Thursday, March 26, 2015

ትጥቅ ትግል ፣ ሰላማዊ ትግል ፣ ሁለገብ ትግል

March 26,2015
(አቶ ዮናታን ተስፋዬ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ ናቸው። ይህ ጽሁፍም ፓርቲን ወክለው ሳይሆን ራሳቸውን ወክለው የጻፉት ነው)
ወቅታዊ አጀንዳ እና በቁንፅል የሚተው ባይሆንኝ ነው – በትግስት አንቡልኝyonatan
ጭቆና ሲበዛ ሰዎች ብዙ መንገድን ተጠቅመው መታገል ይሻሉ፡፡ የጭቆናውን ቀንበር ለመስበር ጨቋኙን ከመግደል አንስቶ ራስን እስከማቃጠል ድረስ የሚደርሱ በርካታ መንገዶችን ሊጠቀሙ ይችላሉ፡፡ ከአገዛዝ ሰንሰለት ራስን ነፃ ለማድረግ ብዙዎች ተጨንቀው ማሰብም አይፈልጉም፡፡ በቃ ገዢውን ወዲያ አሽቀንጥሮ ጥሎ ነፃ መሆን (end of the story end of the oppression)! በተፈጥሮ ነፃ ሆኖ የተፈጠረ ሰው በሂደት እጅግ በተወሳሰበ የህይወት መስተጋብር ውስጥ ቢኖርም የጭቆናው ለከት ሲያልፍ ግን ቀስቃሽ ሳያሻው እንደቡድንም ይሁን በግል በነሲብ ወደ ነፃነት ትግል መግባቱ አይቀርም፡፡ ነፃነት ከብዙ ምክንያታዊነትም በላይ የስሜት ሀይሉ ከፍተኛ ገፊ በመሆኑ ለነፃነት የሚደረገውም እንቅስቃሴ በራሱ ድንገታዊነት ይበዛዋል፡፡ ‘መቼ’ እና ‘እንዴት’ን አያጠይቅም፤ ‘ለምን’ የሚለው ብቻ በቂው ነው፡፡
እንግዲህ እዚህ ጋር ነው የነፃነት ትግል መሪዎች ሚና ወሳኝ የሚሆነው፡፡ ጭቆናን ከምክንያታዊነት በላይ በስሜቱ ተፀይፎ ነፃነቱን ሊቀዳጅ የተነሳን ሰው መንገዱን ማመላከት የመሪዎቹ ሚና ነው፡፡ መሪው የትግሉን ‘እንዴትነት’ ‘መቼ’ ምን መደረግ እንዳለበት አፍታቶ ማሳየት እና እምቅ የሆነውን የነፃነት ፍላጎት ሀይል በተጠናና በተገቢው ቦታ ጥቅም ላይ እንዲውል ማስቻል፤ በዚህም አኳኋን ታጋዮችን አስተባብሮ መምራት አለበት፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥም የነፃነት ትግል መሪ ከስሜት በላይ እጅግ ምክንያታዊ እና በአስቸጋሪ ሁናቴዎች ውስጥም ለታለመው ግብ ሲባል በርካታ ፈታኝ ውሳኔዎችንም እንዲያሳልፍ ይጠበቅበታል፡፡
የዛሬን መጨቆን ሳይሆን የነገን የተጨበጠ ውጤት ቀድሞ ማለም ለዛም የሚከፈለውን መስዋእትነት ሁሉ መክፈል ግዴታው ነው፡፡ ከተራ ውሳኔ አንስቶ በሰዎች ህልውና ላይ እስከመወሰን የሚያደርስ ጠንካራ የዲሲፕሊን ሰው የመሆን ኃላፊነቱ የትግሉ መሪ ላይ ይወድቃል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ሂደቱ ከየት ተነስቶ የት እንደሚደርስ በጠራ ሁናቴ የሚያልም፤ ከግቡም ለመድረስ የቆረጠ፤ ተግባራዊ እና ለዛም ሁነኛ መላ ቀያሽ ብልሃተኛ መሪ ትግሉን ከጫፍ ለማድረስ ይቻለዋል፡፡
ትግል ተፈጥሯዊ ነው – በብልሃት ማስተባበር እና መምራት ደግሞ ትግልን ከፍሬ የሚያደርሱ ነገሮች ናቸው፡፡ ከዚህ ተነስተን በኢትዮጵያ ውስጥ ስለሚካሄዱት የነፃነት ትግሎች እንፈትሽ፡፡ አዋጪነታቸውንና ኪሳራቸውን እንመዝን፡፡
NOTHING PERSONAL NOR DESTRUCTIVE!
ትጥቅ ትግል በኢትዮጵያ?
———————-
* በ21ኛው ክ/ዘመን የትጥቅ ትግል አለማቀፋዊ አንደምታው እጅግ የተወሳሰበና ከፍተኛ የሰው እና የሉዓላዊነት ዋጋ የሚያስከፍል ነው፡፡ ለነፃነት እሞታለሁ ብሎ የወጣን ሰው አስተባብረህ ከምታስጣጥቀው መሳሪያ ጀምሮ የተለያዩ ሎጀስቲክና ዲፕሎማሲያዊ ድጋፎችን ማግኘት ግድ ይላል (ከመጋረጃ ጀርባ ያለውን የዓለም ሴራ ቀመስ ፖለቲካ ትተን)፡፡ እነዚህን ድጋፎች ለማግኘት ደግሞ በዓለም ላይ ከሚገኙ ታላላቅ መንግስታት ጀምሮ ገዢ መሬት ከሚሰጡህ አካላት ጋር በበርካታ ጉዳዮች ላይ ውል መፈፀሙ አይቀርም፡፡
ህወሃት ትጥቅ ትግሉን ድል አድረጎ ስልጣኑን ለመቆናጠጥ በሀገር እና በህዝብ ላይ እስከመደራደር ደርሷል፡፡ ለትጥቅ ትግሉ ስኬት ሲባልም ብዙ ታሪካዊ ስህተቶችም መፈፀማቸው ያልሻረ ቁስል ነው፡፡
በዚህ ዘመን ደግሞ በትጥቅ ትግል ኢህአዲግን ከስልጣን ማውረድ ከዓለም ነባራዊ ስርዓት አንፃር እጅግ አስቸጋሪ እና በአደጋ የተሞላ ነው (at this point there is no near-safe deal)፡፡ ስለዚህ ጥያቄው አህአዴግን ለማስወገድ ከተለያዩ ሀይሎች ጋር የሚደረጉት ስምምነቶች በእውነት ሚዛን ይደፋሉ ወይ? የሚፈፀሙት ስምምነቶች ህወሓት (ሊያውም በዘመነ ጦርነት) ካስከፈለን ዋጋ ምን ያህል ቢሻሉ፤ ምን ያህልስ የህዝባችንን እና የሀገራችንን ጥቅም ያስቀደሙ ወይም ከግምት አስገብተው የተፈፀሙ/ሊፈፀሙ ያሉ ናቸው? እነዚህ እና መሰል ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ እስካላገኙ ድረስ በዚህ ዘመን የሚደረገው የትጥቅ ትግል ለኢትዮጵያ የሚኖረው ፋይዳ ‘ከድጡ ወደማጡ’ ከመሆን ያለፈ አይሆንም!
* ከዚሁ ጋር በተዛመደ የኢትዮጵያ ታጣቂ ሀይሎች የመረጡት ገዢ መሬት የሙግቱ ዋና ማጠንጠኛ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ የሻቢያ ግዛት ኤርትራ፡፡ እዚህ ላይ ስለ ሻቢያ እና ወያኔ ፍቅርና ጠብ – አንድነት እና ልዩነት አሁን ስላላቸው ለክፉም ለደጉም የእርስ በእርስ መጠባበቅ ማውራቱ ‘አውቆ የተኛን . . .’ ካልሆነ በስተቀር ለማንም ምስጢር አይደለም፡፡ ምንአልባትም እነዚህ ሁለት ሀይሎች በኢትዮጵያም ይሁን በቀጠናው ጉዳይ ላይ የራሳቸው ቁማር እየተጫወቱ ስልጣናቸውን ለማስቀጠል ምንም ሊያደርጉ እንደሚችሉም ለሁሉም ሰው ግልፅ ነው፡፡
ይህን ካልን ዘንዳ ኢትዮጵያ ውስጥ በትጥቅ ትግል ለውጥ እናመጣለን የሚሉ ሃይሎች ከሻቢያ ጋር በምን መልኩ ሰምምነት አካሂደው ገዢ መሬት አገኙ? በዚህ ትግል ውስጥ የሻቢያ ጥቅም ምንድን ነው? በየትኛው ስሌት የኢትዮጵያ ታጣቂ ሀይሎች ከሻቢያ ድጋፍ አግኝተው የኢትዮጵያን ጥቅም ያስጠብቃሉ? (በቀደም ለት የኤርትራው ፕሬዘዳንት ስለኤርትራ እና ኢትዮጵያ ስላለፈውና መሆን ስላለበት ሲያብራሩ እነዚህ ጥያቄዎች ይበልጡኑ አወዛጋቢና በትጥቅ ትግሉ የተሰማሩ ሀይሎች ግልፅ ሊያደርጓቸው እንደሚገቡም ጭምር ተገንዝቤያለሁ!)
ስለሆነም እነዚህ መሰረታዊ ነጥቦች ምላሽ ባላገኙበት ሁናቴ ኢትዮጵያ ልጆቿን ዳግም ወደ እርስ በእርስ ጦርነት የምትከትበት አሳማኝ ምክንያት አይኖርም (ምሬት እና ጭቆና ብቻውን ለውጥ ሊያመጣ እደማይችል ከላይ በመግቢያዬ ያሰፈርኩትን ልብ ይሏል) – የጦረኞቹ የፖለቲካ ሰዎች ይህን መሰሉን ጉዳይ አፍታተው መዳረሻውን፣ ጥቅምና ጉዳቱን እስካሁን ማሳመንም ሆነ ደፍረው ለውይይት ሊያቀርቡት አለመቻላቸው በራሱ የትጥቅ ትግሉ አዋጪ እንዳልሆነ አመላካች ነው (there is something fishy behind the silence)፡፡ (እንዲህ አይነቱ ነገር መገለፅ የለበትም የሚል መከራከሪያ እኔ አልቀበልም – ሁላችንም በሀገራችን ጉዳይ ያገባናል!)
* እዚህ ጋር አብሮ መነሳት ያለበት ነገር ደግሞ – ይህን ትግል ለመቀላቀል የሚፈልጉ ሰዎች የሚከፍሉት አላስፈላጊ መስዋእትነት ነው፡፡ ገና ሳይጀመር በባዶ ሜዳ፤ በጉዞ ላይ እየተለቀሙ ዘብጥያ የወረዱትን እግዜር ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ ያም ብቻ ሳይሆን ከምትታገልለት ህዝብ ውጪ ሆነህ ልታገኘው የምትችለው የሎጀስቲክና ሌላም መሰረታዊ ድጋፍ አናሳ ነው፤ ከናካቴውም ላይኖር ይችላል፡፡ ለምሳሌ ያህል አሁን በኤርትራ ምድር ከሌላ ሀይል ጋር ውህደት የፈፀመው የአርበኞች ግንባር በተለይ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ከፍተኛ ድጋፍን ማግኘት የቻለና በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ተስፋ ተጥሎበት ነበር፡፡ ምከንያቱ ደግሞ ይታገል የነበረው በዛው በህዝቡ መሃከል ሆኖ መሆኑ ነው (ያ አደጋ የለውም እያልኩኝ አይደለም ቢያንስ ግን ከባህሩ የወጣ አሳ አለመሆን ያለው ጠቀሜታ ከጉዳቱ ይበልጣል)፡፡ በየትኛው መልኩ ጭቆናው በቃኝ ብሎ ለሚያስብ ሰው ‘መንገዱም ጨርቅ’ ለመቀላቀልም ቀና የነበረ ግንባር ነበር፡፡ አሁንስ?
* እርግጥ የህዝባችን ስነ ልቡና ለትጥቅ ትግል የቀረበ መሆኑ አይካድም፡፡ ታሪካችንም ቢሆን ስልጣን በጦረኞች እንጂ በሰላማዊ መንገድ ተቀይሮ አያውቅም፡፡ ያም ሆኖ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁናቴ የዚህን መሰሉን የህዝብ ስነ ልቡናዊ ዝግጁነት ጥቅም ላይ ሊያውል የሚችል አስማሚ አጀንዳም የለም፡፡ ለዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ ራሱ በትጥቅ ትግል ያሉት የተበታተኑ ሀይሎች ናቸው፡፡ ይህ ችግርም ባልሆነ ነበር ግና ለነፃነት ዋጋ የሰጠና ለዛም ለመሞት የቆረጠው ምን ያህል ነው? አምናለሁ ነገርን የሚለውጡት ሚሊዮኖች ሳይሆኑ ጥቂቶች ናቸው – ቢሆንም በኔ እምነት እነሱም ከላይ በዘረዘርኳቸው ምክንያቶች ሌላ አማራጭ እንዲጠቀሙ ይገፏቸዋል (ለዚህ ነው ብዙዎች ተስፋ ቢያስቆርጥ እንኳን ለሰላማዊው ትግል ቅድሚያ የሚሰጡት)፡፡ ወጣም ወረደ በዚህ ጉዳይ ላይ የማነሳው መሰረታዊ ጥያቄ ግን በጣም ግልፅ ነው – ይህን ታሪክ እና ባህል ይዘን እንቀጥል ወይስ እንቀይረው? እውን ትጥቅ ትግል በትጥቅ ትግል የሚቀያየርን የስልጣን አዙሪት መስበር ይችላል? የጦረኛን ህዝብ ስነ ልቡና በጦረኛ መቀየር ይቻላልን?
* ሌላው ደግሞ ጦርነት ለሰብዓዊነት ቦታ አለመስጠቱ ነው፡፡ የሰው ልጅ አንድ ጊዜ ከገደለ በኋላ – ደም ካየ በኋላ ለሌላ ሰብዓዊ መብቶች ሊቆረቆር የሚችልበት ሩህሩህነት አይኖረውም፡፡ መግደልን የተለማመደ አንድ ሰው ጭካኔን እየተለማመደ መሆኑን ማንም አይክደውም፡፡ በዚህ ሁናቴ ስብእናው የሚገነባ ግለሰብም ሆነ ቡድን ደግሞ ለወደፊቱ ህልማችን አደጋ ነው፡፡ ሰው መጨከን የለበትም እያልኩኝ አይደለም (there may come critical times in life)- ሁሉም ነገር ግን የሚቃኝበት መንፈስ እንደ ነገሩ ተጨባጭ ሁናቴ መሆን አለበት፡፡ አሁን ላይ ይህን ያህል ርቀት መሄድ ይቻላል ወይም አለብን? መቀበል ይቸግረኛል!
ይህን የበለጠ ለማብራራት ሩቅ ሳንሄድ የሀገራችንን የትናንት ታሪክ እናንሳ፡፡ የህወሓት እና ኢህአፓ ታጋዮች ብረቱን እስኪጨብጡት ድረስ እንደሁላችን ሰዋዊ ባህሪያቸው እንዳልተለያቸው ምንም አጠያያቂ አይደለም – አንዴ ሞትን ተኩሰው ከተፉ በኋላ ግን የማያባራ እልቂት ሆነ፡፡ ሰብዓዊነታቸው ተሟጦ ግፉ ለኛም ተረፈ! ትጥቅ ትግል ይህ እንዳይሆን የሚሰጠን አንድም ዋስትና የለውም! በደም የታጠበ እጅ ህሊናው ለመፅዳት ትልቅ ፈተና አለበት፡፡ እረግጥ ሰብዓዊነት በፖለቲካ አውድ ውስጥ አሻሚ ትንታኔ ቢሰጥበትም በጥቅል ግን ከትጥቅ ትግል የፖለቲካ ትርፍ በላይ በማህበረስብ ስነ ልቦና ላይ የሚኖረውን ጠባሳ ከኛ በላይ ህያው ምስክር ያለ አይመስለኝም፡፡ የከፋ የሚያደርገው ደግሞ አሁንም የአንድ አገር ሰው ወንድም በወንድሙ ላይ እጁን ማንሳቱ ነው፡፡
ሰላማዊ ትግል በኢትዮጵያ?
————————
* ዓለም ዛሬ የምትመራበት መርህ እና ሴራው እየረቀቀ ቢመጣም አንድ እውነት ግን መቼም ሊሻር አይችልም! በሰላማዊ ትግል ውስጥ ማናቸውንም ሀይል ከጎን ለማሰለፍ ትለቁ ነገር አገዛዝን በህግ የበላይነት እና የሞራል ልዕልና ማጠየቅ ነው፡፡ መሳሪያ ደግኖ ሲመጣ ደረትህን ነፍተህ መጋፈጥ የመሳሪያውን ብረት በእቶን እሳት ከማቅለጥ ያነሰ አይደለም፡፡ ዛሬ አንተን ቢገድል፣ ነገ ጓድህን ቢደግመው – ቀጥሎ ቃታውን የመሰብ አቅም አይኖረውም – ምክያቱም ጓዶችህ በባዶ እጅ ገጥመው እየወደቁ ህሊናውን አሸንፈውታል፡፡ ገዳይህ ብቻም ሳይሆን ሌላውም ሀይል ይህን ቆራጥነትህን ከመቀበል እና ከመተባበር ውጪ አማራጭ የላቸውም፡፡
እርግጥ ጨካኞች የሞቀ ቤታቸው ውስጥ ናቸው፣ ይህን ቆራጥነትህን አያዩትም አይረዱትም ስሜትም አይሰጣቸውም – መጠቀሚያቸው ግን የሚልኩት ወታደርና ፖሊስ ነው፡፡
በሰላማዊ ትግልም የምታሸንፈው ይህንኑ ሀይል እንጂ ጨቋኞቹን አለመሆኑ እሙን ነው፡፡ አፈሙዙን አዙሮ ጨካኞችን ወደ ዘብጥያ እንዲያወርድ የሚገደድበት የትግል ስልት ቢኖር ሰላማዊ ትግል ብቻ ነው፡፡ ልትገድለው ሳይሆን ሞትን ደፍረህ ለነፃነት ከምታደርገው ትግል በላይ ልቡን አቅልጦ ከጎንህ የሚያሰልፍው ሌላ መንገድም የለም፡፡ እንግዲህ ይህ የትግል ስልት በርካታ ጨቋኞችን ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፍ ስርዓቱን ጭምር እየተፈታተነ ያለ የትግል አይነት ነው፡፡
* በሌላ በኩል ይህ የትግል ስልት በኢትዮጵያ ያልተሞከረ በተግባርም እምብዛም ያልታወቀ ነው፡፡ የህዝባችን ስነ ልቡና በራሱ ለዚህ የትግል ስልት ዝግጁ አይደለም፡፡ ለዚህም ነው ኢህአዴግን በሰለማዊ ትግል ከማስጨነቅ ይልቅ ገና ከጅምሩ እዚህም እዚያም ትጥቅ ትግል የተጀመረው፡፡ ለዚህም ማሳያው ከ1998 በኋላ ከተፈጠረው ቡድን ውጪ ያሉት ታጣቂዎች ከጅምሩም በረሃ ወርደው የነበሩ መሆናቸው ነው (እርግጥ አንዳንዶቹ ከህወሓት ጋርም አብረው የገቡ ናቸው)፡፡ ከ1998 በኋላ ትጥቅ ትግልን የመረጠው ቡድንም ቢሆን ሰላማዊ ትግል ለማካሄድ እምብዛም አልጣረም፡፡ ኢህአዴግ እንከን የለሽ ምርጫ አደርጋለሁ አለ፤ ፓርቲዎች ተሰባሰቡ፤ እስካሁን ተፅዕኖ መፍጠር የቻለ ቅንጅት ፈጠሩ፤ እንከን የለሽ ምርጫ ተካሄደ፡፡ ውጤቱ ግን ብዙዎችን ተስፋ አስቆረጠ፡፡ የዘመነ የምርጫ ፖለቲካም አበቃለት! ቀጠለና አንድነት ፓርቲ ሰላማዊ ትግል አካሂዳለሁ፤ ህዝብን የስልጣን ባለቤት አደርጋለሁ ብሎ ትግል ሲጀምር – ሌሎች ደግሞ አይ ህዝቡ የሰጠንን ድምፅ በመሳሪያ እናስመልሳለን ብለው ጦርነት አወጁ፡፡ በኔ እምነት ሰላማዊ ትግል በኢትዮጵያ ምድር ላይ አለመጀመሩን ብቻ ሳይሆን ለመጀመርም ያለውን ችግር ይህ ኩነት ሁነኛ ማሳያ ነው፡፡
ምናልባትም የዚህ የትግል ስልት ትልቁ ተግዳሮት በህዝቡ ዘንድ አዲስ መሆኑና ለመቀበል እና ለመተግበርም እጅግ ድካምን የሚጠይቅ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ነፍጥ አልባ ትግል ለመምራት የሚነሱ መሪዎችም መጥፋት ነው፡፡ አንዱ ወደ እስር ሲጓዝ ሌላው በስሩ ተተክቶ ትግሉን ማስቀጠል ግድ የሚል የትግል ስልት መሆኑን ብዙዎች ይዘነጉታል መሰል አንዱ ሲነካ አስሩ ወይ ቤቱ ይቀመጣል ወይ ይሰደዳል ወይ ጦር ያነሳል፡፡ ይህ ትግል በቅብብሎሽ እንጂ በአንድ ትውልድ ብቻ የሚያበቃም ላይሆን ይችላል፡፡ እስክንድር ሲታሰር ተመስገን ይተካል ተመስገን ሲታሰር ሌላው ይቀጥላል እንጂ አለቀቀ ደቀቀ ሰላማዊ ትግል አይሰራም ሊባል አይችልም፡፡ አንዷለም ሲታሰር ሃብታሙ ይተካል ሃብታሙ ሲታሰር እኛ እንቀጥላልን እኛ ስንገባ ሌላው ይከተላል፡፡ አንድነት ፈረሰ ሰማያዊ ይቀጥላል – ሰማያዊ ሲፈርስ ወይ ሌላ ፓርቲ ወይ በሌላ መልክ ትግሉ ይቀጥላል፡፡ መሪ ብቻ አያሳጣ!
* ነፍጥ አልባ ትግል በመውጣትና በመውረድ ውስጥ፤ በአድካሚና ተስፋ አስቆራች ጉዞ ዘላቂነት ያለው ድል ያስገኛል፡፡ በነፍጥ አልባ ትግል ብዙዎቻችን ሙሴን እንጂ ኢያሱን ልንሆን አንታደልም (የህወሓቶቹን ሳይሆን የቅዱስ መፅሃፎቹን)፡፡ እንቅፋቶችም ብዙ ናቸው – በመንገድ ተንጠባጥበው የሚቀሩ – በተስፋ መቁረጥ ውስጥ የሚሰናከሉ በርካቶች ለትግሉ በጠላትነት ሊነሱበት ሁሉ ይችላሉ፡፡ ካዛም አልፎ በሌላው ዓለም እንደታየው ዘለግ ያለ ጊዜ መውሰዱ አሰልችነት ቢኖረውም ውጤቱ ግን በሂደቱ ሁሉ የተረጋገጠ ነውና ተመራጭ ያደርገዋል፡፡ ህዝብን የስልጣን ባለቤት እንዲሆን ማስቻል ብቻ ሳይሆን አመለካከቱንና ሌሎች በርካታ ጉዳዮችንም በሂደቱ እየታገለና መልክ እያስያዘ ከግቡ ይደርሳል፡፡
አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ይህን አድካሚ ጉዞ የሚያቃልል እና መንገዱንም የሚያሳጥር ምቹ ሁኔታ አለ፡፡ ላለፉት 40 እና 50 ዓመታት በደም መፋሰስ ውስጥ ያለፈ ህዝብ በስነ ልቦና ረገድ ያን ጊዜ ዳግም ለማየት ፍፁም አይሻም፡፡ ከዛም ሲያልፍ አዲሱ ትውልድና በእርስ በርስ ጦርነቱ ያልነበረው የህበረተሰብ ክፍል አሁን ላለው ዓለምአቀፍ ስርዓት ቀረቤታ ያላቸው መሆኑ ለአዲስ የትግል ስልት ዝግጁነታቸው ከፍተኛ የመሆን እድሉ ቀላል አይደለም (የድምፃችን ይሰማን እንቅስቃሴ ልብ ይሏል)፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ጨቋኞቻችን ዘመኑን የማይመጥኑ በአዲሱም ትውልድ በዓለምም ዘንድ መቀይር እንዳለባቸው፣ በእድሜ መግፋትም ቢያንስ ጡረታ መውጣት እንዳለባቸው የጋራ ግንዛቤ መኖሩ የሰላማዊ ትግሉን የሚያፋጥን ነባራዊ እውነታ ነው፡፡
* ሰላማዊ ትግል በምርጫ ፖለቲካ የሚገደብ አይደለም፡፡ እርግጥ ምርጫን እንደ ጥሩ አጋጣሚ ሊጠቀም ይችላል፡፡ ሂደቱ በራሱ ከአነስተኛ ነገሮች በመጀመር እያደገና እየረቀቀ ይሄዳል፡፡ በትግሉ ውስጥ በተጠና መልኩ የሚንቀሳቀሱ ሰዎችን ብቻ ሳይሆን በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን የማቀፍ ባህሪም አለው፡፡ አውቀው ከሚተገብሩት ባልተናነሰ መልኩ ሳይሰማቸውና ሳያውቁት በትግሉ የሚሳተፉም እንዲኖሩ እድል ይሰጣል፡፡ በሕቡ እና በግላጭም ሊካሄድ ይችላል፡፡ ሰላማዊ ሆነው ህግን መጣስ ድረስም መሄድ ይቻላል – ለምሳሌ ያህልም በሩሲያ Pussy Riot (የሴቶች መብት ተሟጋቾች እንቅስቃሴ – በተከለከሉ ቦታዎች እና ነውር በሆነ ሁናቴ ጭምር ተቃውሞን ማሰማት)፣ በኢትዮጵያ በቅርቡ እየተደረገ ያለው በመገልገያ ብር ኖት ላይ ተቃውሞን በማስፈር ማሰራጨት . . . የመሳሰሉት . . .
* ሰላማዊ ትግል መነሻው እና መዳረሻው የታወቀ ነው፡፡ ጊዜው ምን ያህል ቢረዝም እንኳን ውጤቱ ግን ዘላቂነት ያለው ነው፡፡ ስልጣንን ከጨቋኞች የማውረጃ ትግል ብቻ ሳይሆን – የጦረኝነትን ባህልንና የህዝብ ስነልቦና መቀየር የሚችል ትግል ነው፡፡ ያለመሳሪያ ጨቋኞችን ከስልጣናቻው ማውረድ የቻለ ህዝብ በራስ የመተማመኑ መጠን ከፍተኛ ይሆናል፡፡ ማንም መጣ ማን ያለምንም ስጋት የፈለገውን የመሻር የፈለገውን የመሾም አቅም እንዳለው – እንደሚችልም የሚተማመን ህዝብ ሊኖር የሚችለው በሰላማዊ ትግል በሚመጣ ለውጥ ብቻ ነው፡፡ በተለይ እንደኢትዮጵያ በበርካታ ታሪካዊ ትብታብ እና ግጭቶች ውስጥ ላለፉ ሀገራት ሰላማዊ ትግል የቱንም ያህል ተስፋ አስቆራጭ እና አድካሚ ቢሆንም አማራጭ ግን ሊቀርብበት የሚችል አይመስለኝም!
* ሰላማዊ ትግል ጭቆናን ከማስወገድ ባለፈም በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ የመተማመን፣ የመተሳሰብና የመዋደድን ባህል ያሳድጋል፡፡ ሰብዓዊነትን ያጎለብታል፤ ለዓላማ መሞት እንጂ መግደልን ስለማያበረታታ ሰዋዊ የሆኑ እሴቶቻችንን ጠብቀን ስነምግባር ያለው ህብረተሰብ እንድንፈጥር ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል፡፡
ሁለገብ ትግል በኢትዮጵያ?
———————–
* ይህ አይነት ትግል በተለያዩ ሀገራት ተሞክሮ ስኬታማ ሆኗል፡፡ በጥቅል ሲታይም ህዝባዊ እምቢተኝነትን (የነፍጥ አልባ ትግል አካል) እና ህዝባዊ አመፅ (የትጥቅ ትግል ደጋፊ ‘hot spot for armed struggle’) አቀላቅሎ የሚሄድ የትግል ስልት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁናቴ ሲቃኝ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚበዛ – የጨቋኞች አፈና እንዲጠናከር ሰፊ እድል የሚሰጥ ነው፡፡
* በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁናቴ የዚህ አይነት ትግል ዋነኛ እንቅፋት ደግሞ የቆሸሸው ፖለቲካ ባህላችን ነው፡፡ መተማመን የጠፋበት፣ አንዱ አንዱን ማጥፋት የሚፈልግበት፣ ሴራ የበዛበት እና በተጠና መልኩ መንቀሳቀስ ማናናቅ አዋቂ በሚያሰኝበት የፖለቲካ ባህል ውስጥ ውስብስብነት ያለውን ሁለገብ የትግል ስልት እንጠቀም ማለት ኢህአዴግ እድሜ ልኩን ሲገዛ ይኑር ከማለት አይተናነስም፡፡ ይህ ብቻ ቢሆን ደህና፤ ነገር ግን ሁለገብ ትግልን በሀገራችን ወቅታዊ ሁናቴ ለመተግበር አስቸጋሪ የሚያደርገው ሌላ መሰረታዊ ጉዳይ “የየትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው” አይነት ለውጤቱ ብቻ ትኩርት የመስጠት ዝንባሌ ነው፡፡ እንዲህ አይነቱ ግድ የለሽ ለሂደቱ ደንታ የሌለው አካሄድ በሁለገብ የትግል ስልት ከሚያስገኘው ውጤት በላይ ኪሳራው የትየለሌ ነው፡፡ ስለዚህ በዚሁ ዘግተነው ወደ ማጠቃለያችን እናሳልጥ!
ማጠቃለያ
———-
በዚህ ሀቲት ውስጥ ለማመላከት እንደተሞከረው ሀገራችን አሁን ባለችበት ሁናቴ ከሁሉም የትግል ስልት ይልቅ ሰላማዊ የትግል ስልት ውጤታማነቱ የሚያሻማ አይደለም፡፡ እርግጥ ማናቸውም መንገድ የራሱ የሆነ መጥፎና ጥሩ ነገሮች ቢኖሩትም ከሌሎች የትግል አይነቶች በተሻለ የተመጠነ ኪሳራ ነገር ግን ዘላቂና የሚጨበጥ ውጤት ያለው የትግል ስልት መሆኑም አያከራክርም፡፡ ትልቁ ኃይልም ህዝብ ብቻ መሆኑ ከተቀሩት በቀጠናው ላይ አይናቸውን ከጣሉ ዓለምአቀፍ ሀይሎች ጋር ሰጥቶ መቀበል ወይም በሌላ ሴራ የመጠለፍ አደጋው በእጅጉ የቀነሰ ነው፡፡
ነፍጥ አልባ የትግል ስልት በሀገራችን አዲስ ከመሆኑ አንፃር ገና ዳዴ በማለት ላይ ቢሆንም በጥቂት ጀምሮ እየሰፋና ከዳር ዳር እንደሰደድ በመስፋፋት ለሀገራችን ዘላቂ ለውጥን ለማምጣት ሰፊ እድል ያለው ነው፡፡
ባጠቃላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ (በሀገር ቤትም ሆነ በውጪም) እነዚህን የተለያዩ የትግል ስልት አይነቶች ትርፍና ኪሳራ በመመርመር እና በማገናዘብ ለኢትዮጵያ የሚበጀውን መንገድ እንዲመርጥ እና እንዲደግፍ መልእክቴ ነው፡፡ ከመነሻዬም እንዳሰፈርኩት የትግል ፍላጎት፣ የነፃነት ስሜት ገፊ ሀይል እና ጭቆና ብቻውን ለለውጥ አያበቃምና ሀገራችን በተያያዘችው ከአገዛዝ ወደ ነፃነት የሚደረግ ትግልን የምትመሩ ቡድኖችና ግለሰቦች ቆም ብላችሁ መንገዳችሁን ብትመረምሩ መልካም ነው፡፡ ከታናሽ ወንድማችሁ በሚሆን ምክርም ፅሁፌን ላብቃ – ብቻ ምንም እንወስን ለውሳኔያችን ቆራጥ፣ የተግባር ሰው እና ለሀገራችን እና ለህዝባችን ስንል ከተራ ሴራ፣ በከንቱ ውዳሴ ከመኮፈስ የፀዳን እንሁን!
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

No comments: