Sunday, October 4, 2015

ድርጅታችንን እናጠንክር፤ በጽናት እንታገል!

October 4, 2015
def-thumb“የአርበኞች ግንቦት 7 አባል በመሆኔ እኮራለሁ” እያሉ በአገዛዙ የይስሙላ ችሎት ሳይቀር በድፍረት የሚናገሩ ወጣቶች ተፈጥረዋል። ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለዲሞክራሲ፣ ለእኩልነትና ለሀገር አንድነት መስዋዕትነት መክፈል የሚያኮራ ተግባር መሆኑ በተግባር የሚያሳዩ ወጣቶች መጥተዋል፤ አሁን በርካቶችም እየመጡ ነው። ወያኔ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ በማኅበረሰባችን ውስጥ የዘራው የፍርሀትና የአድርባይነት ስሜት በራሱ በወያኔ የአገዛዝ ዘመን ተወልደው ባደጉ ወጣቶች እየተናደ፤ በምትኩ ሊጠፋ ተቃርቦ የነበረው የአገር ፍቅርና የአርበኝነት ስሜት እያንሰራራ ነው።
ቅንነት፣ ሀቀኝነት እና ጽናት ከተጣሉበት ጉድጓድ አቧራቸውን አራግፈው እየተነሱ ነው። በማኅበረሰባች ውስጥ ትልቅ የስነልቦና አብዮት እየተካሄደ ነው።
ከስነልቦና ለውጡ ጋርም በተግባር የአገር አድን ሠራዊትን የመቀላቀል ፍላጎት ያላቸው ወጣቶች ቁጥር በከፍተኛ መጠን እየጨመረ ነው። ወጣቶች የአገራቸው ባለቤት መሆናቸው ተገንዝበው የፓለቲካ ሥርዓት ለውጥ ለማምጣት በቁርጠኝነት መነሳታቸው ተስፋ ሰጪ ነገር ነው።
አርበኞች ግንቦት 7 በዚህ የለውጥ ወቅት ውስጥ ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ አጽንዖት ልንሰጣቸው ስለሚገቡ የድርጅትና የሥነሥርዓት (ዲሲፕሊን) አስፈላጊነት ላይ የጋራ ግንዛቤ መያዝና በተግባርም መተርጎም አስፈላጊ ነው ብሎ ያምናል።
ወጣቶች ትግሉን ለመቀላቀል መሻታቸው መልካም ነገር ነው። ሆኖም ግን በድንገት ብድግ ብለው መንገድ ከመጀመር ይልቅ ከሚያምኗቸው ወዳጆቻቸው ጋር የመሠረቱት፤ ከአርበኞች ግንቦት 7 ጋርም ትስስር የፈጠረ ስብስብ አካል ሆነው መቆየታቸው እጅግ አስፈላጊ ነው።
በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ ሆኖ የሚስጢር ድርጅት ማዋቀር አስቸጋሪ መሆኑ የማያጠራጥር ቢሆንም የማይቻል ነገር ግን አይደለም። ወጣቶቻችን በአምባገነን ሥርዓት ውስጥም ሆነው በዲሲፕሊን የታነፀ ድርጅት የመፍጠርን ክህሎት መላበስ ይገባቸዋል። ይህንን ማድረግ ስንችል ነው የህወሓትን ፀረ-አገርና ፀረ-ትውልድ ተግባር ማክሸፍ የምንችለው። ትግሉን በሁሉም የኢትዮጵያ ግዛቶች ማቀጣጠል የምንችለው በየአካባቢው የተደራጀ የለውጥ ኃይል ሲኖረን ነው። ስለሆነም የምስጢር የተደራጀ አካል በየመኖሪያና የሥራ አካባቢዎቻችን ሁሉ እንዲኖር ማድረግ ከአጣዳፊ ሥራዎቻችን አንዱ እናድርገው።
ሁለተኛው ነጥብ ሥነሥርዓትን የሚመለከት ነው። ሥነሥርዓት ከሌለ ድርጅት የለም። የህወሓት አገዛዝ ያሳደረብን ጎጂ የባህል ተጽዕኖ ከባድ በመሆኑ ራሳችንን በሥነሥርዓት ለማነጽ መልፋት ይጠበቅብናል። አገራችንና ራሳችንን ከህወሓት አገዛዝ ነፃ አውጥተን የተሻለ ሥርዓት ማምጣት የምንችለው ራሳችን፣ ድርጅታችን እና ተግባሮቻችን ለሥነሥርዓት ተገዢ ስናደርግ ነው። የነፃነት ታጋዮች ራሳቸውን ለሥነ ሥርዓት ያስገዙ መሆን ይኖርባቸዋል። አስተሳሰባችን ራሱ ሥነ ሥርዓት የያዘ ሊሆን ይገባዋል። እንደዚሁም ሁሉ ተግባሮቻችን በሥነሥርዓት የታነጹ ሊሆኑ ይገባል።
የንቅናቄዓችንን መዋቅር በመላው አገራችን ከዘረጋን፤ ራሳችንን፣ አስተሳሰቦቻችንና ተግባሮቻችን በሥነሥርዓት ከመራን፤ ቅንነት፣ ሀቀኝነትና ጽናት ከተላበስን ድላችን ቅርብ እና አስተማማኝ ነው። ለውጥን የሚናፍቅ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ከላይ የተጠቀሱትን ተግባራት ይተግብር።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

No comments: