Sunday, September 11, 2016

ፍትህ ከሌለ ሰላም የለም

September 11,2016
ዳንሄል ጣሳው

በዚህ አጋጣሚ በኦሮሚያ፥በአማራ በቂሊንጦ ወህኒ ቤት የሞቱት፥ ሰሞኑን በደምቢ ዶሎ ልጇ የተገደለባት እናት ታሪክ ዘግናኝና የሚያስቆጭ ነው።ለሁሉም የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እንገልጻለን። ግድያውም አሁኑኑ እንዲቆም፥ወታደሩ ወደ ካምፑ እንዲመለስ፤ ማንም የጸጥታ አካል በህዝብ ላይ እንዳይተኩስ እናሳስባለን።በዚህ በ21ኛው ክ/ዘመን እያንዳንዷ ሂደት በማስረጃ ስለተያዘች ነገ በሀገር ውስጥም በዓለም አቀፍ ህግም ስለሚያስጠይቅ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያስፈልጋል።ይህን የፈፀመ ያስፈፀመ ነገ ከተጠያቂነት አይድንም።

ባለፈው ለሀገራችን መፍትሄ የሚሆኑ 7 ነጥቦች ያወጣንበት ጽሁፍ በ ethiopiariseandshine.comይገኛል።ይህ መልእክት ከተቃውሞ ጋር በተያያዘ የታሰሩ እንዲሁም ከዚህ ቀደም የተፈረደባቸው የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና ጋዜጠኞች ለሰላምና መግባባት ሲባል ይፈቱ፥ በህዝብ ላይ የተኮሱ ለፍርድ ይቅረቡ የሚለውና ሌሎችም ሃሳቦች ያሉበት ነው። 

እንዲህ ግን አይቀጥልም፤የሰላምና የፍትህ ብርሃን በቅርቡ መብራቱ አይቀርም፤እግዚአብሔር አለ።
"የምዋቹን ሞት አልፈቅድምና ይላል ጌታ እግዚአብሔር" ሕዝቅኤል 18:32
በአዲስ አመት አዲስ ነገር 
ፍትህ መብት እንዲከበር
በሥራና በጸሎት
ይቻላል ምን ተስኖት!
ኢትዮጵያ ልማት ያስፈልጋታል።የተጀመሩ መልካም የሚባሉ ጅማሮዎች አሉ።ልማቱ እንዲቀጥል ግን ሰላም ያስፈልጋል።ያለ ሰላም ሰሞኑን እንዳየነው ልማት ይደናቀፋል።ሰላም ደግሞ የሚመጣው ፍትህ ሲኖር ነው።ፍትህ ከሌለ ዘላቂ ሰላም ብንፈልገውም በቀላሉ ማግኘት አይቻልም። ሀገር ሰላም የሚሆነው የህዝብ መብት ሲከበር ብቻ ነው፤ሰብዓዊ መብት ካልተከበረ መረጋጋት አይታሰብም።

ለዚህ ደግሞ ህዝብ የመፍትሔው አካል እንዲሆን መደረግ አለበት፤ህዝብ ሲባል ሰልፍ የወጡትና ዳያስፖራ ያሉ ኢትዮጵያውያን ተቃዋሚዎች፤ወጣቱም ጭምር እንጂ የመንግስት ደጋፊዎች ብቻ መሆን የለባቸውም።የተቃዋሚዎች ድምጽ በሀገሪቷ የመንግስት ሚዲያ መተላለፍ አለበት። በህዝቡ ቀረጥ የሚተዳደር ሚዲያ እስከሆነ በሀገር ውስጥም በዳያስፖራ ያሉትን የተቃዋሚን ድምጽ መስማት ነበረብን።እስካሁን ለዛ አልታደልንም። የኢትዮጵያ ዋና ገቢ ከዳያስፖራ በሚላከው ነው፤እነሱም ይደመጡ፤ "አክራሪ ፅንፈኛ" ብሎ ሁሉንም ማውገዝ፥መድረክ መከልከል፥እንደ ወንጀለኛ ማየት አግባብ አይደለም።እስካሁን ከሀገር ውስጥም ከውጭም የተቃዋሚ ድምጽ በመንግስት ሚዲያ አልተላለፈም።እንደዚያ ቢደረግ ለመፍትሔው ቅርብ እንሆናለን። የመንግስት ሚዲያ ማንኛውንም ኢትዮጵያዊ እኩል ማስተናገድ አለበት እንጂ ለአንድ ፓርቲ ብቻ ማድላት የለበትም።ህዝብ እንደተደመጠ ካወቀ ሊታገስ ይችላል። ያኔ መተማመን ይዳብራል እንጂ አሁን በህዝብና በመንግስት መካከል መተማመን እየጠፋ ነው።ዲሞክራሲ የሁሉንም ሃሳብ ማክበር ማለት ነው፤ከዚያ ህዝቡ በነፃ ምርጫ ይወስናል።"አንተ ጠባብ፥አንተ ትምክህተኛ፥አንተ አናሳ፥አንተ ደጋፊ፥አንተ ተቃዋሚ " ብሎ አንዱ አንዱን ማግለል መፍትሔ አይሆንም። ከዘር ጥላቻና ከወንጀል ነጻ እስከሆነ ድረስ ሁሉም ለሀገሩ ጠቃሚ ያለውን የመናገር መብት ይኑረው። "አንተ እንደዚህ ነህ" ብሎ አንድን ንጹህ ኢትዮጵያዊ በአስተሳሰቡ ብቻ ማግለልና ስም ማጥፋት አይገባም። አንዱ የብሔር አስተሳሰብ አቀንቃኝ፥ሌላው ደግሞ የብሔራዊ(አገራዊ) አስተሳሰብ ያለው ይሆናል፤በሁለቱ ቃላት መሃል ያለው ልዩነት ዊ የምትለው ፊደል ብቻ ናት።እርግጥ ጥልቅ ክርክሮች በነዚህ ሁለት አስተሳሰቦች ይካሄዳል፤ግን ለመገዳደልና ለመጠላላት በፍጹም ሊያበቃ አይገባም።

በዚህ አጋጣሚ ለማሳሰብ የምንወደው ባለፈው "7 የመፍትሔ ሃሳቦች" መልእክታችን እንዳስተላለፍነው ዘርን መሰረት ያደረገ የጥላቻ ንግግርና ጥቃቶች ባስቸኳይ መቆም አለበት። ይህ ለወደፊት አብሮ መኖር አይበጅምና።በማህበራዊ ሚዲያ የሚካሄደው የዘር ጥላቻና የጥቃት ዛቻ የኢትዮጵያን ህዝብ አይመጥነውምና በአስቸኳይ መቆም አለበት። ሌላውን መጥላት መርዝ ጠጥተን የጠላነው ሰው እንዲሞት ማሰብ ነው። በ21ኛው ክፍለ ዘመን ጥላቻ ጊዜው አልፎበታል።እንኳን እንደ ሀገራችን ሃይማኖትና ባህል ያለው ህዝብ ቀርቶ ዛሬ በሳይንሳዊ መንገድ ጥላቻ ራስን ከመግደል ያለፈ ጥቅም እንደሌለው ተረጋግጧል። መቃወም አንድ ነገር ነው፥ ጥላቻ በፍጹም ሌላ ጉዳይ ነው። በሰማያዊውም በሳይንሳዊውም በሁለቱም የተወገዘ ነው።። እርግጥ ሰው ሲማረር ብዙ ያስባል፥ይሁንና በጥላቻ ከመሸነፍ በሰብአዊነት አሸናፊ መሆን የተሻለ ነው። መንግስት እንደሚለው የህዝቡ ችግር መልካም አስተዳደርና ሙስና ብቻ ሳይሆን የሰብአዊ መብት፤የዲሞክራሲና የመንግስት ስልጣን ጥያቄ ነው።አሁን ቁጣው ገንፍሏል፤ብዙ ደም ፈሷል፤ነገሩ ተወሳስቧል። ነገሮችን አቅልሎ ማየት ለከፋ ችግር ሀገሪቷን ማጋለጥ ይሆናል።

የመረረው ህዝብ ከቁጥጥር ውጭ ከመሆኑ በፊት (እስካሁን ካልሆነ) ዛሬውኑ፤አሁኑኑ ይታሰብበት፤በሀገርም በውጭም ካሉ ተቃዋሚዎችና የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር ውይይት ይጀመር፤ፓርቲዎች ያለ ተፅዕኖ ይንቀሳቀሱ፤ሚዲያው ነፃ ይሁን፤ተቃዋሚዎች በምክር ቤት እንዳይሳተፉ አንቆ የያዘው የምርጫ ህግ ይለወጥ።ከዚያም በተቃዋሚም በዓለም አቀፍ ህብረተሰብም ተቀባይነት ያለው ሀገራዊ ነጻ ምርጫ ይካሄድ። ያሸነፈውም ስልጣን ይረከብና ሀገሪቱን ይምራ፤እነዚህ ጥያቄዎች ህገ መንግስታዊ ከመሆናቸውም በላይ ዛሬ በዚህ ሰላማዊ መንገድ መሄድ ካልተቻለ የህዝቡ ቁጣ ከቁጥጥር ውጭ ሆኖ ነገ ይህ የውይይት በር ላይኖር ይችላል። 

አንዳንድ ወገኖች "ብሄራዊ ውይይትና ነጻ ምርጫ የሚለው ሃሳብ አይሰራም ምክንያቱም መንግስት አይቀበለውም፤ስለዚህ በአመጽ ማስወገድ ብቻ ነው" ይላሉ። እንግዲህ እኛ እንደ ሰላም መልእክተኞች ሁሉም ወገን ድምጹ የሚሰማበት፥ ምርጫ ተካሂዶ በሰላማዊ መንገድ መፍትሔ እንዲያገኝ እስከ መጨረሻ እንወተውታለን። ህዝቡ ያላቋረጠ ግፊት ካደረገ መንግስት ለውጥ ለማድረግ እንደሚገደድ እናምናለን፤ስለዚህ ህዝቡ በመንግስት ላይ ሰላማዊ ግፊቱንና ተፅእኖውን ማጠናከር አለበት። 

"ሰላማዊ እንቅስቃሴ የሚከለክሉ የአመጽ እንቅስቃሴን አይቀሬ ያደርጉታል" ብለዋል ፕሬዝደንት ኬኔዲ፤ቄስ ዴዝመንድ ቱቱ ደግሞ "ሰላም ከፈለክ ከጓደኛህ ጋር አትነጋገር፤ከተቃዋሚህ ጋር ነው መነጋገር ያለብህ"ብለው መክረውናል።
ሁላችንም ለሰላምና ፍትህ መስፈን የድርሻችንን እንወጣ።

"ኢትዮጵያ ተነሺ አብሪ አገልግሎት" ከሌሎች ወገኖች ጋር በመተባበር ድርሻችንን ለመወጣት እየሞከርን ነው።የሚመለከታቸውን በማነጋገር ላይ ነን።
የሃይማኖት አባቶች፥የሀገር ሽማግሌዎች፥ምሁራን፥በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን፥የመገናኛ ብዙሃን፥የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች፥የዲፕሎማቲኩ ማህበረሰብ፥ሌሎቻችንም ለሀገራችን የሚጠቅም አቀራራቢ አሳቦችን መሰንዘርና ድምጻችንን ማሰማት፥የችግሩ ሳይሆን የመፍትሄው አካል መሆን ያለብን ጊዜው አሁን ነው፤11ኛው ሰአት ላይ ነንና! 
መጽሀፉ እንደሚለው በጎ ሃሳቦች ያለ መካሪ ይበላሻሉ፤ብዙ ምክር ባለበት ግን ስኬት አለ።ምሳሌ15:22
የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ!

No comments: