Sunday, July 27, 2014

“በኢትዮጵያዊነት ማንም ከኦሮሞዎች አይበልጥም፤ ኦርጅናል ኢትዮጵያውያን ነን” – አቶ ቡልቻ ደመቅሳ

July27/2014
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ለረጂም ዓመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ተሳትፏቸው ይታወቃሉ፤ በተለይም የኦሮሞን ህዝብ መብት እናስከብራለን ብለው የፖለቲካ ፓርቲ መስርተው ከታገሉት ሰዎች መካከል ከፊተኞቹ አንዱ ናቸው፡፡ አቶ ቡልቻ አሁን ስላሉበት የፖለቲካ ተሳትፏቸውና ስለተለያዩ አንኳር ሀገራዊ ጉዳዮች ከጋዜጠኛ በላይ ማናዬ ጋር ቆይታ አድርገዋል፤ እንዲህ ይቀርባል፡-
Ato Bulcha
ነገረ ኢትዮጵያ፡- አቶ ቡልቻ በተለያዩ መድረኮች ላይ በፖለቲካ ተሳትፎዎ ነው የሚታወቁት፤ ነገር ግን አሁን ላይ ከፓርቲ ፖለቲካ ተሳትፎ የራቁ ይመስለኛል፡፡ በዚህ ወቅት ስላልዎት የፖለቲካ ተሳትፎዎ በአጭሩ ቢነግሩኝ?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ ከመድረክ የገባሁት የኦፌኮ መሪ ሆኜ ነው፡፡ አሁን የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ (ኦፌኮ) እስኪ ወጣቶቹ ይስሩ፣ እነሱ ሲሰሩ የሚቻለኝን እርዳታ አደርጋለሁ ብዬ በራሴ ፈቃድ ከፓርቲ ፖለቲካ ወጥቻለሁ፡፡ ‹‹Retire››  አድርጌያለሁ፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን ጤናማ ነኝ፡፡ በእድሜየ በኩል 83 አመቴ ነው፡፡ በትምህርትም ሆነ በተፈጥሮ ስጦታ ትልቅ አቅም ያላቸው ልጆች ስላሉ እኔ በዚህ እድሜዬ መድከም የለብኝም ብዬ ነው የለቀቅኩት፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ስለዚህ አሁን የቱንም የፖለቲካ ድርጅት አይወክሉም ማለት ነው?
አቶ ቡልቻ፡- ልክ ነው! በግሌ ነው የምንቀሳቀሰው፡፡ አሁን ምንም አልወክልም፡፡ አስተያየትም የምሰጠው፣ ንግግርም የማደርገው በግሌ ነው፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- መድረክ በቅርቡ አዲስ አበባ ውስጥ ሰላማዊ ሰልፍ ባደረገበት ወቅት ንግግር ሲያደርጉ በቦታው ነበርኩ፡፡ ‹‹በጋራ መምጣት ከፈለግን አንድ መሆን አለብን›› የሚል ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ምን ለማለት ፈልገው እንደሆነ ሊያብራሩልኝ ይችላሉ?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ ማለት የፈለኩት፤ የኢትዮጵያ ብሄሮች (ብሄሮች አሉ፡፡ የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ብሄሮች እንደለሉ መናገር ችግር የለውም የሚሉ ቢኖሩም ተሳስተዋል፡፡ እኛ አይደለም የምንፈጥራቸው፡፡ እነሱ አሉ፡፡) መኖራቸውን አውቆ ከእነሱ ወኪሎች ጋር መነጋገር ነው፡፡ ኢትዮጵያ መነጋገሯ
አይደለም፡፡ የብሄሮች ወኪሎች ተነጋገሩ ማለት ኢትዮጵያ ተነጋገረች ማለት ነው በውስጧ፡፡ የተለያዩ የፖለቲካ መስመር የሚከተሉ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ማለት የአንድ ማህበረሰብ ሰዎች አንድ አይነት ፖለቲካ ይከተሉ ማለት አይደለም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በጎሳ ወይም በብሄር የተደራጁት አካላት ትክክል አይደሉም የሚሉ ሰዎች አሉ፤ ብሄር ማለት ሀገር ማለት ነውና ከቃሉ ጀምሮ ትክክል አይደለም ይላሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ…ለእርስዎ ብሄር ማን ነው? ብሄረሰብስ የትኞቹ ናቸው?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ ‹‹ብሄር›› የሚባለውን ቃል የሰማሁት የ19ና 20 አመት ሆኜ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት፡፡ አንድ አራት ኪሎ ይገኝ የነበር ተስፋ ገብረስላሴ የተባለ ሰው ማተሚያ ቤት ነበር፡፡ ያ ማተሚያ ቤት ‹‹ተስፋ ገብረስላሴ ዘ ብሄረ ቡልጋ›› ይል ነበር፡፡ ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጠይቄ አሁን የምረዳውን ተረዳሁ፡፡ ብሄር ማለት አሁንም እንደምንሰማው የአንድ ብዙ ወይንም አነስ ያለ ህዝብ አንድነት፣ ወይንም ማንነት ማለት ነው፡፡ ምንም አያስቸግረኝም፣ አስቸግሮኝ አያውቅም፡፡ ብሄር ማለት የህዝብ መገለጫ ማለት ነው፡፡
bulcha_demeksa
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ህዝብ የተለያየና አንጻራዊ መገለጫዎች ይኖሩታል፡፡ በዚህ መሰረት እንደ ኢትዮጵያ የጋራ መገለጫ አይኖረንም? ‹ብሄር› የሚባሉት ቡድኖች መገለጫቸው ድንበር ሲያጣ ይታያል፡፡ ስለዚህ በጋራ የምንጋራቸውን ማንነቶችስ ምን ልንላቸው ነው?
አቶ ቡልቻ፡- ኢትዮጵያ ብቻ አይደለችም በዓለም ላይ ብዙ ሀገራት አሉ፡፡ በተባበሩት መንግስታት ላይ ያየኸው እንደሆነ 198 ነው ሀገራት አሉ፡፡ ኢትዮጵያ ከእነዚህ ሀገራት አንዷ ናት፡፡ እኔ ከእነዚያ መካከል አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ ዜጋ ነኝ፡፡ ልክ አንድ ቤተሰብ ብዙ ሰው እንደሚኖረው እኛም ሀገራችን ውስጥ ስንገባ ብዙ አይነት ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እገሌ ብሄር፣ እገሌ ደግሞ ብሄረሰብ ነው ብለው በምሳሌ ሊያስረዱኝ ይችላሉ?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ እንደሚገባኝ ነው የምሰጥህ፡፡ ኦሮሞ ማለት ኦሮምኛ የሚናገር፣ በምስራቅ፣ መካከለኛውና ምዕራብ ኢትዮጵያ የሚኖር፣ አብዛኛውን ጊዜ ግብርና መኖሪያቸው የሆነ መልካቸው (ከሌላው ኢትዮጵያውያን ይለያል አልልም) ጥቁርም አይደሉም፣ ቀይም አይደሉም፡፡ ብዙው የኢትዮጵያ ህዝብ እንደዚህ ነው፡፡ ኦሮሞ እንዲህ አይነት ህዝብ ነው፡፡ ውስጥ የገባህ እንደሆነ ስነ ልቦና፣ የጋራ አመለካከት የመሳሰሉ የእያንዳንዱ ሰው ፍርድ አለ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- አንዳንድ ፖለቲከኞች ‹‹ብሄር›› የሚባሉትን ጎሳ፣ እንዲሁም ድርጅቶችን ‹‹የጎሳ ድርጅት›› ይሏቸዋል፡፡ እርስዎ ይስማማሉ?
አቶ ቡልቻ፡- አልስማማም! ጎሳ ሌላ ነው፡፡ እኔ የአማርኛ ሊቅ ባልሆንም መናገር እችላለሁ፡፡ ጎሳ የሚባል ቃል፤ እኔ እንጃ?! ኦሮሞ ጎሳ ነው እንዴ? ኦሮሞ ጎሳ አይደለም! አንድ ህዝብ ነው፣ ጎሳ አይደለም፡፡ ምን አልባት የሚዛመዱትን ከሆነ ኦሮሞ ውስጥ ብዙ እርስ በእርሳቸው የሚዛመዱ አሉ፡፡ እኔ በተወለድኩበት ወለጋ ውስጥ በራሱ ብዙ ብዙ ጎሳዎች አሉ፡፡ ጎሳ እንኳ ብዙም ትርጉም የለውም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እንደ ሩዋንዳ ያሉ ሀገራት አንድን ህዝብ ቋንቋን ወይም ጎሳን መሰረት አድርጎ በፖለቲካ ማደራጀት በህግ ከልክለዋል፡፡ በጎሳ መደራጀት በተለይ በፖለቲካ ፓርቲ ደረጃ ምን ያህል ያስኬዳል? ለሀገር አንድነትስ ተጽዕኖ አይኖረውም?
bulcha_demeksaአቶ ቡልቻ፡- እኔ እንደሚመስለኝ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ዘጠና ሚሊዮን ህዝብ ነው የሚኖረው፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን መታወቂያ ስለሰጠን እንጂ ካለዚያማ ማን ምን እንደሆነም አይታወቅም፡፡ አሁን ግን አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ.. በጣም ደስ የሚል መግለጫ፡፡ እሱማ ባይኖር ማን ነበር የምንባለው? የትግሬ ህዝብ በራሱ መሪዎቹን መርጦ ወደ ዋናው ከተማ ይመጣል፡፡ ኦሮሞ በራሱ ክልል የራሱን መሪዎች መርጦ ወደ አዲስ አበባ ይመጣል፡፡ እነዚህ መሪዎች ኢትዮጵያን እንዴት እንምራት ብለው ሊስማሙ ይችላሉ፡፡ ሊነጋገሩ ይችላሉ፡፡ አንድ ህዝብ በስሙ መጠራቱ ምን ከፋ? ችግሩ እኛ ኢትዮጵያውያን አይደለንም ሲባል ነው፡፡ ህወሓት፣ ኦነግና አሁን ኢህአዴግ ውስጥ ያለው የአማራ ድርጅት ኢትዮጵያዊ አይደለንም ይሉ ነበር፡፡ ችግሩ የሚመጣው እንዲህ ሲሆን ነው፡፡ ይህ ሳይሆን በስሙ ተጠርቶ፣ ከሌሎች የኢትዮጵያ ዜጎች ጋር ተዋዶና ተፋቅሮ፣ እየተረዳዳ፣ እየሰራ ቢኖር ምን
ችግር አለው?
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እርስዎ በፓርቲ ደረጃና በግል እንደሚታገሉለት የሚናገሩለት የኦሮሞ ህዝብ ሰፊ መሰረት ያለው መሆኑ ይታወቃል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ሰፊ መሰረት ያለው ሆኖ እያለ በቋንቋ በመደራጀት መብቱን አስከብራለሁ ማለት ለክብሩ የሚመጥን አይደለም የሚሉ አካላት አሉ፡፡ የኦሮሞ ህዝብ በቋንቋ ከመደራጀት ይልቅ በህብረ ብሄራዊነት ተደራጅቶ በኢትዮጵያ የተሻለ ለውጥ ማምጣት አይችልም? በአንድ ክልል፣ በአንድ ማዕቀፍ ብቻ ተወስኖ መደራጀት ለክብሩ የሚመጥን ነው ብለው ያስባሉ?
አቶ ቡልቻ፡- የኦሮሞ ህዝብ ከ37 እስከ 40 ሚሊዮን የሚሆን ህዝብ ነው፡፡ ግን አዋቂዎችና የተማሩት የሚሉትን ልንገርህ፡፡ እኛ የኢትዮጵያ አካል ነን፡፡ የትም መሄድ አንፈልግም፡፡ ኦሮምኛ እንናገራለን፡፡ ግን ኢትዮጵያውያኖች ነን፡፡ በኢትዮጵያዊነት ማንም ከእኛ አይበልጥም፡፡ እኩል ነን፡፡ እገዛችኋለሁ፣ እበልጣችኋለሁ፣ ቋንቋችሁን አፍናለሁ፣ የሚሉ ካሉ እንታገላቸዋለን፡፡ እንጂ የትም አንሄድም፡፡ አገራችንን ትተን የት እንሄዳለን? ዛፍ እንኳ ስታየው ቅርንጫፉ ነው የሚወድቀው፡፡ ዋናው ግንድ ይቆማል፡፡ ኦሮሞ ግንድ ነው፡፡ ማንም ሰው ለኦሮሞ አንተ እንዲህ ነህ፣ አንተ እንዲህ ነህ ብሎ ሊነግረው አይችልም፡፡ ኦሮሞ ምን እንደሆነ ራሱን ያውቃል፡፡ እንዲያውም ኦሮሞ ይህ ሀገር የእኔ ነው፣ ከሌሎች ጋር ተጋርቼ እኖራለሁ ብሎ ነው የሚያምነው፡፡ ስለዚህ ነው እንገነጠላለን የሚሉ ሰዎች ያልተሳካላቸው፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ታዲያ ኦሮሞ ግንድ ሆኖ እያለ እንደ ቅርንጫፍ ነጥሎና ጠበብ አድርጎ መደራጀት ለምን አስፈለገ?
አቶ ቡልቻ፡- ኦሮሞዎች፣ እኛ ኦርጅናል ኢትዮጵያውያን ነን፡፡ ኢትዮጵያውያን ሆነን ግን ለፖለቲካና ማህበራዊ ህይወት እንደራጃለን፡፡ ቋንቋችን ስንናገር ነው የምንግባባው፡፡ አማርኛም እንናገራለን፣ ነገር ግን አማርኛም የማያውቅ አለ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ለምን ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ አማራ፣ ጉራጌ ተብሎ ይጠራል
ብለው የሚከራከሩት አብዛኛውን ጊዜ የቀድሞ የሹማምንት ልጆች ናቸው፡፡ የግራአዝማቹ፣ የቀኝአዝማቹ፣ የራሱ የቀኝአዝማቹ ዝምድና ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነሱ የሚመኙት ወደ ድሮው፣ ወደመሪነት፣ ወደማዘዝ ቦታ ነው የሚመኙት፡፡ የፌደራል ጉዳይ ደግሞ ይነሳል፡፡ ለምንድን ነው ሁላችንም አንድ አዳራሽ ውስጥ የማንኖረው? ለምንድን ነው እያንዳንዱ ሰው ከሌላው ተወዳድሮ ቆንጆ ቤት ሰርቶ ለብቻው የሚኖረው? ፌደሬሽን የሚጠሉ ሰዎች ምንድን ነው የሚፈልጉት? በ1983 ዓ.ም ፌደራሊዝም ከመገንጠል ይሻላል ተብሎ እኮ ነው የመረጥነው፡፡ ያኔ ሁሉም፤ ኦነግም፣ ህወሓትም፣ አማራም፣ ሲዳማም… ሁሉም ብሄር ፌደራሊዝምን የመረጥነው እንገነጠላለን የሚሉትን ሰዎች ለማሸነፍ ነው፡፡ እኔ ኢትዮጵያ ከፌደራሊዝም ውጭ ተስፋ አላት ብዬ አላምንም፡፡
bulcha
ነገረ ኢትዮጵያ፡- አሁንም ቢሆን ከፌደራሊዝም ውጭ አማራጭ ይዞ የመጣ የፖለቲካ ፓርቲ ያለ አይመስለኝም፡፡ ልዩነቱ በቋንቋ/ጎሳ/ብሄር ከሚሆን ይልቅ አስተዳደራዊ አመችነትና ሌሎች መስፈርቶች መታየት አለባቸው የሚል ነው፡፡ እርስዎ አሁን እንደሚናገሩት ግን ኢህአዴግ የሚጠቀምበት ቋንቋን መሰረት ያደረገ አወቃቀር እንዲቀጥል የፈለጉ ይመስለኛል?
አቶ ቡልቻ፡- አዎ! አማራጭም የለውም፡፡ ታዲያ በምን የተመሰረተ ድርጅት ሊሆን ነው? በቋንቋው፣ በባህሉ፣ በሚኖርበት አካባቢ የፖለቲካ ድርጅት ቢያቋቁም ምን ይጎዳል? ለምንድን ነው የሚጠላው? አሁን እነሱ የሚሉት በዘር ሳይሆን በወንዝ፣ በተራራ፣ አንዳንድ ዳርቻዎችን በመጥቀስ ነው፡፡ ለምሳሌ በአጼ ኃይለስላሴ ጊዜ ሸዋ አማራም፣ ኦሮሞም ነበረበት፡፡ በዛን ጊዜ ሀገረ ገዥው ራስ መስፍን ነበሩ፡፡ እኔ አውቃቸዋለሁ፡፡ በጣም ጥሩ ሰው ነበሩ፡፡ በጣም ትሁት፣ ሩህሩህና ፍትህ የሚያውቁ ሰው ነበሩ፡፡ እሳቸው አማራ ነበሩ፡፡ ኦሮሞዎቹ እንደልባቸው ራስ መስፍን ጋር አይመሩም፣ ራስ መስፍንን አያማክሩም፡፡ አማራ የሆኑት የሸዋ ሰዎች ግን ራስ መስፍንን እንደራሳቸው መሪ፣ እንደራሳቸው ሀገረ ገዥ፣ እንደራሳቸው እንደራሴ አድርገው ነበር የሚያዩት፡፡ ይህ ራሴ በህይወቴ ያየሁት ገጠመኝ ነው፡፡ ህዝብ የሚፈልገውን ያውቃል፡፡ ከፌደራሊዝም ውጭ አማራጭ የለንም፡፡ ፌደራሊዝምን በደንብ መምራት የመንግስት ፋንታ ነው፡፡ ፌደራሊዝም በሚመራበት ወቅት የኦሮሞ ህዝብ ‹ራስ መስፍን የእኛ አይደሉም› እንዳሉት እንዳይሆን መደረግ አለበት፡፡ የአዲስ አበባ መንግስት ሁሉንም ሰው በእኩልነትና በፍርድ የያዘ እንደሆነ ፌደራሊዝም ጥሩ አማራጭ ይሆናል፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ፌደራሊዝሙ በቋንቋ መዋቀሩ እንደ ችግር ተብሎ የሚነሳው ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ‹‹ሀገራችሁ አይደለም ውጡ›› እንደሚባሉ በመጥቀስ ነው፡፡ በደቡብና ቤንሻንጉል እየታየ ያለውንም እንደማሳያ ይጠቅሳሉ፤ እና…
አቶ ቡልቻ፡- እሱን በጭራሽ አልደግፍም፡፡ እሱን በመመካከር፣ በአስተዳደር፣ በፖለቲካ፣ አንድም ነገር ሳይደበቅ መነጋገርና መወያየት ያስፈልጋል፡፡ ግልጹን ማውጣት ነው የሚጠቅመው፡፡ ለምሳሌ ከወለጋ አማራዎችን አንስተዋቸዋል ይባላል፡፡ ውሸት መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ግድ የለም አስነሷቸው እንበል፡፡ ታዲያ ለምንድን ነው የምታስነሷቸው ብሎ መጠየቅ ነው? ኢትዮጵያውያን የትም ሄደው መስራትና መኖር አለባቸው፡፡ በመሆኑም ማፈናቀል ካለ ለወደፊት ወንጀል ተደርጎ መወሰድ አለበት፡፡ አንድ ብሄር ሌላኛውን ይህ ያንተ አይደለም፤ ከሌላ ነው የመጣኸው ብሎ ሲያፈናቅል የሚቀጣበትን አግባብ መፈለግ ነው ያለብን፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በአንቦና በሌሎች አካባቢዎች ግጭት ለመነሳቱ ቀዳሚው ምክንያት የኦሮሚያ መሬት ሊወስድ ነው፣ አርሶ አደሮች ሊፈናቀሉ ነው በሚል ነበር ይታወል፡፡ በአንድ በኩል አዲስ አበባ የኦሮሞ ነች እየተባለ በሌላ መልኩ ደግሞ የኦሮምያ መሬት ለአዲስ አበባ ሊሰጥ ነው ማለት እርስ በእርሱ አይጋጭም?
አቶ ቡልቻ፡- እንደ እኔ ይህንን ጣጣ ያመጡት በፌደራል መንግስቱ ውስጥ የሚሰሩ አንዳንድ ባለስልጣናት ናቸው፡፡ እርግጥ ነው ኦሮሞ መሬቱ በአዲስ አበባ እንዲወሰድ አይፈለግም፡፡ ምክንያቱም የጋራ ጥቅም ነው፡፡ አሜሪካም ውስጥ እንዲህ አይነት ጭቅጭቅ አለ፡፡ ትልልቅ የመንግስት ስራዎች ሲሰሩ አንዱ ስቴት ይመረጣል፡፡ ለመንግስት ስራ የተመረጠው ስቴት የስራ አጥነትና ሌሎች ችግሮች እንደሚፈጠሩ በመግለጽ ይከራከራሉ፡፡ ታዲያ ምን አለ የኦሮሞ ወጣቶች እኛ ሳንጠየቅ ይህን ያህል መሬት ለምን ይወሰድብናል? ቢሉ ምን ችግር አለው፡፡ አሜሪካ ዋና ከተማው ዋሽንግተን ዲሲ ነው፡፡ ዋሽንግተን የቨርጂኒያና የሜሪላንድን መሬት ዝም ብሎ ይከልላል? የማይታሰብና የማይደረግ ነገር ነው፡፡ ለማንም ሳይናገሩ ልዩ ዞኖችን እንደወሰዱት አይደለም፡፡ ይህ እኮ ሰውን መናቅ ነው፡፡ ከህዝቡ ጋር ተማክረዋል? መንግስት የህዝብ ወኪል ከሆነ ህዝብን መናቅ አይችልም፡፡ በሰለጠነ መንገድ ቢደረግ ኖሮ ማን ይቃወም ነበር?
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በቅርቡ ‹‹ሰማያዊ ፓርቲ አይገባኝም!›› ማለትዎትን አንብቤያለሁ፡፡ ሰማያዊ አይገባኝም ሲሉ ምን ማለትዎት ነው?
አቶ ቡልቻ፡- አንድነትን አውቀዋለሁ፡፡ መኢአድን አውቀዋለሁ፡፡ ሰማያዊን ግን አላውቀው ማለቴ ነው፡፡ ይህ ግልጽ ነው አላውቃቸውም ማለት ነው፡፡ እነሱም አላማቸውን ለማሳወቅ ፓምፕሌት አይበትኑም፡፡ እኔ ለምሳሌ ኦፌኮ በነበርኩበት ጊዜ ስለ አላማችን በርካታ ፓምፕሌቶችን እያሳተምኩ እበትን ነበር፡፡ ህዝብ አላማችን እንዲያውቅ እናደርግ ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ይህንን ሲያደርግ አላየሁም፡፡ እና ሰማያዊ ከአንድነት ምን ያህል ልዩነት ኖሮት ነው ሰላማዊ ሰልፍ የተፈቀደለትና አንድነት ሰላማዊ ሰልፍ የተከለከለው? አይገባንም፡፡ እውነቴን ነው ፖለቲካም እውነት ሊሆን ይችላል አንዳንዴ፡፡ ይህን አላውቅም የምለው ከልቤ ነው፡፡ አንድነት ከኦሮሞ የሚለይበትን አንዳንድ ምክንያቶች አውቃለሁ፡፡ ይህ ከቅን ልቦና የማደርገው ንግግር ነው፡፡ ቢፈልጉ ፓምፕሌት ይላኩልኝ አንብቤ እረዳዋለሁ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እርስዎስ በግልዎ ለማወቅ ጥረዋል?
አቶ ቡልቻ፡- አዎ! ጠየኩ! ቢሮ ውስጥ እባካችሁ የሰማያዊ ፓርቲ ፓምፕሌት፣ መግለጫ ካላችሁ ብዬ ጠይቄያለሁ፡፡ አሁንም እጠይቃለሁ፡፡ ለምሳሌ ከአንድነት ልዩነታቸው ምንድን ነው? አንድነት አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግራይ ሳይሆን ኢትዮጵያ መባል እንዳለበት እንደሚፈልጉ አውቃለሁ፡፡ የሰማያዊ ምን እንደሆነ አላውቅም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ሰማያዊ አቋሞቹን፣ መግለጫዎቹንና ሌሎቹንም በዚህ ጋዜጣ ያሳውቃል፡፡ ለምሳሌ ነገረ ኢትዮጵያን አንብበው ያውቃሉ?
አቶ ቡልቻ፡- እስካሁን አላየሁም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ለ2007 ሀገራዊ ምርጫ እየተቃረብን ነውና ከምርጫው ምን ይጠብቃሉ?
አቶ ቡልቻ፡- በአሁኑ ጊዜ የህዝቡን የኢኮኖሚ ችግር፣ የኑሮ ውድነት፣ የስራ አጥነት፣ በተለይም የምግብ ዋጋ መናር አለ፡፡ ይህን ሁሉ ህዝቡ ያውቃል፡፡ ታዲያ ህዝቡ ይህን እያወቀ ኢህአዴግን እንመርጣለን ይላል? እንግዲህ እያንዳንዱ ሰው መፍረድ አለበት፡፡ ይህ ሁሉ ችግር እያለ በማን አገር ነው አንድ ፓርቲ 20ና 30 አመት ስልጣን ላይ የሚቆየው? ቻይና ብቻ ነው አይደለም?! እንደ ቻይና ኮሚኒስት እንሁን ብሎ የኢትዮጵያ ፓርላማ ፈቅዷል? ያለ ፓርላማ ፈቃድ የኢትዮጵያ መንግስት እንደፈለገ የሚንቀሳቀስ፣ የፈለገውን ገንዘብ የሚያወጣ፣ የፈለገውን የሚገዛ፣ የፈለገውን የሚሸጥ፣ ዴሞክራሲ እንደሌለ አድረጎ ነው የሚያስተዳድረው፡፡ እንደ ፖለቲከኛ ሳይሆን እንደ ዜጋ ሳየው ተቃዋሚዎች በሚቀጥለው ምርጫ ትልቅ እድል አላቸው፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እርስዎ የሚገልጹት ብሶት መኖሩን ነው፡፡ ግን ተቃዋሚዎች የሚሉትን እድል ለመጠቀም የቤት ስራቸውን እየሰሩ ነው ብለው ያምናሉ?
አቶ ቡልቻ፡- ተቃዋሚዎች የማይፈታ ችግር አለባቸው፡፡ አሁን በቀደም በጋዜጣ ላይ ሳነብ ኢህአዴግ በደግነቱ ለተቃዋሚዎች ገንዘብ ሰጠ የሚል አይቼ በጣም ተደነኩ፡፡ ጋዜጣው ላይ ቃል በቃል ‹‹ለግሷል!›› ይላል፡፡ ይህ እኮ ድንቁርና ወይንም ክፋት ነው፡፡ በየትኛውም ሀገር ምርጫ ሲደርስ መንግስት ለተቃዋሚዎች ገንዘብ መስጠት ግዴታው ነው፡፡ ዋናው የመንግስት ስራ እኮ ነው፡፡ በጀት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ካለ በጀት ምንም ነገር አይሰሩም፡፡ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች አንድ ቦታ ላይ ለመድረስ የኢትዮጵያ በጀት እንዲደርሳቸው ያስፈልጋል፡፡ ይህ ደግነት አይደለም፡፡ የማንም ሀገር ተቃዋሚ በመንግስት በጀት ይንቀሳቀሳል፡፡ ተቃዋሚ አስተያየቱን በግልጽ በጋዜጣ፣ በቴሊቪዥንና በመሳሰሉት ካልገለጸ ማን ይመርጠዋል? እሱ እኮ ነው ኢትዮጵያ ውስጥ የተዘጋው በር፡፡ በሩ ከተዘጋ ተቃዋሚዎች እንዴት ይንቀሳቀሳሉ? በሬድዮና ቴሌቪዥን አትናገሩ ከተባለ፣ ሰላማዊ ሰልፍን ለህዝብ በቴሌቪዥን እንዳይታይ ከተደረገ ተቃዋሚዎች እንዴት ይንቀሳቀሳሉ? እንደዛም ሆኖ ግን ተቃዋሚዎች አሁንም ትልቅ እድል አላቸው ባይ ነኝ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በመጨረሻ መናገር እፈልጋለሁ የሚሉት መልዕክት ካለ?
አቶ ቡልቻ፡- እንዴት የኢትዮጵያ ህዝብ ዝም ብሎ አንድ ጥያቄ ሳይጠይቅ ይኖራል? ተቃዋሚዎችን በራዲዮና በቴሌቪዥን ያሰሙን ብሎ በሰልፍ አይጠይቅም? እንደዚሁም ደግሞ መንግስት መረጃ አልሰጥም እያለ ሲያስቸግር ህዝቡ አይጠይቅም? የመንግስትን ንብረት አጠቃለሁ፣ የሚገዙበት፣ የሚዙት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ብቻ ናቸው፡፡ የመንግስት ኩባንያዎች ሁሉ በኢህአዴግ ስር ነው የሚተዳደሩት፡፡ ድሮ በአጼ ኃይለስላሴ ጊዜ እንደዚህ ነበር፡፡ ነገር ግን በእርሳቸው ጊዜ እንደዛ የሆነው የግል ባለሀብት ስለጠፋ ነው፡፡ ዛሬ የግል ባለሀብት እንደ ልብ ነው፡፡ ለምንድን ነው የኢትዮጵያ መንግስት ይህን ሁሉ ንብረት የሚቆጣጠረው? የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ቴሌ፣ አየር መንገድን ሁሉ ለምንድን ነው በስሩ ያደረገው? እኛ ኮሚኒስት ነን እንዴ? ፓርላማ ኢትዮጵያ ኮሚኒስት ነች ብሏል፡፡ ይህ የኢህአዴግ የራሱና የውስጥ አሰራር ነው፡፡ ይህን ለህዝብ መናገር እፈልጋለሁ፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ከአዲስ አበባ

No comments: