Tuesday, April 19, 2016

በጋሚቤላ ወገኖቻችን ላይ ለደረሰው ጭፍጨፋ ተጠያቂው ወያኔ ነው!!!

April 19,2016
ባለፈው ዓርብ ሚያዚያ 7 ቀን 2008 ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች ድንበር ጥሰው በመግባት በላሬና ጃካዋ ወረዳዎች በሚኖሩ የኑዌር ወገኖቻችን ላይ ጭፍጨፋ ማካሄዳቸውን በአገዛዙ ቁጥጥር ሥር ያሉ ሚዲያዎች ጭምር ዘግበዋል። 

ህወሃት ሥልጣን ከተቆጣጠረ ወዲህ በጋምቤላ ክልል ነዋሪ በሆኑ ወገኖቻችን ላይ እንዲህ አይነት የጅምላ ጭፍጨፋ ሲካሄድ ይህ የመጀመሪያው አይደለም። በ1996 የህወሃት ልዩ ጦር የተሳተፈበት የዘር ማጥፋት ወንጀል በአኝዋክ ተወላጆች ላይ ተካሂዶ ከ400 በላይ ሰላማዊ ዜጎች ህይወታቸው ተቀጥፎአል። በወቅቱ የፈደራል ጉዳዮች ሃላፊ የነበረው አባ ጸሃይና ሌሎች ቱባ ቱባ የመከላኪያና የደህንነት ባለሥልጣናት እጃቸው እንደነበረበት ቢታወቅም እስከዛሬ ድረስ አንዳቸውም ለፍርድ አልቀረቡም። ከ1996ቱ ጭፍጨፋ በተጨማሪም በክልሉ የሚካሄደውን የመሬት ቅሚያ የተቃወሙ፤ ከአያት ቅድሜ አያቶቻችው የወረሱትንና እትብታቸው ከተቀበረበት በሃይል አንፈናቀልም ያሉ በርካቶች ተገድለዋል ፤ ተደብድበዋል፤ ለእስርና ለስደት ተዳርገዋል። ከእስርና ከስደት ያመለጡ በርካቶችም በገዛ መሬታቸው ለአዳዲሶቹ ባለሃብቶች ጭሰኛ ሆነዋል አለያም ለጎዳና ተዳዳሪነት ተዳረገዋል። ይህ ሁሉ ግፍና መከራ አልበቃ ብሎ ከሰሞኑ ደግሞ "ማንነታቸው ያልታወቁ" የተባሉ ታጣቂዎች ከጎሬቤት ደቡብ ሱዳን ድንበር ተሻግረው ከ208 በላይ የኑዌር ተወላጅ ወገኖቻችንን ጨፍጭፈው ወደመጡበት ተመልሰዋል። ከተጨፈጨፉት ወገኖቻችን ከሃምሳ በላይ የሆኑት ህጻናት ሲሆኑ ሴቶችና አቅመ ደካማ የሆኑ ሽማግለዎች ቁጥርም ቀላል አይደለም። 

ለመሆኑ ወያኔ "ማንነታቸው ያልታወቀ" የሚላቸው እነዚህ ታጣቂዎች ድንበር አቋርጠው 40 እና 50 ኪሎ ሜትር ወደ ውስጥ ገብተው ምንም መሣሪያ ባልታጠቁ ወገኖቻችን ላይ እንዲህ አይነት ጭፍጨፋ ሲፈጽሙ የአገር ዳር ድንበር ለመጠበቅ የተቀጠረው መከላኪያ ሠራዊት አንዳችም የአጸፋ እርምጃ እንዳይወስድ ካምፕ ውስት ተዘግቶ እንዲቀመጠ የተደረገው ለምንድነው?የጥቃት ፈጻሚዎቹ ማንነትና የመጡበት ቦታ እንኳ በትክክል እንዳይታወቅና ተድበስብሶ እንድቀርስ የተፈለገው በምን ምክንያት ነው? የአገር ዳር ድንበርና የዜጎችን ደህንነት በአስተማማኝ የሚጠብቅ በሌለበት የአካባቢው ህዝብ ከጥንት ጀምሮ እራሱንና ንብረቱን የሚከላከልበት ነፍሰ ወከፍ መሣሪያ እንዲፈታ ማድረግ ለምን አስፈለገ?የሚሉ ጥያቄዎች ከጭፍጨፋው በስተጀርባ የወያኔ እጅ እንዳለበት ማሳያ ናቸው። ወያኔ የአገዛዝ ዕድሜውን ለማራዘም አንዱን ብሄር ከሌላው በማጋጨት በመካከላቸው መተማመን እንዳይኖር ፍርሃትና ጥርጣሬ እንዲነግስ ሲያደርግ የኖረ ቡድን ነው። ከዚህም የተነሳ "ድንበር ተሻግሮ ጥቃት ፈጸመ የተባለው ታጣቂ " ጋምቤላ ውስጥ የሚካሄደውን የመሬት ቅርመታ የሚቃወሙትን ለማዳከም ሆን ተብሎ የጋምቤላንና የጎሬቤት ሱዳን ዜጎችን ለማጋጨት ከሚጠነስሰው ተንኮል ውጭ ሊሆን አይችልም። በክልሉ የሰፈረው የአገሪቱ መከላኪያ ሠራዊት ምንም አይነት እርምጃ ሳይወስድ ከ208 በላይ ዜጎችን የጨፈጨፉ ታጣቂዎች ከመቶ በላይ ንጹሃን ዜጎችን አግተው በሰላም ወደ መጡበት መመለስ መቻላቸው ለዚህ ዋቢ ምስክር ነው።
አርበኞች ግንቦት 7 ምንም አይነት መንግሥታዊ ከለላና ጥበቃ በሌለው የኑዌርና የአኝዋክ ህዝባችን ላይ የተፈጸመውን ይህንን ዘግናኝ ጭፍጨፋ አጥብቆ ያወግዛል። የመንግሥትን ሥልጣን ለሃብት ዘረፋ ብቻ እየተጠቀመ ዜጎች ለእንዲህ አይነት ዕልቂት እንዲጋለጡ የአደረገው የወያኔ አገዛዝ በጋምቤላ ለደረሰው ለዚህ እልቂት ሙሉ በሙሉ ተጠያቂ እንደሆነም ለመላው የአገራችን ህዝብና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ማስታወቅ ይወዳል።


ንቅናቄያችን አርበኞች ግንቦት 7 በዜጎቻችን ላይ ለደረሰው ለዚህ የጭፍጨፋ ወንጀል ተጠያቂ የሆኑ የወያኔ መሪዎች ህግ ፊት እንዲቀርቡ የጀመረውን ሁለገብ ትግል አጠናክሮ ይቀጥላል። ፍትህ እኩልነትና ነጻነት በአገራችን እንዲሰፍን የሚታገሉ የዲሞክራሲ ሃይሎች ሁሉ በህዝባችን ላይ የሚፈጸመውን ጭፍጨፋና ሰቆቃ ለማስቆም በተናጠል ከሚያካሂዱት ትግል ወደ ትብብርና የጋራ ግንባር እንዲመጡ የሚያደርገውን ጥረት እንደሚገፋበት ይገልጻል። ለዚህ ጥረት መሳካትም ጉዳዩ የሚመለከታቸው ወገኖች ቀናና ያላሰለሰ ትብብር እንዲያሳዩ ወገናዊ ጥሪውን ያቀርባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

No comments: