Saturday, August 27, 2016

በርከታ ከተሞች ራሳቸውን ከወያኔ አገዛዝ ነጻ አድርገዋል

August 27,2016
የዐማራ ሕዝብ ተጋድሎ – ሙሉቀን ተስፋው (ነሃሴ 20 ቀን 2008)
በበርከታ የጎጃም ከተሞች የዐማራ ተጋድሎ ተፋፍሟል፤ ራሳቸውንም ከወያኔ አገዛዝ ነጻ አድርገዋል
 በቡሬ ከተማ ከሠላሳ ሺህ በላይ ዐማራ ለተጋድሎ ወጥቷል፤ የኦሮሚያ ኢንተ. ባንክን ሕዝቡ ጥበቃ አድርጎለታል
 በጅጋ የተጋድሎ ሰልፉ ሦስተኛ ቀኑን ይዟል
 ቋሪት ወረዳ ሙሉ በሙሉ በሕዝብ ቁጥጥር ሥር ሆኗል
 ማንኩሳ፣ ፍኖተ ሰላምና ጉንደወይን ሌሎች የዐማራ ተጋድሎ የተካሄደባቸው ከተሞች ናቸው
 በጎንደር ብዙ የዐማራ ልዩ ኃይል ፖሊስ አባሎች ከሥራ ታግደዋል
 በደብረ ታቦር የሥራ ማቆም አድማ ሊጀመር ነው
 በወልቃይት የአማርኛ ሙዚቃ አትሰሙም በሚል ግጭት ተፈጠረ
 40 የዐማራና ኦሮሞ የጸረ ሙስና ኮሚሽን አቃቢ ሕግ ባለሙያዎች ከሥራ ተባረሩ
ቡሬ፤
በሬ ዛሬ የዐማራ ተጋድሎ ከተካሔደባቸው ከተሞች ዋነኛዋ ናት፡፡ ከጠዋቱ ሦስት ሰአት አካባቢ የጀመረው የዐማራ ተጋድሎ እስከ ምሽት 12 ሰአት ድረስ ቆይቷል፡፡ የተጋድሎ ሰልፉ ማዶ በሚባለው የከተማው ክፍል የተጀመረ ሲሆን ከሰላሳ ሺህ በላይ የሚሆኑ የከተማዋ ነዋሪዎች ተጋድሏቸው ሲያሰሙ ውለዋል፡፡ ወልቃይት ዐማራ ነው፤ ኮ/ል ደመቀ እና የወልቃይት ጠገዴ የዐማራ ማንነት ጥያቄ አቅራቢ ኮሜቴዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ይፈቱ፤ መሬታችን ይመለስ፤ 25 ዓመት ታስረናል አሁን ግን በቃን፤ ዐማራነት ወንጅል አይደለም፣ ወያኔ ሌባ ነው፤ ብአዴን እኛን አይወክልም… የሚሉ መፈክሮች ገልተው ሲሰሙ ውለዋል፡፡ የወያኔ ደጋፊ የሆኑ ድርጅቶችና ግለሰቦች ንብረት ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ ትንሳኤ ሆቴል (ባለቤቱ ዐማራ ሲያስገድል የኖረ ሕወሓት ነው)፣ ቀበሌ 01 ጽ/ቤት፣ አብቁተ፣ የዓባይና የንግድ ባንኮች መጠነኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ የኦሮሚያ ኢንተርናሽናል ባንክን ሊያወድሙ የሚፈልጉ ተላላኪዎችን ወጣቱ ዐማራ አክሽፎታል፡፡ ኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ የሚደርሰው ግፍ መቆም አለበት ሲሉም የዐማራ ሕዝብ አጋርነቱን አሳይቷል፡፡
በሰው ሕይወት ላይ የደረሰ አደጋ መኖሩን በተመለከተ ላቀረብነው ጥያቄ የዐይን ምስክር ሲናገሩ ‹‹እኔ በዐይኔ አንድ ለእረፍት የመጣ የዩንቨርሲቲ ተማሪ አጋዚ ሲገድለው አይቻለሁ፤ ሦስት ዐማሮችም በጥይት ተመተው ሆስፒታል ገብተዋል፤ በሕይወት ስለመኖር አለመኖራቸው ያወቁት ነገር የለም›› ብለዋል አንድ እማኝ በስልክ እንዳረጋገጡልን፡፡ የአጋዚ ወታደሮች ያቆሰሏቸው ሰዎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በቡሬ ከተማ መግቢያና መውጫ በሮች ሙሉ በሙሉ በወጣቱ ተዘግተዋል፡፡
ጅጋ፤
የጅጋ ዐማሮች ዛሬ ለሦስተኛ ቀን የዐማራ ተጋድሎ አድርገዋል፡፡ የጅጋ ከተማ ሕዝብ ከነሃሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በየቀኑ ወደ አደባባይ እየወጣ ተጋድሎውን እያደረገ ነው፡፡ በጅጋ እስካሁን አንዲት እህታችን ተሰውታለች፡፡ ከተማዋንና አጠቃላይ ወረዳውን ዐማሮች ራሳቸው የተቆጣጠሩ ሲሆን ዛሬ ላይ የሃይማኖት አባቶች ወጣቱን ለመሰብሰብ ሞክረው ነበር፡፡ የዐማራው ወጣትም ከእንግዲህ በኋላ የዐማራ የመኖር መብት ሳይረጋገጥ ተጋድሎው እንደማይቆም እንቅጩን በአንድ ድምጽ ተናግረው ስብሰባው ያለስምምነት መበተኑን ከቦታው በስልክ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ በጅጋ ለተከታታይ ሦስት ቀናት ምንም ዓይነት የንግድ እንቅስቃሴም የለም፡፡ ሁሉም ዐማራ የተጋድሎ ጥያቄውን እያስተጋባ ነው፡፡ በስልክ ያነጋገርናቸው ወጣቶች ‹‹ከእንግዲህ በኋላ ዐማራነት ወንጅል ሆኖ የምንኖርበት ምንም ምክንያት የለም፤ የአባቶቻችን የአርበኝነት ታሪክ በዚህ ትውልድ ይደገማል›› ሲሉ በጎበዝ አለቃዎች ጭምር መመራት መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡
ቋሪት፤
በቋት ወረዳ ገነት አቦ ከተማ ትናንት ነሃሴ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. የተጀመረው የዐማራ ተጋድሎ አድማሱን አስፍቶ የወረዳዋ ከተማ ገበዘ ማርያምም በሕዝብ ቁጥጥር ሥር ሆናለች፡፡ ገነት አቦ ከተማ ትናንት ከቀኑ ከ9፡00 እስከ 12፡00 የነበረውን የዐማራ ተጋድሎ ለማደናቀፍ ከወረዳው የወያኔ ተላላኪዎች የተውጣጡ የፖሊስና የሚንሻ አባላት ወደ ገነት አቦ ተላኩ፡፡ የገነት አቦ ዐማሮችም በአንድ ድምጽ ‹‹በመጣችሁበት መኪና አሁኑ ተመለሱ፤ አይ ካላችሁ ሕይወታችሁን ጠልታችኋል ማለት ነው›› አላቸው፡፡ ከመኪና ሳይወርዱ ተመለሱ፡፡ የከተማዋ ነዋሪዎች ለዛሬ ጠዋት ቀጠሩ፡፡ በቃላቸው መሠረት ከጠዋቱ 12፡00 ጀምሮ የተጋድሎ ሰልፉ ተካሄደ፡፡ የገበዘ ማርያም ከተማ ዐማሮችም ተጨመሩ፡፡ የከተማ ፖሊሶች ዝም አሉ፡፡ ከዞን የመጣ ሁለት መኪና የፌደራል ፖሊስም የቋሪትን ዐማራ መጋፈጥ አልቻለም፡፡ የፌደራል ፖሊሶች ልብሳቸውን ቀይረው ተደብቀው ዋሉ፡፡ ነፍጠኛው ዐማራ ጥይቱን ሲቆላው ዋለ፡፡ ለዚህማ ቋሪትን ማን ብሎት፡፡ በቋሪት ነገም የዐማራ ተጋድሎ ይቀጥላል፡፡
ማንኩሳ፤
በማንኩሳ የተጀመረው የዐማራ ተጋድሎ ለሁለተኛ ቀን መቀጠሉን ሰምተናል፡፡ በማንኩሳ ትናንት የተካሔደው የዐማራ ተጋድሎ መጠነኛ ቢሆንም ዛሬ ግን ወደ አደባባይ ያልወጣ የከተመዋ ነዋሪ አልነበረም ነው የተባለው፡፡ በማንኩሳ ዝርዝር ጉዳዮችን በስልክ መቆራረጥ ምክንያት ማግኘት አልቻልንም፡፡
ፍኖተ ሰላም፤
በፍኖተ ሰላም ከተማ የዐማራ ተጋድሎ ዛሬም ቀጥሎ ውሏል፡፡ ትናንት የአንድ ዐማራ ወጣት ነፍስ ያጠፈው ቅጥረኛ ምንሻ ቤት መቃጠሉንም ሰምተናል፡፡ የፌደራልና የአጋዚ ጦር በፍኖተ ሰላም ከተማ ከመጠን በላይ መግባቱን ሰምተናል፡፡ ዛሬ ይህ ሪፖርት እስከተሠራበት ሰዐት ድረስ መንገዶች ሁሉ ዝግ መሆናቸውን ሰምተናል፡፡
ጉንደወይን፤
በእነሴዎች አገር ጉንደወይን ትናንት ነሃሴ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ታላቅ የዐማራ ተጋድሎ ሰልፍ ተካሒዷል፡፡ የጎንቻ ሲሦ እነሴ ወረዳ ዐማሮች ትናንት ባካሔዱት ተጋድሎ የትግራይ የበላይነት ይብቃ፣ የማንነት ጥያቄያችን መልስ ይሰጥ፣ ዐማራነት ወንጀል አይደለም፣ የወንድሞቻችን ደም መፍሰስ መቆም አለበት… የሚሉ መፈክሮች መሰማታቸውን ዛሬ ከጉንደ ወይን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ በተያያዘም ነሃሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በብቸና አንድ የአገዛዙ መሣሪያ የሆነ ሰው ተገድሎ መገኘቱንም ሰምተናል፡፡
ደብረ ታቦር፤ በደብረ ታቦር ከተማ ከነሃሴ 22 ቀን ጀምሮ ለሦስት ቀን የሚቆይ የቤት ውስጥ አድማ እንደሚደረግ መርሃ ግብሩ ያሳያል፡፡ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች እንዳትወጡ የሚሉ ማስታዎቂያዎች ተለጥፈዋል፡፡ ይህን ተላልፎ በሚገኝ ሰው ላይም የዐማራውን ተጋድሎ እንደመተላለፍ ስለሚቆጠር ከህዝብ ጋር እንደተጣላ ይቆጠራል ተብሏል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ቅጥረኛ ካቢኒዎች ነጋዴዎችን ሱቆቻቸውን እንዳይዘጉ ያስጠነቀቀ ሲሆን የቤት ውስጥ ተጋድሎው አስተባባሪዎች ማንኛውንም ተቋም የሚከፍት ሰው ከወያኔዎቸ ጋር እንዳበረ ስለሚቆጠር የሚያስከፍለው ዋጋ የከፋ ነው ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡
ጎንደር፤
ጎንደር የቤት ውስጥ አድማው ለሦስተኛ ቀን ቀጥሏል፡፡ የቤት ውስጥ አድማው እስከ እሁድ ይደርሳል ተብሏል፡፡ ኮሎኔል ደመቀን የመውሰድ እቅዱ መክሸፉን የሰማን ሲሆን ትናንት ምዕራብ አርማጭሆ አብደራፊ አካባቢ አንድ ዐማራ የተሰዋ ሲሆን ሁለት የወያኔ ቅጥረኛ ፖሊሶች ዛሬ መገደላቸውን ሰምተናል፡፡
የጎንደር ከተማ ልዩ ኃይል ፖሊስ ምክትል አዛዥ መልካሙ የሽዋስ ጋርም ብዛት ያላቸው የፖሊስ አባላት በወያኔ ትእዛዝ መቀነሳቸውን ሰምተናል፡፡ የተቀነሱት የዐማራ ልዩ ኃይል ፖሊስ አባላት በሕዝብ ላይ ባለመተኮሳቸው ነው የተባለ ሲሆን ሁሉም የዐማራ ፖሊሶች በዐማራው ሕዝብ ላይ እንደማይተኩሱ ቃል ገብተዋል ሲሉ ምንጮቻችን ነግረውናል፡፡
አዲረመጥ፤ በወልቃይት ከተማ አዲረመጥ ትናንት ነሃሴ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. የወልቃይት ዐማሮች የፋሲል ደመወዝን ‹‹ዐማራ ነኝ›› አዲስ ሙዚቃ ከፍተው ሲያዳምጡ የትግራይ ልዩ ኃይል ፖሊስ ‹‹አማርኛ ሙዚቃ ማዳመጥ አትችሉም›› በማለቱ በተፈጠረ ግጭት ከስድስት በላይ የሚሆኑ ፖሊሶች በከፍተኛ ሁኔታ ቆስለው አምልጠዋል፡፡ አንድ የወልቃይት ዐማራ በጥይት የተመታ ሲሆን ለሕይወቱ አስጊ እንዳልሆነ ከቦታው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
አዲስ አበባ፤
40 የዐማራና ኦሮሞ ተወላጅ የጸረ ሙስና ኮሚሽን አቃቢ ሕግ ባለሙያዎች ከሥራ ተባረሩ፡፡ ከአዲስ አበባ የጸረ ሙስና ኮሚሽን ዋና መሥሪያ ቤት ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው በሙስና ወንጀል የተዘፈቁ የትግራይ ተወላጆችን መዝገብ ክስ የያዙ 40 የዐማራና ኦሮሞ የአቃቢ ሕግ ባለሙያዎች ከሥራ ተባረዋል፡፡ የተባረሩት የአቃቢ ሕግ ባለሙያዎች በሥራቸው የተመሰከረላቸውና አንቱ የተባሉ የሕግ ባለሙያዎች ናቸው ተብሏል፡፡ ሆኖም የያዙት የሙስና ክስ መዝገብ የትግራይ ተወላጅ ሙሰኞችን በመሆኑ ሕወሓትን በከፍተኛ ሁኔታ ያዳክማል በሚል የዐማራና የኦሮሞ የሕግ ባለሙያዎቹ ከሥራ ገበታቸው ለመጨረሻ ጊዜ ተባረዋል፡፡ ወያኔ ከዚህ በፊትም እንደ ዳኛ ግዛቸው ምትኩ ያሉ ጠንካራ የዐማራ የሕግ ባለሙያዎችን የማባረር ልምድ መኖሩን ያስታውሷል፡፡

No comments: