Monday, October 27, 2014

የ “ካዛንችሱ መንግስት በአዲሰ አበባ ማዘጋጃ ቤት” – ከግርማ ሰይፉ ማሩ

October 27.2014
ዛሬ ጥቅምት 17/ 2007 እግር ጥሎኝ አዲሰ አበባ ማዘጋጃ ቤት ጎራ ብዬ ነበር፡፡ የታዘብኩት ነገር ያስታወኝ ኤርሚያስ ለገስ “የመለስ ትሩፋቶች” በሚል ባወጣው መፅሃፍ ውስጥ “የካዛንችስ መንግሰት” ብሎ ያስነበበንን በገሃድ ከካዛንችስ ቦታ ቀይሮ አዲስ አበባ መስተዳደር ግቢ ውስጥ መኖሩን ነው፡፡ የካዛንችሱ መንግሰት ምን እንደሚሰራ እዚህ መዘርዘር አይጠበቅብኝም፤ በጥቅሉ ግን የአዲስ አበባ ህዝብ “መርጦ” ወይም ቀጥሮ ያስቀመጣቸው ሰዎች ሳይሆን ውሳኔ የሚስጡት ሌሎች በስውር በደህንነት ስም በኢህአዴግ የተቀመጡ ሰውር እጆች መሆናቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
እነዚህ ሰውር እጆች ለእኛ ለተቃዋሚዎች አዲስ አይደሉም ለምሳሌ፤
· በሆቴሎች አዳራሽ ለማከራየት አንችልም ምንም ጠቃሚ ገንዘብ ቢሆን ሆቴሎች ፈቃደኞች አይደለም፤
· ማተሚያ ቤቶች የተቃዋሚ ፓርቲዎች ወይም እነርሱን ይደግፋሉ የሚባሉ የግል ጋዜጦችና መፅሄቶች አያትሙም
· መብራት ኃይል ለአንድነት የማተሚያ ማሽን ሊያንቀሳቅስ የሚችል የኤሌትሪክ ሀይል (ሰሪ ፌዝ የሚባል ሀይል) ለፓርቲ ለማስገባት ፈቃደኛ አይደለም፤
· ቤት አከራዮች ቤታቸውን ለማከራየት ይፈራሉ፤
· በቅስቀሳ ጊዜ መኪና እና የድምፅ መሳሪያዎች ማግኘት ፈተና ነው፤
· ለቅስቀሳ የወጡ ሰዎች እንደ በግ በየጣቢያው ሲታሰሩ የሚያስሩት ሰዎች በግልፅ ዩኒፎርም የለበሱት ፖሊሶች ሳይሆኑ በሬዲዮ የሚያዙ ማን እንደሆኑ የማይታወቁ ናቸው፤ ወዘተ ይህ ሁሉ የሚሆነው በህግ አግባብ ሳይሆን በሰውር መንግስት ውስጥ ያሉ ሰውር እጆች የሚሰሩት ነው፡፡
ለዛሬ ፅሁፌ መነሻ የሆነኝ ግን በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር የህዝባዊ ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል ኦፌሰር የሆኑት አቶ ማርቆስ ብዙነህ የሰጡን ምላሽ ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ በቀጣይ ፓርቲው በሚያደርገው እንቅስቃሴዎች የፓርቲ አባላትን በስነ ምግባር የታነፁ እና ሰላማዊ ትግል በሰለጠነ መንገድ የሚደረግና በግብግብ ሳይሆን በሃሳብ የበላይነት የተመሰረተ እንዲሆን ለማድረግ ለሚያካሂደው ስልጠና ለማካሄድ አዳራሽ ለመከራየት ባቀረብነው ጥያቄ በጎ ምላሽ እንደሌለ ከውስጥ ሰምተን ምክንያቱን በግንባር ለማወቅ ሄጄ የሰማሁት ምላሽ በአንድ መንግሰታዊ ተቋም ውስጥ ተቀጥሮ ደሞዝ ከሚበላ ሲቪል ሰራተኛ የሚጠበቅ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ የሰጡን ምላሽ “አራት ሰዎች መጥተው ፍቃዱ እንዳይስጥ ጠይቀው አለቃይ እንዳትሰጥ ስለአለኝ ነው የሚል ነው፡፡” በቃ ይህ ነው ምክንያቱ፡፡ አንድነት ፓርቲ ይህን ፈቃዳ ላለማግኘት አንድም ያጎደለው መስፈርት የለም፡፡ አቶ ማርቆስ አለቃቸው ይህን መልስ ሲሰጣቸው ለምን? እንዴት ብዬ? ከመመሪያ አንጻር ልክ አይደለም ብለው አይጠይቁም፡፡ አለቃቸውንም አይሞግቱም፡፡ እርሳቸውም የሚያውቁት አለቃቸውም ቢሆን እራሳቸው እንደማይወስኑ፡፡ የሚወስነው ይህ ስውር እጅ ያለው ካዛንችስ የነበረው አሁን በመስተዳድር ቅፅር ግቢ የሚገኘው መንግሰት እንደሆነ፡፡
አንድ መስሪያ ቤት ሰራውን የሚሰራው በአዋጅ በተሰጠው ስልጣን በደንብ እና መመሪያ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ኦፊሰሮች ተግባራቸውን ሲያከናውኑ ደግሞ እነዚህ የህግ ማዕቀፎች መሰረት አድረገው ነው ብለን እንጠብቃለን፡፡ በዚህች ምስኪን ሀገር ግን ይህ ምፀት ነው፡፡ በህግ ማዕቀፍ የሚሰራ ኦፊስር ማግኘት ዘበት እየሆነ መጥቶዋል፡፡ አለቃው በቃል አድርግ ያለውን የሚያደርግ የማርቆስ ዓይነት ኦፊሰር ሞልቶ ተርፎዋል፡፡ በጣም የሚገርመኝ የዚህ ዓይነት ኦፊሰሮች ለልጆቻቸው ሰራ ሄጃላሁ የሚሉ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ባይሉ
ዋቸው ደግ ነው፡፡ ይህን ሊያደርጉ መሄዳቸውን ሲያውቁ ያፍሩባቸዋል ብዬ ስለማስብ ነው፡፡ ለምን ለልጆቻችን ማፈሪያ እንደምንሆን አይገባኝም፡፡
መልካም አስተዳደር አስፍናለሁ የሚል መንግሰት መልካም አሰተዳደር የሚሰፍነው በአዳራሽ ኮፍያና ቲ ሸርት ለብሶ በሚደረግ ዲስኩር እንዳልሆነ የገባው አይመስለም፡፡ መልካም አስተዳደር የሚሰፍነው በህግ ማዕቀፍ አገልግሎት የሚሰጥ ሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛ አገልግሎት ሲሰጥ እንጂ በስውር በቃል በሚሰጥ ትዕዛዝ እንዳለሆነ መረዳት ይኖርብናል፡፡ ማርቆስ በሚሰጠው መልስ እየተበሳጨ፣ እያዘነ ሲከፋውም እየተሳደበ የሚሄድ ተገልጋይ መዘዝ እንደሚያመጠ ግን የገባቸው አይመስለኝም፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው ደግሞ በስውር መንግሰት በዚህ መንገድ እንዲሆን ስለሚፈልግ ነው፡፡
ዛሬ በግልፅ የተረዳሁት በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ብሎም በሀገር አቀፍ ደረጃ መልካም አስተዳደር የማሰፈን ችግር ምንጭ በደህንነት ስም በስውር ያለው መንግሰት የሚሰጠው ትዕዛዝ ሲሆን፣ ሲቀጥልም አድርግ ያሉትን ለማድረግ በተጠንቀቅ ዝግጁ የሆነው የማርቆስ ዓይነት ደሞዝ እየበሉ ያሉ ሲቪል ሰራተኞች ናቸው፡፡ አለቃዬ እንዲህ አድርግ ብሎኝ ነው በሚል መመሪያን መሰረት ያላደረግ ትዕዛዝ የሚሰፈፅሙ የማርቆስ ዓይነት ኦፊሰሮች የዚህች ሀገር መከራ እንዲረዝም፣ ህዝቡ የመልካም አስተዳደር ትሩፋት እንዳያገኝ ተባባሪ እንደሆኑ አበክረን መንገር ይኖርብናል፡፡ ይህንን አሜን ብሎ የተቀበለ ህዝብ መከራውና ግፉ ተስማምቶኛል እንዳለ ይቆጠራል፡፡ የዚህ ዓይነት ህዝብ ደግሞ ምንም ዓይነት አንባገነን መንግስት ቢመጣ የሚገባው ነው ማለት ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ኢህአዴግ አይመጥነንም ያለ ህዝብ በቃ!!!! ሊለው ይገባል፡፡ ኢህአዴግ በቃ ሊባል ይገባል!!!!
ቸር ይግጠምን

No comments: