጋ ቦታ ላይ ባደረሰው ጥቃት ከ70 በላይ ንጹሃንን በገደለበት ወቅት ዘጠኝ ቻይናውያን ከሞቱት መካከል ነበሩ፡፡
በትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግምባር አዛዥነት በየጊዜው በዖጋዴን ሕዝብ ላይ የሚደርሰውን ጥቃት ሲቃወም የነበረው ኦብነግ ለወሰደው ድንገተኛ እርምጃ በሟቹ መለስ የሚመራው ህወሃት በክልሉ አምስት ቦታዎች ማለትም በፊቅ፣ ቆራሄ፣ ጎዴ፣ ዋርድሄር እና ደጋሃቡር ዘግናኝ የሆነ የመልሶ ማጥቃት ጭፍጨፋ በነዋሪው ሕዝብ ላይ አድርሷል፡፡
የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት (ሂውማን ራይትስ ዎች) ባወጣው ዘገባ መሠረት ኦብነግ ላደረሰው የአጸፋ መልስ እና ታጣቂዎችን ለመደምሰስ በሚል ህወሃት ያዘመተው ጦር በተደጋጋሚ በሰላማዊው ሕዝብ ላይ ፍጹም ጨካኝና ዘግናኝ ዕልቂት ፈጽሟል፡፡
samorayየመልሶ ማጥቃቱን ዘመቻ ለማካሄድ ጂጂጋ ላይ የክልሉ የደኅንነት ኃላፊዎች ስብሰባ ባደረጉበት ወቅት የመለስ የጸጥታ አማካሪ አባይ ጸሃዬ እና ሳሞራ የኑስ በጥቃቱ ዕቅድ አወጣጥ ላይ ተገኝተው እንደነበር ታማኝ ምንጮቹን ጠቅሶ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ ያስረዳል፡፡
ከዚያም በ1999 ሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ አቶ መለስ መጠነ ሰፊ የመልሶ ማጥቃት ዘመቻ እንዲካሄድ ትዕዛዝ አስተላለፉ፡፡ የዖጋዴን ሕዝብ ፍዳውን በላ፤ እንደ ቅጠል ረገፈ፤ ዕድሜያቸው ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጃገረዶች፣ ሴቶች አዛውንቶችንም ጨምሮ ተደፈሩ፡፡ ህጻናት ወንዶችም ሳይቀሩ የዚህ ሰለባ ሆነዋል፡፡
የቀድሞው የቻይና መሪ ማዖ ሴቱንግ ሽምቅ ተዋጊዎችን ስለማጥፋት የተናገሩት ቃል በመለስ ፊት አውራሪነት ተፈጸመ፡፡ “ዓሣ በባህር እንደሚዋኝ ሽምቅ ተዋጊም በሕዝቡ መካከል መንቀሳቀስ አለበት፤ (ሽምቅ ተዋጊን ለማጥፋት ካስፈለገ ዓሣው ያለበትን ባህር ማድረቅ ነው)” ያሉት የማዖ ቃል በመለስ ትዕዛዝ በሳሞራ የኑስና ሌሎች የህወሃት አጋፋሪዎች ተፈጸመ፡፡
ውለታ የማይረሱት ቻይናውያን የትምህርት ደረጃው በውል የማይታወቀውን በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አሉ ከሚባሉት የጦር አካዳሚዎች ሥልጠና ስለመውሰዱ ምንም ማስረጃ ላልተገኘለት “ቻይናዊ ጄኔራል ደምመላሽ” ባቋራጭ “የላቀ ምሁርነት” አጎናጸፉት፡፡
ውለታን መመለስ ከሆነ አይቀር እንዲህ ነው፡፡
ማዖ ነኝ ከቲያንጂን

No comments: