የሚጠጣ ውሃ በጠፋበትና የምግብ እጥረት በከፍተኛ ደረጃ በተከሰተበት ፈታኝ ወቅት ውስጥ ገነትና በሚልዩኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን የሚገኙ ቢሆንም ጉዳዩ በአለም አቀፍ ደረጃ ተገቢውን ትኩረት እያገኘ አለመሆኑ መጪውን ጊዜ የበለጠ አስፈሪና አስጨናቂ ያደርገዋል፡፡
10.2 ሚልዩን ኢትዮጵያዊያንን ለመመገብ እስካሁን 1.4 ቢልዩን ዶላር ያስፈልጋል ተብሏል ፡፡ነገር ግን የተገኘውና ተስፋ የተገባው
የሚፈለገውን ግማሽ ያህል እንኳን አልሆነም፡፡አለም ከኢትዮጵያ ይልቅ ፊቷን አውሮፓን እያጥለቀለቃት ለሚገኘው የስደተኞች ጎርፍ፣ለየመንና ለሶሪያ ቀውሶች መስጠትን ምርጫዋ አድርጋለች፡፡
addየቻይልድ ፈንድ ኢትዮጵያ ዳይሬክተር የሆኑት ቼጌ ጉጊ ‹‹ለችግሩ እየተሰጠ የሚገኘው ምላሽ በጣም ዘገምተኛ ነው፡፡የእኔ ኃላፊነት ህይወትን ለማዳን የኢትዮጵያን መንግስት አቅም መደገፍ ቢሆንም ሁሉንም መድረስ አልቻልንም››ይላሉ፡፡
የአገሪቱን 85% ህዝብ የሚመግበው ግብርና በጠንካራው ኤልኒኖ የተነሳ ለሁለት ተከታታይ አመታት ዝናብ ማግኘት ባለመቻሉ መንግስትን አሜሪካንን ጨምሮ ሌሎች ለጋሾችን የምግብ እርዳታ ለመጠየቅ አስገድዶታል፡፡
የአሜሪካ መንግስት በቅርቡ ለአደጋው ምላሽ የሚሰጥ ቡድን ወደኢትዮጵያ መላኩን አስታውቋል፡፡ቡድኑ 4 ሚልዩን ዶላር የተገመተ የበቆሎና የስንዴ እርዳታ ለ200.000 ቤተሰቦች እንደሚያደርግም ተነግሯል፡፡
በኦሮሚያ ክልል የኢትዮጵያን መካከለኛ ክፍልም ያጠቃልላል አይናችሁ ማየት እስከቻለ ድረስ የምትመለከቱት መሬት በዝናብ እጦት ክፉኛ የደረቀ ነው፡፡በእነዚህ ቦታዎች የሚገኙ እንስሳትም አጥንታቸው ጎላ ብሎ የሚታይና የጠወለጉ ናቸው፡፡ባለፈው ዓመት የእርዳታ ድርጅቶች የተነበዩት የተረጂዎች ቁጥርም በአካባቢው በዚህ ወቅት በሶስት እጥፍ አድጓል፡፡
በድርቁ በከፍተኛ ሁኔታ በተጎዱ አካባቢዎች የአለም አቀፉ የጤና ድርጅት ትንበያ የነበረው የአልሚ ምግብ የሚያስፈልጋቸው ህጻናት ቁጥር በ20% ተመንድጓል የሚሉት የአለም አቀፉ የምግብ ፕሮግራም ቃል አቀባይ ካሊስ ማክዶን ናቸው፡፡
በዚህ ዓመትም የምግብ ፕሮግራሙ 2 ሚልዩን ልጆችን፣እርጉዞችንና የሚያጠቡ እናቶችን ለመርዳት እቅድ መያዙን ማክዶን ይናገራሉ፡፡
ዩኒሴፍ በበኩሉ ባቀረበው ትንበያ 500.000 ህጻናት አልሚ ምግብ በማጣት የተነሳ ለሚከሰት የጤና ችግር ይዳረጋሉ ብሏል፡፡
‹‹ሌላው ቀርቶ ድጋፍ እየተደረገም ሁኔታው እየተባባሰ ነው ››የሚሉት ደግሞ በፈንታሌ የቻይልድ ኢትዮጵያ ሰራተኛ ኢዮኤል ለማ ናቸው፡፡
ኢዮኤል ድርጅታቸው ከተባበሩት መንግስታት በሚያገኘው ድጋፍ እየታገዘ ከአምስት ዓመት በታች ለሚገኙ ህጻናት የአልሚ ምግብ እርዳታ ሲያደርግ መቆየቱን ይገልጻሉ፡፡ነገር ግን በተከታታይ ለልጆቻቸው አልሚ ምግቦቹን መውሰድና የሚሰጣቸውን ህክምና መከታተል ሲገባቸው ወላጆቻቸው ወደሌሎች አካባቢዎች ውሃ፣ምግብና ስራ ፍለጋ ስለሚሄዱ ስራቸውን አስቸጋሪ እንዳደረገባቸው ይጠቅሳሉ፡፡በዚህ ምክንያትም በሬሽን የሚከፋፈለውን ምግብ ብዙ ቤተሰቦች እንደሚያመልጣቸው ይናገራሉ፡፡
በእንቅስቃሴ ላይ ከሚገኙ ወላጆች አንዷ የ27 ዓመቷ ቡልቱ ሃሶ ትጠቀሳለች፡፡ለሰዓታት አናትን ከሚበሳው ጸሐይ እየታገለች አስቸጋሪውን ተራራ ታክካ ውሃ ፍለጋ ፈንታሌ ደርሳለች፡፡ቡልቱ ይህን ጉዞ ስታደርግ የ9 ወር ህጻን ልጇን በጀርባዋ አዝላለች፡፡
‹‹በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ምንም እንቅልፍ አልነበረኝም፣ ምክንያቱም ለእንስሳቶቻችን የተወሰነ ምግብ መፈለግ ነበረብኝ ፡፡ህይወታችንን ለማቆየትም ያለማቋረጥ መጓዝ ይኖርብናል››ብላለች፡፡
ኢትዮጵያ በማደግ ላይ ከሚገኙ የአለማችን አገራት አንዷ ተደርጋ ስትጠቀስ ብትቆይም እውነታው ግን 80% የሚሆኑት ኢትዮጵያዊያን የግብርናው ጥገኛ መሆናቸው ነው ፣ግብርናው ደግሞ የዝናብ ጥገኛ ነው፡፡የአለም ምግብ ፕሮግራሟ ማክዶን ድርጅታቸው በቀጣይ እርዳታ ማግኘት ካልቻለ በሁለት ወራት ውስጥ ያለውን በማጠናቀቅ ባዶ እጁን እንደሚሆን ያስጠነቅቃሉ፡፡
‹‹ለወራት አስቸኳይ እርዳታ ለማግኘት በማሰብ ጥሪ ስናደርግ ቆይተናል፡፡እጃችን ላይ የሚገኘው ግን ለቀጣዩቹ ስድስት ወራት ያስፈልገናል በማለት ከምናስበው ሩብ ያህሉን ብቻ ነው፡፡በጣም በቅርቡ አዲስ እርዳታ ማግኘት ካልቻልን በግንቦት ወር ያለንን በማጠናቀቅ ድጋፍ መስጠታችንን እናቆማለን››ማለታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ዩኒሴፍ ባወጣው ሪፖርትም ከምግብ እጥረቱ ጎን ለጎን 6 ሚልዩን ሰዎች አስቸኳይ የመጠጥ ውሃ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው አውስቷል፡፡በፈንታሌ በሚገኝ አንድ የእርዳታ ድርጅት የሚሰሩት ሳሙኤል ፈርፉ የአካባቢው ሌላኛው ዋነኛ ችግር ውሃ ነው ይላሉ፡፡
‹‹በአጠቃላይ ውሃ የለም ማለት ይቻላል፣ ወንዞቹ በሙሉ ደርቀዋል፡፡ውሃ በሌለበት ሁኔታ ደግሞ ህይወትን አስቸጋሪ ያደርገዋል ያደርገዋል፡፡በዚህ ምክንያትም የሰዎች በበሽታዎች የመጠቃት ዕድላቸው ይጨምራል››ብለዋል ኢዮኤል፡፡
ለጊዜው ኢትዮጵያዊያኑ በጣም በተጎዱት አካባቢዎች ዝናብ መጣል እንዲጀምር በጸሎት ተጠምደዋል፡፡ነገር ግን ለረዥም ጊዜ ዝናብ ጠፍቶ ሲመጣ ጎርፍ ሊፈጠር እንደሚችል ብዙዎች ይሰጋሉ፡፡
ኢዩኤል ‹‹በቅርቡ ዝናብ ይመጣል በመባሉ ሰዎች ጎርፍ ሊከሰት ይችላል በማለት ይሰጋሉ፡፡ነገር ግን ጎርፉ ቢመጣ እንኳን ከመኖሪያ ቤታቸው ውጪ የሚያጡት ምንም ነገር የቀራቸው የለም፡፡እንስሳቶቻቸውንና እርሻዎቻቸውን እንደሆነ ቀደም ብለው አጥተዋቸዋል››ብለዋል፡፡
ለ27 ዓመቷ ገነትና ለታዳጊው ልጇ ዝናብ በቅርቡ ይመጣል መባሉ የውሸት ተስፋ ነው፡፡‹‹ምግብና ውሃ የለንም፣ስለወደፊቱ ምን ሊፈጠር እንደሚችል አላውቅም ስለዝናቡ መምጣትም ቢሆን ምንም ተስፋ የለኝም››ትላለች፡፡
ምንጭ ዩኤስኤ ቱይ