Sunday, July 27, 2014

ሰማያዊ ፓርቲ ምሁራን ተሳትፈውበታል ያለውን የቃል ኪዳን ሰነድ ይፋ አደረገ

July26/2014
ሰማያዊ ፓርቲ ምሁራን ተሳትፈውበታል ያለውን የቃል ኪዳን ሰነድ ይፋ አደረገ
-ፓርቲዎች በድርጅታዊ ፕሮግራሞቻቸው ውስጥ እንዲያካትቱት ጠይቋል

ሰማያዊ ፓርቲ በአገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ በርካታ ምሁራን ተወያይተውበት ብዙ ጥናትና ምርምር አድርገውበታል ያለውንና ‹‹የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ ለዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ›› በሚል መጠሪያ ያዘጋጀውን ሐምሌ 18 ቀን 2006 ዓ.ም. ይፋ አደረገ፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ይፋ ያደረገው የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ ዜጎች በጋራ አንድ ሆነው ሊስማሙባቸው የሚችሉ፣ አጠቃላይ በአገራቸው ሁኔታ ላይ የሚግባቡባቸው ጉዳዮችን የያዘ የጋራ ሰነድ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ከፕሮግራም፣ ከፖለቲካ ሐሳብ፣ ከአስተሳሰብና ለወቅታዊ ችግሮች መፍትሔ ከመስጠት ልዩነት ባሻገር፣ ኢትዮጵያዊያን እንደ አገር የሚግባቡበት አንድ የጋራ ሰነድ አስፈላጊ መሆኑን ፓርቲው ገልጿል፡፡ ይህም ሰነድ ፓርቲው ብቃት ባላቸው ምሁራን ተጠንቶና ውይይት ተደርጎበት፣ ሕዝብ ውይይት አድርጎበት አንድ የሚሆንበትና ‹ሕገ መሠረት› (የሕገ መንግሥት ማርቀቂያ መነሻ መሠረት) ሲል የጠራው ሰነድ መሆኑን የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር) ገልጸዋል፡፡

እንደ አቶ ይልቃል ገለጻ፣ ሰነዱ ውይይት ተደርጎበትና የኅብረተሰቡን ይሁንታ ካገኘ፣ ወደፊት ለሚረቀቀው ሕገ መንግሥት ወይም በሰማያዊ ፓርቲ አጠራር ‹ርዕሰ ሕግ›፣ በሰነዱ የቀረቡት ምሰሶ (ፒላር) የሆኑ ነገሮች ሆነው እንዲካተቱ ይደረጋል፡፡

የዜጎች ቃል ኪዳን ሰነድ (ሕገ መሠረት) በሚል ፓርቲው ይፋ ያደረገው ሰነድ አዘጋጅ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ እምልአሉ አሰፋ እንደገለጹት፣ ሕገ መንግሥት የሚለውን ‹‹ርዕሰ ሕግ›› ቢባል የተሻለ ትርጓሜ ሊኖረው ይገባል የሚል እምነት ፓርቲው ስላለው ርዕሰ ሕግ ብሎታል፡፡ ርዕሰ ሕጉን የሚያቋቁሙበት መሠረታዊ ምሰሶዎች (ፒላርስ) ደግሞ ሕገ መሠረት መባል እንዳለባቸው የሰማያዊ ፓርቲ እምነት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ ርዕሰ መንግሥትን (ሕገ መንግሥትን) በባለቤትነት የሚያቅፈው ዘላቂ ሰላምን፣ የሕግ የበላይነትንና ፍትሕን አራማጅ ሆኖ ሲያገኘው መሆኑን የገለጹት ምክትል ሰብሳቢው፣ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ አዲሱ ርዕሰ ሕግ የሚረቀቅ ከሆነ ካለፉት ዘመናት ከተደረጉት ጥረቶችና ልምዶች የተገኙ ትምህርቶችን ያካተተና በሕገ መሠረቶች ላይ የተመሠረተ መሆን እንዳለበት፣ የቃል ኪዳን ሰነዱ እምነትም መሆኑን አቶ እምልአሉ ገልጸዋል፡፡

ፓርቲው ይፋ ያደገው የዜጎች ቃል ኪዳን ሰነድ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና ግዛት ማስከበር፣ የግለሰብ መብቶች ቀደምትነት፣ ለህልውና መሠረታዊ ፍላጎቶችን የማግኘት ዋስትና፣ በአገሪቱ ብሔራዊ ቋንቋ(ዎች) እንዲኖሩ ማድረግ፣ የመሬት ባለቤትነት መብትና ዋስትና፣ ያልተማከለ መንግሥታዊ ሥርዓት፣ ሁሉን ወካይ የፍትሕ፣ የወታደርና የሲቪል አገልግሎቶች፣ ነፃና ፍትሐዊ የገበያ ሥርዓት፣ ነፃና ተጠያቂ የሲቪክ ማኅበራትና የፖለቲካ ፓርቲ ተቋማት የሚባሉት መሠረታዊ መመርያዎች ላይ ኅብረተሰቡ እንደሚወያይባቸው አስረድተዋል፡፡

መሠረታዊና ለርዕሰ ሕጉ ምሰሶ (ፒላርስ) ናቸው ባሏቸው ከላይ በተዘረዘሩት ዘጠኝ ነጥቦች ላይ ሕዝቡን በማወያየት አንድ ነጥብ ላይ እንደሚደረስ የሰማያዊ ፓርቲ እምነት መሆኑን የገለጹት አቶ እምልአሉ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብን ያሳተፈና ዘመን ተሻጋሪ ርዕሰ ሕግ ይኖራል የሚል እምነት እንዳላቸው አስረድተዋል፡፡

ርዕሰ መንግሥት ማለትም ሆነ ሕገ መንግሥት የተለያየ ስም ከመስጠት ያለፈ ፋይዳ ስለሌለው ይህንን ማድረጉ ለምን እንዳስፈለገ፣ ብሔርን ማዕከል ያደረገ የፌዴራል ሥርዓት አወቃቀሩ የብሔር ብሔረሰቦችን እኩልነት አረጋግጦ ሳለ፣ ብሔራዊ ቋንቋ እንዲኖረው በማለት ወደ አንድ መጠቅለሉ የዜጎችን መብት ማጣበብ ከመሆኑም በላይ አንዱን የበላይ አንዱን የበታች ማድረግ ስለመሆኑና  የግለሰቦችን መብት አክብሮ የቡድን መብትን መደፍጠጥ በሰነዱ ላይ ስለተገለጸበት ሁኔታ ማብራሪያ እንዲሰጥበት ለአቶ እምልአሉ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል፡፡

አቶ እምልአሉ እንደገለጹት፣ የቃል ኪዳን ሰነዱ ሕገ መንግሥት ማለት አይደለም፡፡ ሕገ መንግሥት ወይም እንደ ሰማያዊ ፓርቲ እምነት ርዕሰ መንግሥት ለማርቀቅ እንደ ምሰሶ ሆነው የሚያገለግሉ ዋና ዋና የሁሉም ኅብረተሰቦች መሠረታዊ መመርያዎችንና የመወያያ ርዕሶችን የያዘ ሰነድ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ስሙን ርዕሰ መንግሥት ማለት የተፈለገው የተሻለ ትርጉም ስለሚሰጥ መሆኑንም አክለዋል፡፡

ቋንቋን በሚመለከት ማብራሪያ የሰጡት የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበርና የቃል ኪዳን ሰነዱ አዘጋጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ስለሺ ፈይሳ ሲሆኑ፣ ሰማያዊ ፓርቲ የሁሉንም ብሔረሰቦች ቋንቋ እንደሚያከብር አስረድተው፣ ኢትዮጵያ እንደ አገር ግን አንድ፣ ሁለትና ሦስት ብሔራዊ ቋንቋዎች እንደሚያስፈልጓት ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከሌሎች አገሮች የተለየችና ብቸኛዋ ብሔራዊ ቋንቋ የሌላት አገር በመሆኗ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ እምነት ብሔራዊ ቋንቋ ሊኖራት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ የክልል ወይም የጎሳ ቋንቋ መኖርንም ፓርቲያቸው እንደሚያከብር ገልጸው፣ ሁሉም ሊግባባበት በሚችለው ቋንቋ አይጠቀም የሚል አቋም እንደሌላቸው አስረድተዋል፡፡

የቃል ኪዳን ሰነዱ ሁሉንም የሚያግባባ የጋራ ነጥቦችን የያዘ ሰነድ መሆኑንና ብሔርን መሠረት ያደረገ መሆኑን በማከል፣ ስለብሔር ትርጉም የተናገሩት አቶ እምልአሉ፣ ‹‹ብሔር ማለት ትርጉሙ አገር ወይም ቦታ ማለት ነው፡፡ በ1960ዎቹ የሶሻሊስት ሥርዓት ሲመጣ፣ ስታሊን ‹ኔሽንስ ራይት› ብሎ ስለተነሳ ምሁራን ተሰባስቡና ሲተረጉሙ ብሔር አሉት፡፡ የቡሄ ለት ያበደ ዘላለም ‹ሆ› እንዳለ ይኖራል እንዲሉ እስካሁን ‹ኔሽንስ› የሚለውን ብሔር እያልን እንተረጉማለን፤›› ብለው ትርጉሙ ሌላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ትርጉሙ ሊስተካከል እንደሚገባና አንድነትን የሚያጠናክር፣ የባህል፣ የእምነትና ሌሎች ግንኙነቶችን የሚያጠናክር ነገር መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ የቃል ኪዳን ሰነዱ የያዛቸውን የርዕሰ ሕግ ምሰሶዎች ሕዝቡ ተወያይቶበት ወደ አንድነት መምጣት ሲቻል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

የመሬት ባለቤትነትን በሚመለከት በቃል ኪዳን ሰነዱ ላይ ስለተጠቀሰው ጉዳይ፣ መሬት የሀብት ሁሉ መሠረት ወይም ምንጭ በመሆኑ እንዴት የባለቤትነትና የመብት ዋስትና ሊከበር ይገባል ሊባል እንደቻለ ተጠይቀው፣ የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ‹‹መሬት የሕዝብና የመንግሥት ነው ይላል፤›› ካሉ በኋላ፣ ‹‹መንግሥት መሠረቱ ሕዝብ ነው፡፡ ለምን ሕዝብን አያምንም? የራሱን ነጥሎ በመያዝ የሕዝቡን ለምን ለራሱ ለሕዝቡ አይተውም?›› በማለት ጥያቄ አንስተዋል፡፡ መንግሥት ከራሱ ሕዝብ የበለጠ የውጭ ኢንቨስተሮችን እንደሚያምን የገለጹት አቶ እምልአሉ፣ ኢንቨስተር ግን አምርቶ ዶላሩን ይዞ ሲወጣ እንጂ ሌላ የታየ ነገር እንደሌለ ጠቁመዋል፡፡ የሙስና ዋናው መንገድ መሬት በመንግሥት መያዙ መሆኑንም አክለው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ነዳጅ ቢወጣ መሬት የኢኮኖሚ መሠረት መሆኑ እንደሚያከትምና ጥያቄ መሆኑ እንደሚያበቃ ያልተረዱ፣ ዜጋን የመሬት ባለቤት እንዳይሆን እንዳደረጉት አብራርተዋል፡፡

በሰማያዊ ፓርቲ የተዘጋጀው የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ የተለፋበትና እነ ዶ/ር ብርሃኑ አበጋዝ፣ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ፣ ፕሮፌሰር አክሎግ ቢራራና ሌሎች ምሁራን የተሳተፉበት መሆኑን የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ይልቃል አስረድተዋል፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችና የሲቪክ ማኅበራት የቃል ኪዳን ሰነዱን አጥንተውና ተወያይተውበት በፕሮግራሞቻቸው ውስጥ እንዲያካትቱት ሰማያዊ ፓርቲ ጥሪ አቅርቧል፡፡ 

No comments: