Monday, December 15, 2014

በአፈና፣ በኃይል እርምጃና በውንብድና መብታችንን ለድርድር አናቀርብም! ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ መግለጫ

December15,2014
• ትግሉ ተጠናክሮ ይቀጥላል!

እኛ 9 ፓርቲዎች በትብብር ለመሥራት በፈጸምነው ስምምነት ያወጣነውን የጋራ ዕቅድ ለማስፈጸም ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ስንገባ ህገ መንግስቱ፣ የምርጫና የሰላማዊ ሠልፍና ህዝባዊ ስብሰባ አዋጆች በሚፈቅዱት መሰረት ያቀረብናቸውን ጥያቄዎች በቢሮክራሲያዊ ሴራና ማስፈራራት ለማፈን የአዲስ አበባ መስተዳድር የተከተለውን ህገወጥ አካሄድና ይህንኑ ተከትሎ የተወሰዱትን የኃይል እርምጃዎች በሚመለከት ፡- 

1ኛ/ ‹‹በቢሮክራሲያዊ ሴራ የዜጎችን ህገመንግሥታዊ መብት ማፈን ሠላማዊ ትግሉን አያቆመውም !!››በሚል ርዕስ ሕዳር 08 ቀን 2007 ዓ.ም.

2ኛ/ ‹‹ማስፈራራትና አፈና የዲሞክራሲ ጥያቄዎችንና ሠላማዊ ሕዝባዊ የለውጥ ንቅናቄዎችን አይቀለብስም!!›› በሚል ርዕስ ሕዳር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. መግለጫዎች ማውጣታችን፣ እንዲሁም በአባል ፓርቲዎቻችንን አማካኝነት -


1. ‹‹ የህገ መንግሥቱ የበላይነትና የዜጎች ህገ መንግሥታዊ መብት እንዲረጋገጥ ›› ለተከበሩ የተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባኤ፣


2. ‹‹በአገሪቱ ህገመንግሥትና ህጎች የተረጋገጡ የዜጎች መብቶች እንዲተገበሩ ›› ለተከበሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ህዳር 24/2007 ዓ.ም ጥያቄ ማቅረባችንና በግልባጭ ለ- ኢትዮጵያ ሰብዐዊ መብት ኮሚሽን፣- የህዝብ እንባ ጠባቂና -ሰብዐዊ መብት ጉባኤ ማሰማታችን ይታወሳል፡፡


የእነዚህ መግለጫዎችም ሆነ ደብዳቤዎች ይዘት ሲጠቃለል ‹‹የአገሪቱ ህገመንግሥት ይከበር ›› የሚል ጥያቄና መስተዳደሩ በሚወስዳቸው ህገወጥ እርምጃዎች ከያዝነው ህጋዊና ሠላማዊ ትግል የማናፈገፍግና የትኛውንም መስዋዕትነት በመክፈል ለህገመንግሥታዊ መብታችን መከበር የጀመርነውን የጋራ ትግል እንደምንገፋበት፣ የአዲስ አበባ መስተዳድር ከህገ ወጥ ድርጊቱ እንዲታረም፣ ጥሪ ማቅረብና ግልጽ አቋማችንን ማሳየት ነበር፡፡ በዚሁ ሂደት ያጋጠሙንን ህገወጥ ድርጊቶች በሙሉ በዝርዝር ለህዝባችንና ለባለድርሻ አካላት በሙሉ በፕሬስ ሬሊዞችና ዕለታዊ የውሎ ዘገባና ዜናዎች አድርሰናል፡፡ ግን ሰሚ ጆሮ ሊናገኝ አልቻልንም፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳድር የመረጠው መንገድ ለጥያቄዎቻችንና ጥሪዎቻችን ተገቢውን ህጋዊ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ በህገ ወጥ ድርጊቱ መግፋትና ጥያቄዎቹን በኃይል እርምጃ ማፈን ነው፡፡ አፈ ጉባኤውም ሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምንም ባለማለታቸው መስተዳድሩ ‹‹በያዝከው ግፋበት ፈቃድ›› በማግኘቱ ለበለጠ ህገወጥነትና የኃይል እርምጃ በመበረታታት ለህዳር 27 እና 28 ቀን 2007 በጠራነው ህጋዊ ሠላማዊ ሠልፍ ሂደት ላይ በሰጠው ከመንግሥት የማይጠበቅ የቅጥፈት መግለጫ ፣ በዕለቱ በሠላማዊ ዜጎች ላይ በተወሰደው አረመኔኣዊ እርምጃና ጥይት እራሱ ገሎ እራሱ ይጮኃል እንዲሉ በንጹኃን የመብት ጠያቂ ዜጎች ላይ የተለመደውን የፈጠራ ክስ ለመፈብረክ በተጠቀመው ነጭ ውሸት አረጋግጧል ፡፡ የአብነት ማሳያዎችም--


1. ኢቲቪ/ኢብኮ/ ሰሚ ባላገኘው የ‹‹ማስፈራሪያ›› ማስጠንቀቂያው ‹‹በሌላ ቦታ እንዲያደርጉ›› የቀረበላቸውን አማራጭ ባለመቀበልና እዚያው ካልሆነ ሞተን እንገኛለን በማለት ‹‹አሉ›› ያለው እኛ ዓርብ(26/03/07) ከሰዓት በኋላ እስከ ቀኑ 10፡30 ድረስ ውሳኔ ከማይሰጡ (ሥልጣኑ ከሌላቸው) የመስተዳድሩ ሹማምነት ጋር ቆይተን ‹‹የማሪያም በር›› ልንሰጣቸው ከሞከርነው ጋር የማይጣጣምና መግለጫው ‹‹ ባይበላስ ቢቀር›› የሚያስብል መሆኑ፤


2. ከ80 በላይ ንጹኃን የመብት ጤቂ ዜጎች ላይ የተፈፀመው እስራትና ከ50 በላይ በሆኑት ላይ የ ለማመንና መቀበል የሚያስቸግርና (በተለይ በሴት እህቶቻችን ላይ)አረመኔያዊ ድብደባ (ፖሊስ ጣቢያ ግቢ ውስጥ ጭምር) በተፈጸመበት የተሞከረው ‹‹ ከባድ የኮንስትራክሽን መሣሪያ በኪሳቸው ደብቀው›› ልማቱን አደናቀፉ ዓይነት የፈጠራ ውንጀላና ክስ ማቅረባቸውን፤ መጥቀስ ብቻ ይበቃል፡፡


በመሆኑም መስተዳድሩ ከሠልፉ ዕለት በፊትና እስከዛሬ እነዚህን ዓይን ያወጡ ህገመንግሥቱን የደፈጠጡ የአደባባይ እውነታዎች ለመሸፈን በፓርቲዎች ላይ በተለመደው መንገድ በህዝብ ሃብት የሚተዳደሩትን የመንግሥት መገናኛ ብዙሃን በተለይም ኢቲቪ/ኢብኮ/ በመጠቀም በሰራው የበሬ ወለደ ፕሮፖጋንዳ ማንነቱን ፍንትው አድርጎ ለህዝብ አሳይቷል፣ ራቁቱን አስቀርቶታል፣ተጋልጦበታል፡፡


በእኛ በኩል ከሂደቱም ሆነ ከተወሰደው እርምጃና ከተሞከረው ርካሽ ፕሮፖጋንዳ ለቀጣዩ የጋራ ትግላችን ብዙ ተምረንበታል፤ አስተምረናል፣አትርፈንበታል እንጂ ከዓላማችን አልተገታንም፣ ቃላችንን አላጠፍንም፡፡በመሆኑም


1. ከዚህ በኋላ ለሰልፍም ሆነ ስብሰባ ገዢው ፓርቲ በዘመናት በማለማመድ ፈቃጅ ሆኖ ለመታየት ያደረገውን ጥረት ሰብረን ዕውቅና ከመስጠት ያለፈ ህጋዊ ሥልጣን የሌለው መሆኑን እንዲያውቅ/እንዲማር አድርገናል፤


2. በማስፈራራት ትግሉን መግታት እንደማይቻልና ለዚህም ለነጻነታቸውና ክብራቸው የቱንም መስዋዕትነት ለመክፈል የተዘጋጁ ታጋዮች በተለይም ወጣቶች መኖራቸውን አሳይተናል፤


3. የህዝቡ የለውጥ ፍላጎት የደረሰበትን ደረጃና የንቃተ ኅሊና መዳበር ከክልል ጭምር በመምጣት በጋራ ትግሉ በመሳተፍና የትግል አጋርነታቸውን በመግለጽ ባደረጉት አስተዋጽኦና በመንግሥት መገናኛ ብዙሃን ፕሮፖጋንዳ ያለው እምነት መሟጠጡን ፣እንዲሁም የገዢው ፓርቲ በሠላማዊ ትግል ያደረበትን የፍርኃትና ሥጋት ደረጃ ለክተንበታል፤


4. ህዝቡ ለፈጠራ ወንጀሎች እንዳይፈራና ይልቁንም በመንግሥት አሠራርና አመራር ላይ ያለው እምነት ከጥያቄ እንዲወድቅ፤ፖሊስንና ፍርድ ቤቶችን ጨምሮ አስፈጻሚ አካላት ያለባቸውን ተጠያቂነት እንዲረዱና ራሳቸውን እንዲጠይቁ የሚያስችል ስሜት ፈጥረናል፤


በአጠቃላይ የገዢውን ፓርቲ እየባሰ የመጣውን አምባገነናዊ ባህሪይ አጋልጠን ፣ኢትዮጵያዊያን ለተባበረ የጋራ ትግል ያላቸውን ድጋፍ በተግባር ተመልክተን፣ የጀመርነው የ‹‹ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ›› ፕሮግራማችንን ትክክለኛለትና ተቀባይነት ለክተን ትግሉ ወደማይቀለበስበት የላቀ ደረጃ መሸጋገሩን አረጋግጠናል፡፡ስለሆነም የጋራ ትግላችንን አጠናክረን በበለጠ ጽናትና የኃላፊነት መንፈስ በጥበብ በመምራት እንደምንቀጥል እያረጋገጥን የሁለተኛውን ዙር ፕሮግራም ዕቅድ በቅርብ ጊዜ እንደምናሳውቅ እየገለጽን -


1ኛ/ በአገር ቤትና በውጪ የምትገኙ ኢትዮጵያዊያን በሙሉ ከጎናችን በመቆም ላደረጋችሁት ሁለንተናዊ ድጋፍ፣ በአምባገነኑ ሥርኣት የተወሰደብንን አረመኔያዊ እርምጃ በመቃወም በሰልፍ፣ በመግለጫ፣በታሰርንበት አስፈላጊውን በማቅረብና ተመላልሳችሁ በመጠየቅ … የትግሉ ባለቤትነታችሁን ላረጋገጣችሁና አጋርነታችሁን ለገለጻችሁና ላኮራችሁን ክፍ ያለ ምስጋናችን እያቀረብን፣በዚህ ረገድ ድምጻችንን ከህዝባችንና ከዓለም ህዝብ ዘንድ በማድረስ ፣ከወገኖቻችን ጋር በማወያየት ከፍተኛውን ሚና ለተጫወታችሁ በአገር ቤትና በውጪ ለምትገኙ መገናኛ ብዙኃን አድናቆታችንን እየገለጽን በቀጣዩ ፕሮግራማችንም ከጎናችን እንድትቆሙ ፣


2ኛ/ገዢው ፓርቲ/መንግሥት የወሰደውን ኢህገመንግሥታዊና ህገወጥ እርምጃና አሰራር አጥብቀን እየተቃወምን፣ይህ ዓይነቱን ለማንም የማይበጅ አካሄድ መርምሮና የህዝቡን የለውጥ ፍላጎት ተረድቶ ቆም ብሎ ራሱን እንዲፈትሽ፣ከገባበት ፍርኃትና ሥጋት ተላቆ ለህዝብ ጥያቄዎች ተገቢውን ወቅታዊ ምላሽ በመስጠት ህገመንግሥቱን አክብሮ እንዲያስከብር፤


3ኛ/ የዓለም አቀፉ ማኅበረ ሰብ አባላትም ተገቢውን አዎንታዊ ተጽዕኖ በገዢው ፓርቲ/መንግሥት ላይ በማሳረፍ ለሰብዐዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች መከበርና ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የበኩላችሁን አስተዋጽኦ እንድታበረክቱ፤ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

ያለመስዋዕትነት ድል የለምና ትግሉ ተጠናክሮ ይቀጥላል!

No comments: