Saturday, April 23, 2016

በወገኖቻችን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ሰቆቃ፤ ሞትና ስደት ለማስቆም ሁላችንም ጠንክረን እንታገል!!!

April 23,2016
የአርበኞ ግንቦት 7 ሳምንታዊ ርዕስ አንቀጽ
አፕሪል 22 2016
ህወሃት ሥልጣን ከተቆጣጠረበት 1983 ጀምሮ በህዝባችንና በአገራችን ላይ እየተፈጸመ ያለው ወንጀል ቁጥር ስፍር የለውም። እስከ አምናና ካቻምና የሆነውን እንኳ ትተን በዚህ በያዝነው አመት ብቻ በወገኖቻችንና በአገራችን ላይ ከተፈጸሙት ወንጀሎች ጥቂቶቹን ብናስታውስ የሚከተሉትን እናገኛለን ፤
በጎንደር በኩል አገራችንን ከሱዳን ጋር የሚያዋሰነውን ለምና ድንግል መሬት ቆርሶ ለርካሽ የፖለቲካ ጥቅም ማራመጃ ለሱዳን አሳልፎ ለመስጠት የተፈጸመውን ስውር ስምምነት የተቃወሙ በርካታ ወገኖቻችን ላይ ከፍተኛ ስቃይና እንግልት ተፈጽሞአል።
ለዘማናት ተዋህዶ የኖረውን የቅማንትና የአማራ ህዝብ በማንነት ጥያቄ ለመከፋፈልና ለማጋጨት በተደረገው ደባ በርካታ ንጹሃን ዜጎች ህይወት እንዲቀጠፍ ተደርጎአል።
የወልቃይት ህዝብ ያነሳውን የማንነት ጥያቄ ለማዳፈን ሲባል ለዓመታት ወደ ክልሉ ተሰዶ በሠላም ሠርቶ የሚኖረውን የትግራይ ተወላጅ በማስታጠቅና በማነሳሳት በሁለቱ መሃል ጥላቻና ቂም እንዲረገዝ ተደርጎአል።
በደቡብ የአገራችን ግዛት የማንነት ጥያቄ ያነሱና ወያኔ ለሚያካሂደው የስኳር ምርት ከመሬታቸው አንፈናቀልም ባሉ የኦሞ ሸለቆ ነዋሪዎች ላይ ግዲያና እስር ተፈጽሞአል። በባሪያ ፈንግል ዘመን ይካሄድ በነበረ አዋራጅ ሁኔታ ዜጎች ራቁታቸውን እጅና አንገታቸውን በገመድ ታስረው በወታደር መኪና ሲጓጓዙ ታይቶአል።
በአርባምንጭ ፤ በቴፕና ማጂ በአገዛዙ ዘረፋና ሙስና የተማረሩና ተቃውሞ ያነሱ ዜጎች ሽብርተኛ ተብለው ተደብድበዋል፤ ተገድለዋል፤ ታስረዋል፤ ከሥራቸው ተፈናቅለው ሜዳ ላይ ተጥለዋል።
በብዙ ድካምና ጥረት ያገኙትን ገንዘብ አጠራቅመው ለራሳቸውና ለቤተሰቦቻቸው መጠለያ ቤት በአነስተኛ ቦታ ላይ የገነቡ በርካታ ዜጎች የሠሩት ቤት ለከተማ ውቤት አይመጥንም ተብሎ በላያቸው ላይ በቡልዶዘር እንዲፈርስ ተደርጎ ለበረንዳ አዳሪነት ተዳርገዋል።
በአፋርና በሱማሌ ክልሎችም እንዲሁ ከመሬት ነጠቃ ጋር በተያያዘ ወንጀል ከመሬታችን አንፈናቀልም ያሉ ዜጎች ታስረዋል ፤ ተገድለዋል ፤ ለስደት ተዳርገዋል።
ሃሳባቸውን በነጻነት ለመግለጽ የሞከሩ፤ የአገዛዙን ዘረኛ አካሄድና ዘረፋ የተቃወሙ በርካታ ዜጎች በተቀነባበረ የሽብርተኝነት ወንጀል እየተከሰሱ ዝብጥያ ወርደዋል፤ እስር ቤት ውስጥ እያሉም በጨካኞችና አረመኔዎች አሰቃቂ ድብደባና ማሰቃያ እርምጃ ተፈጽሞባቸዋል።
ለወያኔ ባለሥልጣናት ከፍተኛ የሃብት ምንጭ የሆነውን የመሬት ዘረፋ በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ሥም ለማካሄድ የተደረገውን እንቅስቃሴ ተቃውመው አደባባይ በወጡ የኦሮሚያ አካባቢ ተወላጆች ላይ መጠነ ሰፊ የሆነ ጭፍጨፋ በአጋዚ ጦር እንዲካሄድ ተደርጎአል። በዚህም የተነሳ ከ400 በላይ ዜጎች ህይወት ተቀጥፎአል፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ከትምህር ገበታቸው ታድነው እስር ቤት ተወርውረዋል፤ ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ ዜጎች አካባቢያቸውን ለቀው ተሰደዋል።
ህዝባችን ከፍተኛ የረሃብ አደጋ አንዣቦበት አለም አቀፍ ለጋሾች ህይወት ለማዳን በሚራወጡበት ወቅት ለባለሥልጣናቱ መኖሪያ ዘመናዊ ቪላ ለመገንባት ከመንግሥት ካዜና በብዙ መቶ ሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ወጪ እንዲሆን ተደርጎአል።
የወያኔ መሪዎች ከደሃው ህዝብ ጉሮሮ እየዘረፉ ወደ ውጪ ከሚያሸሹት በቢሊዮን ዶላር የሚገመት ገንዘብ ውስጥ አምስት ሚሊዮን የእንግሊዝ ፓውንድ በአንድ የወያኔ አባል በሻንጣ ተይዞ እንግሊዝ አገር ለማስገባት ሲሞከር ተይዞአል።
በቅርቡም በቻይና አየር ማረፊያ በተመሳሳይ መንገድ የተገኘ ብዙ ሺህ የአሜሪካን ዶላር ለሥርዓቱ ቅርበት እንዳለው በተገለጸ ሰው እጅ ተገኝቶ በቁጥጥር ሥር ከዋለ ቦኋላ በባለሥልጣናቱ ጣልቃገብነት መለቀቁ ተዘግቦአል።
ይህ ሁሉ ሰቆቃና ግዲያ መንግሥት ነኝ በሚለው የህወሃት አገዛዝ በወገኖቻችንና በአገራችን ላይ መፈጸሙ አንሶ ድንበር አቋርጠው ገቡ የተባሉ ታጣቂ ሃይሎች ከሰሞኑ በጋምቤላ ክልል ከ230 በላይ ወገኖቻችንን ገድለው ከ150 በላይ ህጻናትን ከእናቶቻቸው ጉያ ነጥቀው ተሰውሮአል። በጣም የሚያሳዝነውና አገራችን ያለቺበትን የውድቀት ደረጃ ፍንትው አድርጎ የሚያሳየው ደግሞ በሁለት ቀናት ዕድሜ እንዲህ አይነት ጭፍጨፋ በወገኖቻችን ላይ ፈጽሞ ወደመጣበት የተመለሰ የውጭ ታጣቂ ሃይል ማንነት እስከዛሬ አልታወቀም መባሉ ነው ።
ሌላው አሳዛኝ ክስተት በአገራቸው ተስፋ የቆረጡና ኑሮ የምድር ስኦል ሆኖባቸው በስደት የተለያዩ አፍሪካ አገሮች ውስጥ በመንከራተት ላይ ከነበሩ ኢትዮጵያዊያን መካከል በጀልባ ወደ አውሮጳ ለማምለጥ ሲጓዙ ከ200 በላይ የሚሆኑት ሜዲትራንያን ባህር ውስጥ ሰጥመው የአሳ እራት ሆነዋል። በታንዛኒያ በኩል ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመግባት ሲሞክሩ የተያዙ በርካታ ወጣቶች ለረጅም ወራት በታንዛኒያ እስር ቤት ውስጥ ሲማቅቁ ቆይተው ከተለቀቁ ቦኋላ የታንዛኒያ መንግሥት አገልግሎቱን እንደጨረሰ ዕቃ ኬንያ ጠረፍ ላይ ወስዶ አራግፎአቸዋል። በእርምጃው ደስተኛ ያልሆነው የኬንያ ፖሊስም ወጣቶቹን አፍኖ ወደ መጡበት ታንዛኒያ ምድር በመመለስ አውላላ ሜዳ ላይ አራግፎአቸው ተመልሶአል። አዛኝና ተቆርቋሪ መንግሥት የሌላቸው እነዚህ ወጣቶች በማያውቁት አገር ለጅብ እራት አሳልፈው ተሰጥተዋል ። ይህ ሁሉ መከራና ስቃይ በወገኖቻችን ላይ ሲፈራረቅ ህዝባችንን ለዚህ ሰቆቃ የዳረጉት ወያኔና ግብረአበሮቹ ከህዝብ በዘረፉት ገንዘብ ፎቅ ላይ ፎቅ በመገንባት በዶላር እያከራዩ ሃብት ላይ ሃብት ያከማቻሉ። ልጆቻቸውንና የቅርብ ዘመዶቻቸውን በዲፕሎማቲክ ፓስፖርት ከአገር እየሸኙ ውድና ምርጥ በተባሉ ትምህርት ቤቶች ያስተምራሉ ።
አርበኞች ግንቦት 7 በወገኖቻችን ላይ የሚፈጸመው ሰቆቃ ፤ ግዲያ ፤ እስርና ስደት መቆም የሚችለው የአፈናው ፤ የግዲያው እና የስደቱ ምንጭ የሆነው የወያኔ አገዛዝ ከህዝባችን ጫንቃ ላይ ለአንዴና ለመጨረሻ መወገድ ሲችል ብቻ ነው ብሎ ያምናል። ለአገሩና ለወገኑ የሚቆረቆር ማንኛውም ዜጋ የዚህን ዘረኛና ከፋፋይ አገዛዝ የሥልጣን ዕድሜ ለማሳጠር የተጀመረውን ሁለገብ ትግል አቅሙ በፈቀደ መንገድ ሁሉ እንዲያግዝና ትግሉን እንዲቀላቀል አርበኞች ግንቦት 7 ወገናዊ ጥሪውን ያቀርባል። ሁላችንም ጠንክረን በመታገል በአገራችንንና በወገኖቻን ላይ የሚደርሰውን ሰቆቃ፤ ግዲያና ስደት ማስቆም እንችላለን።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

No comments: