Saturday, June 27, 2015

ሙሱናን እንደባህል የሚጠቀሙ መሪዎች! የኢኮኖሚ እድገት አያረጋግጡም!!

 June 27,2015

የኢህአዴግ መሪዎች የህዝቡን የኑሮ ደረጃ በእጥፍ እንደጨመረ አስመስለው ቢናገሩም ሃቁ ግን በተቃራኒው አሰከፊ የኑሮ ደረጃ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረና ህዝቡ በድህነት አለንጋ እየተገረፈ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። ከ 24 ዓመት በፊት በቀን ሦስት ግዜ ትመገባለህ ተብሎ ቃል የተገባለትድሃው ህዝብ እስካሁን ድረስ ራሱን መቻል አቅቶት እርዳታ ጠባቂ ሆኖ ሂወቱ ለመምራት ተገዷል።
በአሁኑ ወቅት በመንግስት ስራ ተቀጥሮ የሚሰራው ሲቪል አገልግሎት ሰጪም ቢሆን ምሳ በልቶ ራት የማያገኝ፤ ቁርስ በልቶ ምሳ የማይበላ እጅግ በርካታ ህዝብ መኖሩን የሚካድ አይደለም፣ የሸቀጦች ዋጋ እጅግ በመጨመሩ፤ የሚኖርበት የቤት ኪራይ ዋጋ ከሚከፈለው ደመወዙ ጋር የሚመጣጠን ስላልሆነ በርካሽ ዋጋ ለማግኘት ብሎ ወደ ከተማው ጫፍ እየሄደ ደረጃቸው በወረዱ መኖርያ ቤቶች ውስጥ የሚኖረው ወገን እጅግ በርካታ ነው።
በእርግጥ የኢህአዴግ መሬዎችና አጃቢዎቻቸው ኑሮአቸው ተሻሽለዋል፤ አይተውት የማያውቁት አፓርታማዎች አሰርቷል። እነሱ ከሚኖሩበት ዘመናዊ መኖርያ ቤት ውጭ ለውጭ ዜጎች እያከራዩ በሚልዮን የሚገመት ገንዘብ ውጭ በሚገኙ ባንኮች የሚያስቀሙጥበት ሁኔታ ነው ያለው።
ባለፈው ወር የፀደቀው የአገሪቱ አጠቃላይ የ 2008 ዓ/ም በጀት እጅግ በሚያስገርም ሁኔታ ካለፈው ዓመት ትልቁን የሃገሪቱ በጀት ለመከላከያና ለደህንነት ተመድበዋል፣ ይህ በጀት በሰራዊቱ ደመወዝ ላይ ለውጥ ያመጣበት መንገድም የለም፣ በመሆኑም የተመደበው በጀት ለመሳርያዎች ግዢ፤ ንፁሃን ሰዎችን ለማፈን፤ የህዝቡን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብት ለማኮላሸትና የሰራዊቱ አዛዦችን የተንደላቀቀ ሂወት እንዲያሳልፉበት ተብሎ የሚባክን ሃብት ነው።
ባሁኑ ግዜ አገራችን ለዜጎቿ የምትጠቅም ሳትሆን ለውጭ ዜጎች የምትመችና በርካታ የውጭ ባለሃብቶች በኢንቨስትመንት ምክንያት በርካሽ ዋጋ መሬት እያከራዩና እዚህ ግባ በማይባል ዋጋ የህዝቡን ጉልበት እየበዘበዙ እንደ ፈለጉ ተንደላቅቀው እንዲኖሩና ከፍተኛ ሃብት እንዲሰበስቡ እድሉ ተፈጥሮላቿል። እነዚህ የውጭ ባለሃብቶች ከውጭ የሚያስገቡትን ከፍተኛ ንብረት ኢንቨስተሮችን ለማነሳሳት ተብሎ ተገቢ ግብርና ታክስ እንዲከፍሉ አይደረግም። ኑሮውን ከእጅ ወደ አፍ የሆነው ጭቁኑ ህዝቡ ግን እዚህ ግባ የማይባሉ የንግድ ስራዎች በሚጀምርበት ግዜ ከገቢው ጋር የማይመጣጠን ከፍተኛ ግብር እንዲከፍል ስለሚገደድ እጅና እግሩ አስሮ እንዲቀመጥና ከስራ ውጭ እንዲሆን ተፈርዶበታል።
በሌላ መንገድ ከለጋሽ ሃገሮች የሚመጣ ብድርና እርዳት ተስፋ ተደርጎ የሚገኘውን በጀት። ወደ ልማት ስራዎች ከማዋል ይልቅ ከፍተኛ ገንዘብ በሙሱና መልክ ወደ አመራሮቹ ኪስ እንዲገባ ይደረጋል። ሙሱና ዋነኛውና የማይድን የኢህአዴግ በሽታ መሆኑ የስርዓቱ ከፍተኛ አመራሮች በተለያዩ መድረኮች አምኖውበት ያለፉ የተረጋገጠ ጉዳይ’ዩ።
የአገራችን አብዛኛው በጀት በልማት ስራዎች መዋል ሲገባው ከኢንተርፖል ጋር ተሳስሮ ስርዓቱን የሚቃወሙ ሰዎች ወንጀሎኞች እንደሆኑ አስመስሎ መረጃ በማስተላለና ግለሰቦችን ለመያዝ በሚልዮን የሚገመት ገንዘብ ወጪ በማድረግ፤ ሃቀኛ የሆነ መረጃ የሚያስተላልፉትና የስርዓቱ ብልሹ አሰራርን የሚያጋልጡት የብዙሃን መገናኛዎች በሚልዮን የሚገመት ያገሪቱን ሃብት በማፍሰስ፤ የአገራችን ኢኮኖሚ እድገትና ኑሮ ሊሻሻል የሚችልበት አጋጣሚ ሊኖር አይችልም፣ እናም! በህዝባችን ኑሮ ላይ ለውጥና እድገት ሊረጋገጥ ከተፈለገ ፀረ ልማትና እድገት የሆነው የኢህአዴግ ስርዓት በህዝቡ ትግል ሲገረሰስ ብቻ እንደሆነ አውቀን ለማይቀረው ድል ትጥቃችን አጠናክረን መቀጠል ይገባናል።

No comments: