Wednesday, November 18, 2015

“ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያውያን መብት” ረሃቡን በሚመለከት የስራ እቅዶችን አውጥቷል

November 18,2015

ረሃቡን በሚመለከት የተሰጠ መግለጫ፣ ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያውያን መብት (Global Alliance for the Rights of Ethiopians – GARE)

ዓለም አቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት ከተቋቋመበት ወቅት ጀምሮ ለኢትዮጵያዊያን ወገኖቹ በያሉበት ለሚደርስባቸው ግፍና ችግር ያልተቆጠበ ጥረት በማካሄድ ላይ ይገኛል። በዚሁ መሰረት በሳውዲ አረቢያ፤ በየመን፤ በሊቢያ፤ በኬንያ፤ በሰሜን ሱዳንና በማላዊ ችግር ለገጠማቸው ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች የገንዘብ፤ የዲፕሎማሲ፤ የምክርና ሌሎች ድጋፎች አድርጓል። ይኼ ግዙፍ ድጋፍ ስኬታማ ሊሆን የቻለበት ዋና ምክንያት ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በያሉበት የገንዘብ ድጋፍ ስላደረጉ ነው። ድርጅታችን እነዚህን ደጋፊዎች ያመሰግናል።Global Alliance for the Rights of Ethiopians (GARE)
አሁን የተከሰተውን የድርቅ ረሃብ፤ ቢቢሲ የተባለው ድርጅትና ሌሎች ተቋሞች ከዛሬ ሰላሳ ዓመታት በፊት “ከተከሰተው የድርቅ ረሃብ የማያንስና አሳሳቢ ነው” ያሉትን ረሃብ በሚመለከት ድርጅታችን መረጃዎችን ሰብስⶅ የችግሩን ጥልቀትና ስፋት ተገንዝቧል። የስራ እቅዶችን አውጥቷል። የኢትዮጵያ መንግሥት “እኔ ራሴ እወጣዋለሁ” ያለውን ብናውቅም፤ በሌላ በኩል የችግሩን መጠን በመረዳት መንግሥት ለተባበሩት መንግሥታት የምግብ ድርጅት፤ ወዘተ እና በያሉበት ለኢትዮጵያዊያን ያቀረበውን የድጋፍ ጥሪ በጽሞና ተመልክተነዋል። የተጎዱት ወገኖቻችን ቁጥር ወደ አስራ አምስት ሚሊየን እንደሚደርስ መታወቁ ብቻ ሳይሆን፤ በእኛ ግምትና ግንዛቤ በድርቅ ረሃብ ምክንያት አንድ ህጻን፤ አንድ እናት ወይንም አንድ አባት መሞት የለበትም።
ድርጅታችን ማንኛውም ከሕዝብ የሚሰበሰብ ገንዘብ፤ ተጠያቂነት፤ ግልፅነትና ሃላፊነት ባለው መልክ፤ መንገድና ድርጅት አማካይነት ለተጠቃሚዎች መድረስ አለበት የሚል መርህ ሲከተል ቆይቷል። ከInternational Organization for Migration (IOM) ያደረግነውና አሁንም የምናደርገው ስራ ምሳሌ ነው። በዚህም መሰረት ትብብሩ አግባብ ያላቸውን፤ በረሃቡ ዙሪያ በኢትዮጵያ ሰብአዊ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋሞችን ሲያነጋግር ቆይቶ በቅርቡ አጥጋቢ መልስ እንደሚደርሰውና ከስምምነት ላይ እንደሚደርስ ይተማመናል።
ይኼን በሚመለከት ትብብሩን በመወከል በNovember 17, 2015 በኢሳት ሬዲዮ ለታዳሚዎች አንደገለጽነው በሚከተሉት ቀናቶችና ሳምንታት ትኩረት የምንሰጠው በረሃብ ለሚሰቃዩ ወገኖቻችን ድርሻችን ለመወጣት የተቀነባበር የገንዘብ ስብሰባ ዘመቻ ማካሄድና የተሰበሰበው ገንዘብ ለተጠቃሚዎቹ እንዲደርስ ማድረግ ነው። በዚህ አጋጣሚ ከዚህ በፊት በየአካባቢው ያልተቆጠበ ጥረት ላደረጉት፤ ለወገኖቻችን እንደርስላቸው ለሚሉትና ለሌሎች ጥሪ የምናደርገው በያላችሁበት የገንዘብ መሰብሰብ ጥረቱን እንድትቀጥሉ፤ ያልጀመራችሁ እንድትጀምሩና ላልሰሙት እንድታሰሙ ነው።
የትብብሩን ድጋፍ የምትፈልጉ በቴሌፎንና በኢሜይል ለመገናኘትና የተዋጣውን ገንዘብ በትብብሩ ባንክ ለመላክ እንደምትችሉ እናሳስባለን።
4ruleoflaw@gmail.com
Tele: 877-746-4384
www.DefendEthiopians.org

No comments: