Monday, November 9, 2015

ከትናንት በፊት የተቀሰቀሰው ጦርነት ሮቢት፣ ጎንደሮች ማሪያምና ጋባ በተባሉ አካባቢዎችም ጭምር ዛሬም ለሦስተኛ ቀን ቀጥሎ ውሏል፡፡

November 9,2015
(የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ)
ከጎንደር 20 ኪሎ ሜትር ርቀት ከምትገኘው ማውራ መንደር በገበሬው ህዝብና በህወሓት ልዩ ኃይል መካከል ከትናንት በፊት የተቀሰቀሰው ጦርነት አድማሱን አስፍቶ ሮቢት፣ ጎንደሮች ማሪያምና ጋባ በተባሉ አካባቢዎችም ጭምር ዛሬም ለሦስተኛ ቀን ቀጥሎ ውሏል፡፡
ቅዳሜ ዕለት ጥቅምት 27 2008 ዓ.ም ከ200 በላይ የህወሓት ልዩ ኃይል አባላት በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ተደማጭነት ያላቸውንና እንደ መሪ የሚታዩትን የአገር ሽማግሌዎች በቁጥጥር ስር ለማዋል ወደ ማውራ ለመግባት ሞክረው የአካባቢው ገበሬ በጠቅላላ በአንድነት ሆ ብሎ ታጥቆ በመውጣት ወደ ቀዬው አላስደርስም በማለቱ ሲሆን ግጭቱ የተቀሰቀሰው ወደ ማውራ ከሄዱት 200 የህወሓት ልዩ ኃይል አባላት ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ከገበሬዎቹ በተተኮሰባቸው ጥይት ሙትና ቁስለኛ ሆነዋል፡፡ 
ማውራ ላይ የተቀሰቀሰው ጦርነት ወደ ሌሎች አጎራባች መንደሮችም በመቀጣጠል ተስፋፍቶ በጎንደሮች ማርያም፣ ሮቢትና ጋባ በጎንደር ገበሬዎችና በህወሓት ልዩ ኃይሎች መካከል ደም ባፋሰሰ ሁኔታ እየተካሄደ ይገኛል፡፡ በተለይም ደግሞ የጎንደሮች ማርያም ገበሬ ከፍተኛ ቁጥር ያለውን የህወሓት ልዩ ኃይል ጦር በመክበብ መውጫ ቀዳዳ አሳጥቶ ጭፍጭፎ አስቀርቶታል፡፡
በማውራ የተከፈተው ጦርነት ትናንት ቀኑን ሙሉ ውሎ እስከ ምሽቱ ሶስት ሰዓት ያለምንም ፋታ መቀጠሉን ምንጮቻችን ገልፀዋል፡፡ ዛሬ ከማለዳ ጀምሮ እስከ ረፋዱ አራት ሰዓት ድረስ በማውራ ገበሬዎችና በህወሓት ልዩ ኃይሎች መካከል ከባድ ውጊያ ተካሂዷል፡፡ 
በአሁኑ ሰዓት የማውራና ሌሎች መንደሮች ነዋሪ የሆኑ ወንዶች በጠቅላላ ታጥቀው ባቅራቢያቸው ወደሚገኝ ጫካ የገቡ ሲሆን መንደሮቹ ከፍተኛ ቁጥር ባለው የህወሓት ፌደራል ፖሊስ ጦር ተወረዋል፡፡ በመንደሮቹ ውስጥ የቀሩት ህፃናትና ሴቶች ብቻ ናቸው፡፡ አስገድዶ መድፈር፣ ግድያ፣ ግርፋትና እስር በፖሊሶቹ እየተፈፀመባቸው ይገኛሉ፡፡ መፈናቀልም ተፈጥሮ ብዙ ጎጆዎች ውስጣቸው ኦና ሆኖ በሮቻቸው ተዘግተዋል፡፡
በውጊያ ከገበሬዎች በኩል 1 ተዋጊ ብቻ እስካሁን ተሰውቷል ሌሎችም የቆሰሉ አሉ እየተባለ ነው፡፡ በተጨማሪም ቁጥራቸው ያልታወቁ ህፃናትና ሴቶች ተገድለዋል፡፡ 
የህወሓት አገልጋይ የሆነው ብአዴን አባል የሆኑት የጎንደር ሹሞች ነፍጥ አንስተው እየተፋለሙ ከሚገኙት ገበሬዎች ጋር በስልክ ለመደራደር ሞክረው "እንኳን ለእናንተ ልንሸነፍ እነ ገዛኸኝ ወርቄንም አርበድብደናቸዋል፡፡" የሚል ምላሽ እንዳገኙ ታውቋል፡

No comments: