Tuesday, April 15, 2014

“አዲስ አበባ የኦሮምያ ናት” የሚለውን ቀልድ ተውትና ለእውነተኛ የነጻነት ትግል ተነሱ! (ይድረስ ለጥቂት የኦሮሞ ሊህቃን) – ከፋሲል የኔዓለም

April 15/2014

ከፋሲል የኔዓለም (ጋዜጠኛ)

የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ትግል በሁለት አቅጠጫዎች የሚካሄድ ነው ። አንደኛው ከህወሃትና አጋሮቹ ጋር የሚካሄደው የሽቅብ (vertical) ትግል ሲሆን ሌላው ደግሞ ተቃዋሚዎች እርስ በርስ የሚያካሂዱት የአግድሞሽ (horizontal) ትግል ነው። የአግድሞሹ ትግል ሲዳከም የሽቅብ ትግል ይጠነክራል፣ የአግድሞሹ ትግል ሲጠናከር ደግሞ የሽቅብ ትግል ይዳከማል። ለ23 ዓመታት የተካሄደው የነጻነት ትግል ፍሬ ሊያፈራ ያልቻለው በከፊል የአግድሞሹ ትግል ሙሉ በሙሉ ሊጠፋ ወይም ሊዳፈን ባለመቻሉ ነው። ለወደፊቱም ቢሆን የአግድሞሹ ትግል እየተዳከመ ካልሄደ ሽቅብ የሚካሄደው ትግል ሊጠናከር አይችልም። ህወሃትና አጋሮቹ ከመቼውም ጊዜ በላይ ተዳክመው የሚገኙበት ጊዜ ላይ እንገኛለን። ይህን የተዳከመ ሃይል በካልቾ መትቶ ለማባረር የአግድሞሹን ትግል በማዳከም የሽቅብ ትግሉን ማጠናከር ያስፈልጋል፤ የአግድሞሹ ትግል ሊዳከም የሚችለው ደግሞ ዋነኞቹ ተቃዋሚዎች ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ስምምነት ፈርመው የያዙትን ጥይት ወደ    ሽቅብ ለመተኮስ መስማማት ሲችሉ ብቻ ነው።                                   
ወደ ሽቅብ የሚደረገውን ትግል ከሚያዳክሙ ሃይሎች መካከል በተቃውሞ ጎራ ተሰልፈናል የሚሉ የተወሰኑ የኦሮሞ “ሊህቃን” በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። እነዚህ ሊህቃን ምን እንደሚፈልጉ አይታወቅም። አቋማቸው በየጊዜው እንደ እስስት የሚለዋወጥ በመሆኑም እንዲህ ናቸው ብሎ አፍን ሞልቶ ለመናገር አይቻልም። እነሱን አምኖ አብሮ ለመታገልም በጣም አስቸጋሪ ነው፤ መቼና የት ቦታ ላይ እንደሚለወጡ አይታወቅም፤ ከእነሱ ጋር አብረው ለመስራት የሞከሩ ድርጅቶች ሁሉ እስከዛሬ አልተሳካላቸውም። እነዚህ ጥቂት ሊህቃን የኦሮሞን ህዝብ ፍላጎት የሚያውቁ አይመስለኝም። መሽቶ በነጋ ቁጥር አቋማቸውን በብርሃን ፍጥነት ሲለዋዉጡ የምናየውም ለዚህ ይመስለኛል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እነዚህ ጥቂት ሊህቃን የመገንጠል አጀንዳቸውን በመተው ለነጻይቷ አገር መወለድ እንደሚሰሩ ሲነግሩን ተስፋ አድርገን ነበር፤ ነገር ግን ሰሞኑን የሚጽፉትና የሚናገሩት አሁንም ካረጁበት የመገንጠል አላማ ፈቅ አለማለታቸውን የሚያሳይ ነው። በተለይ የአዲስ አበባ ከተማን አዲስ ካርታ ለመቃወም የሚያነሱት መከራከሪያ ልብን ዝቅ የሚያደርግና የሰዎቹን እውነተኛ ፍላጎት ገሃድ የሚያወጣ ነው።

ጥቂት የኦሮሞ ሊህቃን የአዲስ አበባን መስፋፋት የሚቃወሙት “መሬቱ የኦሮሞ ነው” ከሚል ጠባብ ስሜት ተነስተው ነው። በአንድ በኩል “አዲስ አበባ የኦሮምያ ናት” ይሉንና በሌላ በኩል ደግሞ “የኦሮምያ ልዩ ዞኖች በአዲስ አበባ ስር መሆን የለባቸውም” ይላሉ። አዲስ አበባ የኦሮሞ መሬት ከሆነ ፣ ልዩ ዞኖቹ በአዲስ አበባ ስር ሆኑ አልሆኑ ምን ልዩነት ያመጣል? ክርክራቸው ስሜት እንዲሰጥ ከፈለጉ “አዲስ አበባ የኦሮሞ አይደለም” ብለው መነሳት አለባቸው። ሳሎን ውስጥ ያለውን ሶፋህን አንዱ ወስዶ መኝታ ቤትህ ውስጥ ቢያደርገው ሶፋ ተሰረቀ ብለህ ልትከስ አትችልም ። መክሰስ የምትችለው ሶፋህን ሌላ ሰው ቤት ካየኸውብቻ ነው። የኦሮምያ መሬት ወደ አዲስ አበባ ዞረ ብሎ ለማልቀስ፣ አዲስ አበባ የኦሮሞ አይደለችም ብሎ ማመንን ይጠይቃል። ይህን የነሳሁት ሊህቃኑ የሚያቀርቡትን የተምታታ ሃሳብ ለማሳየት እንጅ፣ አዲስ አበባም ሆነ ኦሮምያ “የኦሮሞ ብቻ ነው” የሚለውን አስተሳሰብ ለመደገፍ አይደለም።

“ኦሮምያን የኦሮሞ፣ አማራን የአማራ፣ ትግራይን የትግሬ…” ንብረት ብቻ እንደሆኑ አድርጎ ማየቱ የኢትዮጵያን አንድነት የሚያዳክም፣ የአገርን ምንነት ትርጉም የሚያዛባና አደገኛ ነው። ለመሆኑ ማን ነው አዲስ አበባን ለኦሮሞ ብቻ የሰጠው? እንኳንስ አዲስ አበባን ማን ነው ጅማን፣ ቦረናን፣ አዳማን፣ አርሲን ወዘተ የኦሮሞ ብቻ ያደረጋቸው? ማን ነው ባህርዳር ፣ ጎንደር፣ ደሴ ወዘተ የአማራ ብቻ ነው ያለው ? ጋምቤላን ለጋምቤላዎች፣ አፋርን ለአፋሮች ፣ ትግራይን ለትግሬዎች ብቻ የሰጠው ማን ነው? በየትኛው ህግ፣ በየትኛውም አንቀጽ ነው ክልሎች መሬት ተከፋፍለው “ያ ያንተ ይሄ የኔ ነው” የተባባሉት? የይስሙላው ህገመንግስት ( ህገ-አገዛዝ) እንኳ ክልሎች በስራቸው ያለውን መሬት ያስተዳድራሉ አለ እንጅ መሬቱ የእነሱ ብቻ ነው አላላም። የአስተዳደር ባለቤትነት ሰጣቸው እንጅ የውርስ ባለቤትነት አልሰጣቸውም። ክልሎች እስካልተገነጠሉና በአንድ አገር ስር እስካሉ ድረስ “ይሄ የእኔ ያ ያንተ መሬት ነው” ሊሉ አይችሉም፣ የአንዱ መሬት የሌላው፣ የሌላው መሬት የአንዱ ነውና።

የኦሮሞ ተወላጅ የመከላከያ ሰራዊት አባል ትግራይ ሄዶ ሲሞት “ትግራይም የእኔ ናት” ብሎ እንጅ ትግራይ የትግሬዎች ናት ብሎ ስላመነ አይደለም። የአማራ ተወላጅ ኦሮምያ ድንበር ሄዶ የሚሞተውም በተመሳሳይ እምነት ነው። ዛሬ ህወሃት የአገራችንን አንድነት ቢያዳክምም እልፍ አእላፍ ዜጎች ለዚህች አገር መስዋትነት የከፈሉት “ሁሉም የኔ፣ እኔም የሁሉም” በሚል እምነት ነው። እያንዳንዷ ቅንጣት የኦሮምያ አፈር፣ ልክ እንደ ኦሮሞው ሁሉ፣ አማራውንም ታገባዋለች፣ እያንዳንዷ የአማራ ቅንጣት አፈር ፣ ልክ እንደ አማራው ሁሉ፣ ኦሮሞውንም ትመለከተዋለች። በአንድ ጎጆ ስር እስከኖርን ድረስ “ይሄ የእኔ ያ ያንተ” የሚባል ነገር የለም። አዲስ አበባ የሁላችንም ናት፣ ኦሮምያም የሁላችንም ናት፣ ባህርዳርም የሁላችንም ናት፣ መቀሌም የሁላችንም ናት። ኢትዮጵያ የሁላችንም ናት።

ኦሮምያ የኦሮምያ፣ ትግራይ የትግራይ የሚለው አስተሳሰብም የደባልነት አስተሳሰብ ነው። ደባልነት ከትዳር የሚለየው በማንኛውም ጊዜ የሚፈርስ፣ መተሳሰብ የሌለው፣ ለጊዚያዊ ጥቅም ተብሎ የሚገባበት በመሆኑ ነው። ኢትዮጵያን እንደ ትዳር ትተን እንደ ደባል ህይወት የምንመስላት ከሆነ አደጋ አለው። ጥቂት የኦሮሞ ሊህቃን አዲስ አበባንና ኦሮምያን የእነሱ ብቻ አድርገው ማየት በማቆም፣ የአዲስ አበባን መስፋፋት የሚቃወሙበትን ሌሎች ወንዝ የሚያሻግሩ ምክንያቶችን ማቅረብ አለባቸው። ሊህቃኑ ከኦሮምያና ከአዲስ አበባ ውጭ ያሉ ቦታዎችንም እንደራሳቸው አድርገው መውሰድ መጀመር አለባቸው። እንዲያ ከሆነ ብቻ ነው ስለጋራ ችግር መነጋገር የሚቻለው።

የአዲስ አበባን መስፋፋት የምቃወመው በሁለት ምክንያቶች ነው። አንደኛ፣ አዲስ አበባ ወደ ላይ እንጅ ወደ ጎን መስፋት የለባትም ። አሁን ያለውን ህዝብ ህንጻዎችን ወደ ላይ በማሳደግ ማኖር ይቻላል። ለወደፊቱ ጥሩ የህዝብና ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መቅረጽና ማስተዳደር ግድ ይላል።
ሁለተኛው ምክንያቴ ደግሞ የአካባቢ ውድመት ስለሚያሳስበኝ ነው። በአዲስ አበባ የሚገነባው ነገር ሁሉ ዘላቂነት ያለው አይመስለኝም። እንበደራለን፣ እንገነባለን፣ እናፈርሳለን። እዳው ደግሞ በውርስ ለልጆቻችን ይተላለፋል። ከተማዋ አረንጓዴነት አይታይባትም፤ ኳስ ሜዳ፣ መናፈሻ ፓርክ ወዘት ቦታ አልተሰጣቸውም። ታሪካዊ ቦታዎች ይወድማሉ። ከተማዋ የቻይና የቴክኖሎጂ ቤተ-ሙከራ ( laboratory) እንጅ ህዝብና አስተዳደር ያለባት ከተማ አትመስልም። ከመንገድና ከሌሎች ግንባታዎች ጋር ተያይዞ የሚረጩት ኬሚካሎች እንኳ በጤና ላይ ስለሚኖራቸው ጉዳት በቂ ጥናት የሚካሄድባቸው አይመስለኝም። በቃ ሁሉም ነገር ለመታየትና ለፕሮፓጋንዳ ተብሎ ስለሚሰራ ያስጠላል። ደረቅ ህንጻዎችን ማየት የመረረው ሰው አረንጓዴ መስክና አዝመራ ማየት ቢፈልግ ወደ እነዚህ ቦታዎች መሄድ አለበት። ልዩ ዞኖቹ ህንጻ መስሪያ ቦታዎች ከሆኑ የአዲስ አበባ ህዝብ አይኑን የሚያሳርፍበት አረንጓዴ ቦታ አያገኝም። ተፈጥሮን በግዴለሽነት ማውደምም ፍትሃዊ አይደለም።

የኦሮምያ ልዩ ዞኖች በአዲስ አበባ ወይም በኦሮምያ ስር ስለሆኑ ገበሬው ከመፈናቀል አይድንም፣ ልዩነት ቢኖር ፈቃድ ሰጪው ወይ ኦሮምያ ወይ አዲስ አበባ መሆኑ ነው። በለገዳዲና በለገጣፎ አካባቢዎች አንዳንዶች በስማቸው እስከ 30 ቦታዎችን ይዘው ተገኝተዋል፣ የሚያስመዘግቡት የሰው ስም አጥተው በውሾቻቸው ስም ካርታ ያሰሩም አሉ። ይህን የሚያደርጉት ገንዘብ ያላቸው ናቸው። ገንዘብ ያላቸው እነማን ናቸው? ገብረዋህድ ሁሉንም ነገር ይነግረናል። ገብረዋህድ መንግስት እንደነገረን 16 የቤት ካርታዎች አሉት። ስንት ገብረ ዋህዶች እንደሚኖሩ አስቡት። ሰሞኑን አንዱ ወዳጄ በጋምቤላ ስለሚካሄደው የመሬት ዘረፋ ይነግረኝ ነበር። “ህንዶች ሲቀነሱ፣ መሬቱን ተቆጣጥረው የያዙት የህወሃት የቀድሞ መኮንኖች ናቸው” አለኝ። ያሳዝናል!

የኦሮሞንም ሆነ የሌሎችን አካባቢዎች ገበሬዎች ከመፈናቀል ለመታደግ የጎንዮሹን ትግል ለጊዜው ትቶ ከሌሎች ተቃዋሚዎች ጋር በማበር ይህን በሙስናና በጎጠኝነት ላይ የተመሰረተ ስርዓት ለማስወገድ መሰባሰብ ግድ ይላል ።

No comments: