Wednesday, July 9, 2014

አንበሳውን በጅቦች ተከቦ አየሁት

July9/2014
ፋሲል የኔአለም
ኢቲቪ የአንዳርጋቸው ንግግር ነው ብሎ ያቀረበው ፊልም አስቂኝ ነው። እንደነ ቢቢሲ በኮርፖሬሽን ደረጃ ለመዋቀር በቃሁ የሚለው ድርጅት በሴኩርቲ ( በድብቅ )ካሜራ የተቀረጸ የደበዘዘና የተቆራረጠ ፊልም ሲያቀርብ ማፈር ነበረበት።
አንዳርጋቸው ከተያዘ 2 ሳምንታት አለፉ። ዛሬ በድብቅ ካሜራ ተቀርጾ የተላለፈው ፊልም በእለቱ ኢትዮጰያ ሲገባ የተቀረጸ ነው – አለማቀፍ ግፊት ቢበዛብን እናሳየዋለን ብለው ቀርጸው ያስቀመጡት ነው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ግን አንዳርጋቸው እያንዳንዷን ቀን በድብደባ እያሳለፈ ነው። ኢቲቪ ልብ ካለው አንዳርጋቸውን ላይቭ ያሳየን።
አንበሳው ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ የሚውል አንድም ነገር አልሰጣቸውም። “እኔ ስራየን ጨርሼ ደክሞኛል፣ እረፍት እፈለግ ነበር” ነው ያለው፤ ይህንን ደግሞ ዶ/ር ብርሃኑ ና ንቅናቄው አስቀድመው ተናግረውታል- አንዳርጋቸው ስራውን በጊዜ አጠናቆና ሃላፊነቱን ለወጣት አመራሮች ሰጥቶ እሱ መጠነኛ የዲፕሎማሲ ስራ እየሰራ ነበር።
ህወሃቶች በደንፎ “የትግራይን ህዝብ ትጠላለህ?” ብለው ጠየቁት። “ለማንም ህዝብ ጥላቻ የለኝም” ብሎ መለሰላቸው። አንዳርጋቸው የትግራይን ህዝብ ከጉጅሌው እንለየው የሚል ጽኑ አቋም ነበረው፣ያንን ነው የደገመው።
የታዩትን ፎቶግራፎች ድሮም አውቃቸዋለሁ፤ ከላፕቶፑ የተወሰዱ ናቸው። በእዚህ እድሜው የአውሮፓ ህይወቱን ትቶ በዛ አይነት ህይወት ለመኖር መፍቀዱ የሚደነቅ ነው። የእኔንም ኮምፒዩተር በቫየረስ በከሉት እንጅ እነዚህና ሌሎች ፎቶዎችም ነበሩኝ።
ፈገግታና ደግነት ደግሞ ባህሪው ነው። ጠላቶቹን ሳይቀር በፈገግታው ይገላቸዋል።
ከሁለት ሳምንት ድብደባ በሁዋላ ለፕሮፓጋንዳ የሚሆን ነገር አለማግኘታቸው ሃረር ውስጥ በጅቦች ተከቦ አልበላም ብሎ ሲታገል የነበረውን አንበሳ አስታወሰኝ።
ኮራሁብህ ወንድሜ አንዲ።

No comments: