Thursday, May 21, 2015

ለውጤታማ ድል፤ ተግባራዊ ትብብር!

May 21, 2015
def-thumbበመርህ ላይ በተመሠረተ ትብብር ወያኔን በጋራ ታግሎ ማሸነፍ እና በየደረጃው የሚገኝ የመንግሥት ስልጣን ነፃ፣ ፍትሀዊና ተዓማኒን በሆነ የሕዝብ ምርጫ ብቻ የሚያዝበት የፓለቲካ ሥርዓት መገንባት የአርበኞች ግንቦት 7፡ የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ተልዕኮ ነው። በዚህም መሠረት አርበኞች ግንቦት 7፣ በተግባራዊ እንቅስቃሴ ላይ ከሚገኙት ከትግራይ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ፣ ከጋምቤላ ሕዝብ ነፃነት ንቅናቄ፣ ከቤንሻንጉል ሕዝብ ነፃነት ንቅናቄ እና ከአማራ ዴሞክራሲ ኃይል ንቅናቄ ጋር በመርህ ላይ በተመሠረተ ትብብር በጋራ ለመታገል የሚያስችለውን ስምምነት ላይ እየደረሰ ነው።
ይህ የትብብር ጥረት ብዙ ጉዳዮችን ታሳቢ ያደረገ በመሆኑ የኢትዮጵያን ሕዝብ ጠንካራ ድጋፍ ይሻል።
  1. ህወሓትን ከስልጣን የማባረር ኃላፊነት የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ኃላፊነት ነው። ይህ ትልቅ ኃላፊነት በአንድ ወይም በጥቂት ድርጅቶች ላይ መጣል የለበትም። ይህ ትብብር ይህንን የጋራ ኃላፊነትን በጋራ ለመወጣት የተደረገ በዓይነቱ አዲስ የሆነ ተግባራዊ ትብብር ነው።
  2. ህወሓት በትግራይ ውስጥ መቶ በመቶ ተቀባይነት ያለው አስመስሎ ፕሮፖጋንዳ ሲነዛ ቆይቷል። ህወሓት፣ የትግራይና የአማራ ሕዝብ በጠላትነት እንዲተያዩ፤ የትግራይ ሕዝብ ራሱን ከሌላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነጥሎ እንዲያይ የረዥም ግዜ እቅድ አውጥቶ ተግባራዊ እያደረገ ነው። ይህን እኩይ ሴራ ማክሸፍ የምንችለው በፀረ-ወያኔ ተግባራዊ ትግል በጋራ ስንቆም ነው። ይህ ትብብር ለአገራችን አንድነትና ዘላቂ ሰላም ወሳኝ የሆነው በፀረ ህወሓት አቋሙ የጠነከረ የትግራይ ሕዝብ እንዲኖር ወሳኝ ሚና ይኖረናል ብለን እናምናለን።
  3. በአሁኑ ሰዓት የህወሓት አገዛዝ የቆመው ዘረኛ በሆነ መንገድ ባደራጀው ጦር፣ በስለላ ድርጅቱ እና ኃያላን መንግሥታት ለጥቅማቸው ሲሉ በሚያደርጉለት ሁለተናዊ ድጋፍ ነው። እነዚህ ህወሓትን ደግፈው የያዙ ኃይሎች ጠባቸው ከመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር መሆኑን በተግባር የምናሳያቸው ተግባርን መሠረት ያደረገ ጠንካራ ኅብረት ፈጥረን ስንገኝ ነው።
  4. ኢትዮጵያ ውስጥ ባለው ነባራዊ ማኅበራዊ ሀቅ ምክንያት ከፓለቲካ አመለካከት ይልቅ በወል ማንነት ላይ የተመሠረቱ ድርጅቶች የሚበዙበት ሆኗል። የኢትዮጵያን ችግር ለመፍታት ሁለቱን አመለካከቶች መሠረት አድርገው በተደራጁ ድርጅቶች መካከል ትብብር መፍጠር ወሳኝ ነው።
አርበኞች ግንቦት 7፣ ከላይ በአጭሩ በተዘረዘሩት ምክንያቶች እየተፈጠረ ያለው ትብብር የኢትዮጵያን የፓለቲካ መልካምድር ወደተሻለ ሁኔታ ለመቀየር የራሱ አስተዋጽዖ ይኖረዋል የሚል እምነት አለው። በዚህም ምክንያት መጠናቀቅ የሚገባቸው ነገሮች ተጠናቀው ትብብሩ በይፋ እንዲመሠረት የበኩሉን ጥረት ያደርጋል።
ከላይ በተዘረዘሩት ምክንያቶች ሳቢያ የትብብር አድማሳችን ከዚህም መስፋት አለበት ብሎ አርበኞች ግንቦት 7 ያምናል። ስለሆነም፣ በተለያዩ ምክንያቶች ለጊዜው የትብብር ማዕቀፍ ውስጥ ያልገቡ የፓለቲካ ድርጅቶች ወደ ትብብሩ እንዲመጡ፤ ለሀገራችን እና ለሕዝብ በጋራ መሥራት በምንችላቸው ጉዳዮች ላይ እንድመክር ጥሪውን ያስተላልፋል። በመመካከር ህወሓትን ማስወገድ ብቻ ሳይሆን ለሁላችን የሚበጅ የተሻለ ሥርዓት በአገራችን ላይ እንዲመሠረት መሠረት መጣል እንችላለን ብሎ አርበኞች ግንቦት 7 በጽኑ ያምናል። ስለሆነም እንነጋገር፤ ለሁላችን የሚበጀንን መንገድ በጋራ እንፈልግ፤ የህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝን በጋራ እንታገል፤ ከራሷ ጋር የታረቀች አገር ጥንስስ እኛው ውስጥ እንፍጠር ይላል።
ለውጤታማ ትግል እንተባበር!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

No comments: