Friday, July 15, 2016

መፍትሄው አንድ ብቻ ነው - ህዝቡን ማክበር (ግርማ ካሳ)

July 14,2016
"አጋዚና ተጨማሪ የመከላከያ ኃይል ወደ ጎንደር ማምሻውን ገብቷል!!" የሚል ዜና አነበብኩ። አጋዚን ወደ ህዝብ መላክ መፍትሄ አይደለም። ነገሩን የበለጠ ነው የሚያባብሰው።

አጋዚ ተቀባይነት የለውም። አጋዚማ በሌሊት እንደ ወንበዴ መጥቶ ሰላማዊ ዜጎችን ለማፈን ሲል አሁን የተፈጠረውን ቀዉስ ያመጣው እርሱ ነው። እዚህ ላይ "አጋዚ አይደለም፣ የፌዴራል ፖሊስ ነው ምናምን .." የምትሉ ልትኖሩ ትችላላችሁ። በኔ ግምት ያው ናቸው። የተለያዩ ስም ያላቸው፣ የተለያየ ልብስ የሚለብሱ፣ ግን አንድ አይነት ተግባር የሚፈጸሙ፣  በሕወሃት ብቻ የሚታዘዙ ጸረ-ህዝብ ታጣቂዎች።

እነዚህ ሃይሎች ህዝብን ሲጠበቁ አላየንም። በጋምቤላ አሸባሪዎች መጥተው ወገኖቻችን ሲገድሉ በዚያ አልነበሩም። በሱዳን ድንበር ሱዳኖች ገበሬዎቻችንን ሲያጠቁ፣ ኢትዮጵያዉያንን ለመጠበቅ አልተንቀሳቀሱም። ሁልጊዜ የነዚህን ታጣቂዎች ጉልበት የምናየው ሰላማዊ ዜጎችን፣ ሕጻናትን አረጋዊያን እና ራሳቸውም መመከት የማይችሉት ሲደበድቡና በጠራራ ጸሃይ ተኩሰው ሲገድሉ ነው። በቅርቡ በኦሮሚያና አዲስ አበባ በንፋስ ስልክ አካባቢ በሕዝቡ ላይ ያደረጉትን ብቻ መመልከት ይበቃል።

ከጎንደር በተለያዩ ገጠሮችና ከተማዎች እያየን እንዳለው፣ ሕዝቡ እጅግ በጣም አምሯል። ከዚህ በኋላ የባርነት እና የጭቆናን ቀንበር ላለመሸከም ተማምሏል።

በነገራችን ላይ በጎንደር የተነሳው ከየትም የመጣ እንቅስቃሴ አይደለም። ወያኔዎች እንደሚሉት ከ ኤርትራ የመጣ አይደለም። የሻእቢያ እጅ  የለበትም። እንደው ሻእቢያ ቢያግዝ የሚያግዘው ወያኔዎችን ነው። ኤረትራ አሉ የሚባሉ ደግሞ  የት እንዳሉ ሁላችንም የምናወቀው ነው። ብዙም በዚያ ዙሪያ መጻፍ አያስፈለግም። እያየን ያለው እንቅስቃሴ፣ በሕዝቡ ዉስጥ ያለ ፣ ገንፍሎ የወጣ የነጻነትና የፍትህ ጥያቄ ነው።  ልክ በኦሮሚያ እንደነበረው፣ በሕዝብ ሃይል ላይ ብቻ የተመሰረተ እንቅስቃሴ ነው።

ወያኔዎች ከማንም በላይ ይሄንን የጎንደር ህዝብ የሚያወቁት ይመስለኛል። ምናልባት ጥጋቡ፣ ጮማዉና ስቡ አይምሯቸዉን ሸፍኖ  ያለፈዉን ታሪክ ካላስረሳቸው በስተቀር።

በመሆኑም ወደ ጎንደር እየላኩት ያለውን አጋዚ ወደ መጣበት ቢመልሱ፣ የገባም ካለ ደግሞ ቢያስወጡ ይሻላቸዋል። ጉዳዩን የክልሉ አስተዳደር በሰለጠነ መልኩ ማስተካከል ይችላል።

ይሄን የምጽፈው ለማስፈራራት አይደለም። በሜዳ ላይ ያለዉን ተጨባጭ ሁኔታ ከግምት በማስገባት እና ወደ ለየለት ጦርነት ከሚኬድ በሚል ነው። አጋዚዎች መጥተው እንደለመዱት እንግደል፣ እንጨፍጭፍ ቢሉ የተለየ ሁኔታ ነው የሚያጋጥማቸው። ተሸናፊ የሚሆኑት፣ የሚያልቁት ራሳቸው ናቸው። የአካባቢው መሬት ከዉጭ ለመጡ አመች አይደለም። ተራራማ ነው። እንኳን የታጠቀ ፣ ገደል ሸንተረሩን የሚያውቅ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ ቀርቶ፣ የቆረጡ ፣ ጥቂቶች ብቻ ይሄ የሰላማዊ ዜጎችን ደም እየጠጣ የደለበን የአጋዚ ጦር ድባቅ ማድረግ አያቅታቸዉም።

የወያኔ ባለስልጣኖች ልብ ይግዙ እላለሁ። ሕዝቡ ተናግሯል። አንፈልጋችሁም ብሏቸዋል። ሕዝቡን ይተወት ። አበቃ !!!!!!

ከዚህ በታች የምታይዋቸው የፌዴራል ልብስ የለበሱ የሕወሃት ሚሊሺያዎችን ነው። ሕዝቡ በሰላም በተቀመጠበት በመተንኮሳቸው የወደቁ ናቸው። በጣም ያሳዝናል።እድሜ ለወያኔዎች ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለብሄራዊ እርቅ በሮችን በሙሉ ዘግተው፣  እንደዚህ እንድንተላለቅ እያደረጉን ነው። ያሳዝናል። እስከአሁን ጥይት የሚተኮሰው በአንድ አቅጣጫ ነበር። አሁን ከሁለት አቅጣጫ እየሆነ መጥቷል።

ደግሜ እላለሁ።፡ይሄንን ህዝብ ወያኔዎች ባይተነኩሱት ይሻላል። የሕዝቡ ጥይቄ ቀላል ነው። ሰላም፣ ፍትህ፣ ነጻነትና እኩልነት ነው። በአገራችን ሁለተኛ ዜጋ አንሁን የሚል ነው። የሕዝቡን ጥያቄ ማክበርና መቀበል ነው ብቸኛው የሚያዋጣው መፍትሄ።




No comments: