Wednesday, May 18, 2016

የኢየሩሳሌም ተስፋው ደብዳቤ ከቃሊቲ እስር ቤት – ግንቦት 7

May 18,2016
ከእየሩሳሌም ተስፋው (ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት)


(እየሩሳሌም ተስፋው የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ አባል ስትሆን፣ በነብርሃኑ ተክለያሬድ መዝገብ ‹ግንቦት 7›ን ሊቀላቀሉ ሲሄዱ ተይዘዋል በሚል ክስ ቀርቦባቸው አሁን የመከላከያ ምስክር ለማስደመጥ በቀጠሮ ላይ ናቸው፡፡ እየሩሳሌም ተስፋው ይህንን ደብዳቤ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት በግንቦት 7፣ 2008 እንዲታተም ያወጣችው ቢሆንም፤ በተለያዩ እንቅፋቶች በዕለቱ ለሕዝብ ሳይደርስላት ቀርቷል፡፡) (የ እጅ ጽሁፏን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ) ይህቺ ቀን ከዛሬ 11 ዓመት በፊት በ1997 ዓ.ም. በዕለተ እሁድ ኢትዮጵያ ውስጥ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ ድምፁን ለመረጠው ፓርቲ ሊሰጥ የተሰለፈበት ዕለት ነበረች፡፡ ሕወሓት/ኢሕአዴግ እስቲ እንያቸው ምን ያመጣሉ በማለት ከዛ በፊትም ከዛ በኋላም ተደርጎ በማይታወቅ ሁኔታ የምርጫ ምኅዳሩን ገርበብ አድርጎ ከፍቶ በሩን አልፈው እንዲገቡ ፈቀደላቸው፡፡ በዛች በር ገብተው ብዙ ነገር ሠሩ፡፡ በውጭ ሚዲያ ላይ እምናውቀውን hard talk በአገራችን ላይ በአገራችን ሚዲያ ለማየት በቃን ተስፋችንም ለመላው ይህ ትውልድ ታሪካዊ (ዕድለኛ) ትውልድ ነው አልን፡፡ ለአገራችን ታሪከ ለመጀመሪያ ጊዜ በመረጥነው መንግሥት ልንተዳደር ነው፡፡ በሠላማዊ መንገድ (በምርጫ) የመንግሥት ለውጥ ልናይ ነው እያልን ስንደሰት ወዲያው በዛች ቀን ምሽት ምርጫው ተጠናቆ ወደቆጠራው ሲገባ ሕወሓት/ኢሕአዴግ አልበዛም?! በሚል መልኩ እስርና ግድያውን ጀመረ፡፡ ብዙ ሺሕ ዜጎቻችንን እንደቀልድ አጣናቸው፡፡ በአልሞ ተኳሽ ግንባር ግንባራቸውን እየተባሉ በየደጃፋችን ተደፍተው ቀሩ፡፡ ኮሎኔል መንግሥ?ቱ ኃ/ማርያም ከዛሬ ጀምሮ ብሎ – መስቀል አደባባይ ላይ ቀይ ሽብርን እንዳወጀ – ታሪክ ራሱን ደገመና ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ከዛሬ ጀምሮ በአንድ ዕዝ ስር በማለት የሞቱን ዐዋጅ ዐወጀ፡፡
ትዝ ይለኛል የዛሬ 3 ዓመት አካባቢ 2006 ላይ ሰኔ 3፣ 1997 ዓ.ም. በግፍ የተገደሉትን ንፁኃን ዜጎች ለማሰብ በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት ተሰባስበን ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም እንባቸው በጉንጮቻቸው እየወረደ ‹የማይታመን አምነን ወገኖቻችን አለቁ፡፡ ሰው እንዴት መለስን ያምናል? እንዴት ሕወሓት/ኢሕአዴግ ይታመናል?› እያሉ በቁጭት የተናገሩት ትዝ አለኝ፡፡ አዎ፣ የማይታመነውን አምባገነን በዚች ዕለት ወገኖቻችን የጥይት ራት ሆኑ!! እነሆ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የሠላማዊ ትግል በር ተዘጋ ብለው ያመኑ ድምፃቸው የታፈኑ መብታቸው የተረገጠ ንፁኃን ዜጎች እንዲሁም ከዚህ ቀን በኋላ ኢትዮጵያ ውስጥ ሠላማዊ ትግል ተዘጋ ሲሉ ግንቦት 7 አሉት፡፡ ይህ ሕዝባዊ ኃይል የተመሠረተበት ዋናው ዓላማ የወያኔን ዘረኛና አምባገነን አገዛዝ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ በትጥቅ ትግል ለማስወገድ በሃገር ወዳድና ለሕዝብ ተቆርቋሪ በሆኑ ወጣቶች ምሁራንና ዜጎች ግንቦት 7 ሕዝባዊ ኃይልን መሠረቱ፡፡ ይህ ሕዝባዊ ኃይል ሰንቆ የተነሳው ራዕይ “የሕዝብ ሉዓላዊ የሥልጣን ባለቤትነት የተረጋገጠበት የዜጎች መብቶች፣ አገራዊ አንድነት፣ ደኅንነትና ጥቅም የተከበሩባት ጠንካራና ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እውን ሆና ማየት” ሲሆን ተልዕኮው ደግሞ “መንግሥትን በኃይል የማስወገድ ሠላማዊና የሥልጣን ሽግግር በአገሪቱ እንዲኖር የማስቻል እና ከማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ጋር ያልወገኑ ነጻ እና ጠንካራ ብቃት ያላቸው ሕገ-መንግሥታዊ የመከላከያ የፖሊስና የደኅንነት ተቋማት እንዲኖሩ ማድረግ” ነው፡፡Eyerusalemነገር ግን ሕወሓት/ኢሕአዴግ ለሕዝብ ድምፅ ሥልጣን ላይ የወጣ ፓርቲ አይደለምና በየዕለቱ የሚፈጠረው ኮሽታ ስለሚያስበረግገው እንዲሁም ንፁኃንን ለማሰር እና ለመግደል ምክንያት ይፈልግ ነበርና ይህ ሕዝባዊ ኃይል እንደተመሠረተ “ሽብርተኛ” ስለፈረጀው መስራቾቹን እንዲሁም ወደሃገር እንዲገቡ የማይፈልጋቸውን ተቃዋሚዎች በዚህ አጋጣሚ “አሸባሪዎች” ሲል ፈረጃቸው፡፡ ከዚህ ጊዜ በኋላም ለሥልጣኔ ያሰጉኛል ያላቸውን ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ የሲቪክ ማኅበራት አመራሮች፣ ጦማሪዎች፣ የሃይማኖት አባቶች በአጠቃላይ ለም ብለው ጥያቄ እሚያነሱ ዜጎችን ግንቦት 7 በማለት በየወኅኒው እያሰራቸው ይገኛል፡፡
እንግዲህ ይህ ሕዝባዊ ኃይል ከላይ እንደገለጽኩላችሁ አሸባሪ ሊያሰኘው የሚችል ዓላማ፣ ራዕይም ሆነ ተልዕኮ የለውም፡፡ ለሠላማዊ መንገድ የተነጠቀውን መብቱን በሁለገብ ትግል ለማስከበር ዓልሞ የተነሳ ድርጅት ነው፡፡ ሠላማዊ ትግል ብቻውን ሕወሓት/ኢሕአዴግ ከወንበሩ እንደማያነቃንቀው እስካሁን የታዩት ሙከራዎች በቂ ናቸው ለዚህም ነው በዚህ ሰዐት ብዙ ወጣቶች ይህን ሕዝባዊ ኃይል በቆራጥነት እየተቀላቀሉት የሚገኙት፡፡
ሕወሓት/ኢሕአዴግ ባወጣው የፀረ-ሽብር ዐዋጅ (በነገራችን ላይ ይህን የፀረ-ሽብር ዐዋጅ ልብ ብላችሁ ካያችሁት ሕወሓት/ኢሕአዴግ ለራሱ ያወጣው ይመስላል፡፡ ለምሳሌ ሽብር በሌለበት ሽብር መንዛት አሸባሪነት ነው ይላል፡፡ ታዲያ በአገር ሠላም፣ በጠራራ ፀሐይ ቦንብ አፈነዱ እያለ documentary የሚሠራ ሕወሓት እንጂ ግንቦት 7 ነው እንዴ? በተረፈ ሁሉንም አንቀፆች ተመለከቷቸው ከግንቦት 7 ይልቅ ለሕወሓት ይቀርባሉና ገና ጫካ እያሉ የሕዝብን ተቀባይነት ለማግኘት ሲሉ በገዛ ሕዝባቸው (በሓውዜን) ላይ የጀመሩት እልቂት በደርግ ማሳበብ፣ አሁንም ከ25 ዓመት በኋላ ሳይቀነስ ሳይጨመር እንዳለ ነው፡፡ አሸባሪ ማነው?
እንግዲህ ይህ ሁሉ የተፈፀመው በዚህች ዕለት ነው፡፡ “ግንቦት 7” ይህቺ ቀን የትናንት አሰቃቂ ትዝታችን የዛሬ ክሳችን የነገ ተስፋችን ናት፡፡
ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ያልተማረ ዜጋ አይገኝም፡፡ ሁሉም ነጻነትን ይናፍቃል፡፡ ነጻ ለመውጣት ግን ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ማድረግ ይፈራል፡፡ የሆነ አካል መጥቶ ነጻ እንዲያወጣው ይፈልጋል፡፡ ይህ ደግሞ ሊሆን አይችልም፡፡ ነጻ ለመውጣት መጀመሪያ ራስን ከታሰሩበት የፍርሓት እስር ነጻ በማውጣት ትግሉን መቀላቀል ነው፡፡ ድርጅታችን ግንቦት 7 ለነጻነት፣ ለፍትሕና ለዴሞክራሲ የተቋቋመ ነጻ አውጪ ድርጅት እንጂ አሸባሪ አይደለም፡፡ ስለዚህ በድፍረት እናገራለሁ፡፡ እኔ ግንቦት 7 ነኝ፤ እናንተስ? ሁሌም እንደምለው የታሰረው አካሌ እንጂ ልቤ ቀይ ባሕርን ተሸግሮ ከጓዶቼ ጋር በኤርትራ በረሃ ነው፡፡ ይህቺ ቀን ለብዙዎች ሞት፣ አካል መጉደል፣ እስራት አብቅታለች፡፡ መራራውን ሳያልፉ ጣፋጭ፤ ሳይሞቱ ትንሳኤ የለምና ባለፈው ከመፀፀት ባለፈ እልህ አስይዞን ይህንን ዘረኛና አምባገነን የሽፍታ ቡድን ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መንግለን ለመጣል እንዘጋጅ፡፡ ከላይ እንዳልኩት የትላንት ጥቁር ጠባሳ፣ የዛሬ ግርፋትና እስራት፣ የነገ ተስፋ ናትና እንኳን ለዚች ቀን አደረሳችሁ፡፡ ይህች ቀን፣ የነጻነት እንዲሁም የድል ቀናችን እንደምትሆን አልጠራጠርም፡፡ ግንቦት 20 በግንቦት 7 እንደመስሰዋለን!!
የነጻነት ታጋዩ ጀግናው አንዳርጋቸው ፅጌ አንድ ጊቢ ብንኖርም መገናኘት አልቻልንም፡፡ እንኳን አካልህን ወሬህንም በስንት ስቃይ ነው፡፡ እምሰማው ያንተ መታፈን ወያኔ እንደጠበቀው ትግሉን አላሽመደመደውም፡፡ እንደውም፣ ይበልጥ አጦዘው ለኛ ከቤት መውጣት ምክንያት አንተ ነህ፡፡ እኛ የአንተ ፍሬዎች ነን፡፡ ዛሬ ታፍነህ ቀንና ሌሊቱን መለየት የማትችልበት ሁኔታ ውስጥ ብትሆንም የነጻነት ቀን ቀርባለችና እስከዛው ዕድሜህን ያርዝምልን፡፡

No comments: