Tuesday, October 11, 2016

በኢትዮጵያ እስረኞች አጥንትን ቀስ በቀስ በሚያፈርስ መርዝ እየተጠቁ መሆኑን ታውቀ

Oktober 11,2016
“ህወሃት በእስረኞች ላይ አጥንት የሚያመነምን መርዝ ይጠቀማል” እማኝ
"የባዮሎጂካል መሣሪያ ጥቃት ነው፤ ቤተሰብ ለልጆቻችሁ ድረሱ"
bio-bone

ከጥቂት ዓመታት በፊት የግንቦት ሰባት መሪዎች እና አባላት መታሰራቸው ይታወሳል። ብዙዎቹ ቃሊቲ የሚገኘው እስር ቤት ነበሩ። በእስር ቤት እያሉ በደረሰባቸው ያልታወቀ ሕመም ምክኒያት ሕይወታቸውን ያጡ መሪዎችም ነበሩ።ታዲያ አንዴ ከሜክሲኮ ወደ ሃያሁለት በታክሲ ተሳፍሬ ስሔድ በግምት የሃያ ዓመት ዕድሜ ያለው ልጅ ታክሲው ውስጥ ገብቶ አጠገቤ ተቀመጠ።
ታክሲው ሞልቶ መሔድ ሲጀምርም ወንድሜ ይቅርታህን የታክሲ ትከፍልልኛለህ ብሎ ጠየቀኝ። ዞር ብዬ ያየሁት ይህን ሲል ነበር። ድንጋጤ እና መሸማቀቅ ይነበብበት ነበር።ልቤ በጣም አዘነለት። ምን ሆነህ ነው? ከዬት ነው የምትሔደው፤ወዴት ነው የምትሔደው ብዬ ጠየኩት። እርሱም ከቃሊቲ እስርቤት ዛሬ መለቀቄ ነው አለ። ለምን ታሰርክ እንዴትስ ተለቀቅህ ስለው የቦሌ ሁለተኛ ደረጃ  ት/ቤት ተማሪ እንደ ነበረ እና ከመንገድ አፍሰው ወደ እስር ቤት እንደጣሉት ነገረኝ። የግንቦት ሰባት አባል እና ደጋፊ ናችሁ ብለው ቀን ከለሊት ሲገርፉን፤ ሲያስርቡን፤ መዓት መከራ ደርሶብናል፤ እንደምታዬው አእምሮዬ ራሱ ልክ አይደለም። ነገርግን በጣም ጤነኛ ልጅ ነበርኩ ብልህ አታምነኝም፤ ድሮም ትንሽ እብድ ነገር ነበርክ ብለህ ብታስብ አይገርመኝም አለ።
ፍርድቤት የሚባል ነገር አይተን አናውቅም።
መጀመሪያ ላይ ቤተሰብ እንዲጠይቀን ተፈቅዶላቸው ይጠይቁን የነበረ ሲሆን በኋላ ግን ተከለከሉ። ቤተሰቦቼን በአይኔ ካየሁ ሁለት ዓመት ሊሆነኝ ነው አለ። ከዚያም ወዲያው ስለ ራሱ ትቶ ሁላችንም ስለምናውቃቸው እና በግንቦት ሰባት ሰበብ እስርቤት ተጥለው ስለ ነበሩ መሪዎች ይነግረኝ ጀመር። እነ አቶ እከሌ እኛ ጋ ነው ታስረው የነበሩት። እንላላካቸውም ነበር። ምንም እንኳን እነርሱ እንደ እኛ ወደ ውጪ ብዙውን ግዜ እንዲወጡ ባይፈቀድላቸውም ፀሐይ እንዲሞቁ በሚያወጡዋቸው ሰዓት እየተላላክን የሚፈልጉትን እንገዛላቸው ነበር። ከቆይታ በኋላ እነ አቶ እንትናን እና አቶ እንትናን ከሌሎች ለይተው ሌላ ክፍል ውስጥ አሰሯቸው። በኋላም አይናችን እያየ ሰውነታቸው መፈራረስ ጀመረ። አፍንጫቸው፤ ጆሮዋቸው፤ አይናቸው ጣታቸው የስጋ ደዌ እንደያዘው ሰው ይፈራርስ ጀመር። አንድ ቀን ሊልኩኝ ሲጠሩኝ በድፍረት ምን ሆናችሁ ብዬ ስጠይቅእንደ ፍሊት ያለ መርዝ እየረጯቸው መሆኑን ነገሩኝ። መድሃኒቱንም እድሜ ለቻይና እናንተን የማሰናበቻ ቀላል መንገድ ተገኘ እያሉ ይፎክሩብናል፤ ይስቁብናል፤ የውሸታቸውን ሆስፒታል ይወስዱናል። ለቤተሰባችን ታመዋል ብለው ይነግራሉ ብለው ነገሩኝ አለ።
ከዚያስ በኋላ ስለው ቀስ በቀስ መንቀሳቀስ የማይችሉበት ደረጃ ላይ ደረሱ። በሚያስጠላ ሁኔታ ሰውነታቸው እየፈራረሰ ስለነበረ መሸፋፈን ጀመሩ። መጀመሪያ ወደዚያ ክፍል ከገቡት መካከልም እነ አቶ እንትና ሞቱ። ታመው ሞቱ ተብሎ ሲነገር ሰማን አለ።
ቤተሰብ እንዳያያችሁ ለምን ተከለከለ ብዬ ስጠይቀው፤ ምክንያቱን አላወቅንም ነበረ። በኋላ ግን ቤተሰባችን እንዳያዬን ከከለከሉ በኋላ ምግብ ያመጡልን ጀመረ አለ። ምግባቸውን መብላት ስለቀፈፈን የበላን እያስመሰልን እንደፋ ነበረ፤ ወደ ውጪ የመውጣት እድል ስናገኝም የሌሎች እስረኞችን ትራፊ እንበላ ነበር።ከቆይታ በኋላ ግን ምግቡን እንድንበላ አስገድደው እንቢ ስንል የሆነ መርፌ ወጉን። ቀስ በቀስ ሰውነታችን እየደከመ ሔደ፤ ቀስ በቀስ አእምሯችንም እየጨለመ ሲሔድ ይታወቀን ጀመር።
አንዳንዶቹ ልጆች ከሌሎቻችን በበለጠ መልኩ እንደ እብድ የለየላቸው ሆኑ። ታመው ነው እያሉ ሆስፒታል ይወስዷቸዋል። የአእምሮ ጭንቀት ነው እያሉ የስነልቦና ጠበብት መጥተው እንዲጎበኟቸው ያደርጉ ነበር። ከዚያ አውጥተው መንገድ ላይ ይጥሏቸዋል። ስንቶቹን ቤተሰብ እንዳገኛቸው እግዚአብሔር ብቻ ያውቃል አለኝ።
ሰፈሩን ያውቅ እንደሆነ ስጠይቀው በጣም ደስ አለው። አዲሳባ ሃያሁለት ተወልጄ ያደኩ መሆኑን እና ቦሌ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪ እንደነበርኩ ነግሬህ ቤቴን እንደማውቅ ስትጠይቀኝ ችግሬ በጣም ገብቶሃል ማለት ነው አለኝ። እስከ ቤተሰቡ ቤትም ሸኘሁት። ያ ልጅ ምን ላይ እንደደረሰ አላውቅም። ነገርግን እግዚአብሔር በጥበቡ ካልደረሰለት በስተቀር በሕይወት አለ ብዬ አልገምትም።
ይህ ነገር ወደ አእምሮዬ የመጣው ትላንት የአሜሪካ ድምፅ ሬድዮን ዜና ስከታተል አንድ ብሔሩ ኦሮሞ የሆነ ኮማንደር በሰበታ የታሰሩ ልጆችን በተመለከተ የአጋዚ አዛዦች ስብሰባ ጠርተውን ለታሰሩት ልጆች ከምግብ ጋር መርዝ እንድንሰጣቸው መመሪያ ተላልፎልናል ብለው በመቆርቆር ሲናገሩ ስሰማ ነው። ከምንምግዜ በላይ አሁን አደጋ ላይ መሆናችን አሳሰበኝ። በየእስርቤት የታጎሩ የኦሮሞ እና የአማራ ልጆች እጣ ፈንታ ይሔው የተባለው መርዝ መሆኑ እረፍት ነሳኝ።
አሁን ሊበሉን ተነሱ ማለት ነው። አሁን ቤተሰብ ለልጆቹ መድረስ ይኖርበታል።ልጆቹ በእጁ እንዲገቡ እስኪያደርግ ድረስ ቤተሰብ መተኛት የለበትም። ይህ እንዲሆን ደግሞ ቤተሰብ ሚስጥሩን መረዳት ይኖርበታል።
ይህ ዜና እንዲሰራጭ ማድረግ አንዱ የመከላከያ መንገድ ሊሆን ስለሚችል እባካችሁ ለዚህ ጉዳይ ትኩረት በመስጠት ዘገባችሁን አጠናክሩ።
ወደ ሕዝቡ ሊደርስ በሚችልበት በማንኛውም መንገድ ይህ ዜና ይሰራጭ። እውነት መሆኑን ማመን ቢያቅታችሁም እንኳን በማሰራጨታችሁ የምትጎዱት ነገር ግን የለም።
(ለደህንነታቸው ስንል ይህንን መረጃ የላኩልን ማንነት ከማውጣት ተቆጥበናል፡፡ ፎቶው ለማሳያነት የተወሰደ ነው)

No comments: