Thursday, April 17, 2014

ይድረስ ለብዙሃኑ የሠራዊቱ አባል ወገናችን!! የግንቦት7 መልእክት

April 17/2014

የመከላከያ ሚኒስትር በተሰኘው የውሸት ሥልጣን ላይ የተቀመጠው አድርባይ ሲራጅ ፈርጌሳ ለይስሙላው ምክር ቤት ባቀረበው ሪፓርት፣ “የመከላከያ ሚኒስትር የብሔር ተዋጽዖ የተመጣጠነ” እንደሆነ ገለፀ። እንደ ሰውየው ሪፓርት ከሆነ የመከላከያ ሠራዊቱ 29.46 በመቶ አማራ፣ 25.05 በመቶው ከደቡብ ብሔሮች የተውጣጣ፣ 24.45 በመቶ ኦሮሞ፣ 17.47 በመቶው ትግራይ እና የተቀሩት ክልሎች ድርሻ 4.17 በመቶ ነው። መረጃው የተቀናበረው በክልል ቢሆንም የቀረበው ግን በዘር ነው። “ተመጣጠነ” የተባለውም የክልሎች ተዋጽዖ ሳይሆን የዘር ተዋጽዖ ነው። ሠራዊቱን እንዲህ በዘር ሸንሽንኖ የስታትስቲክስ ጨዋታ መጫወት አሳዛኝም አሳሳቢም ነገር ነው። የሆነ ሆኖ ይህ መረጃ፣ መረጃ ነው ተብሎ ለሕዝብ ቀርቧል።
ይህንን መረጃ የሰማ ማሰብ የሚችል አዕምሮ ያለው ሰው የሚጠይቀው የመጀመሪያ ጥያቄ “የሠራዊቱ ስብጥር በተገለፀበት ዓይነት የመኮንኖቹም ስብጥር ለምን አልተገለፀም?” የሚል ነው። ይህ ጥያቄ በአስተዋይ ሰው አዕምሮ ውስጥ በተነሳነበት ፍጥነት ምላሽ ያገኛል፤ ምክንያቱም ምላሹ እዚያው እቁጥሮቹ ውስጥ አለ። የመኮንኖቹ ስብጥር ያልተነገረበት ምክንያት አብዛኞቹ መኮንኖች በ17.47 በመቶው በመሆናቸው ነው። ወደዚህ መምደሚያ የሚደርሰው አሳቢው ስለፈለገው ሳይሆን የመረጃው አቀራረብ አመክኖ (ሎጂክ) ወደዚያ ስለሚገፋ ነው። በዚህም ምክንያት በሲራጅ ፈርጌሳ አንባቢነት የቀረበው የህወሓት ሪፓርት በገዛ ራሱ ላይ ነው የተኮሰውም።
እኛ እንደ ሲራጅ ፈርጌሳ የዘር ስታትስቲክስ ውስጥ አንገባም፤ መልዕክታችን ለተገፋውና እየተበደለ ላለው ለመላው የሠራዊቱ አባል ነው።
ይድረስ ሹመትና ኃላፊነት ተነፈገህ፤ የጥቂቶቹን ሀብትና ዝና ጠባቂ እንድትሆን ለተፈረደብህ ወገናችን!!! እስከመቼ ለህወሓትና ጥቂት አጎብዳጅ መኮንኖች ባርነት ትገዛለህ? ይህ ውርደትህ የሚያበቃው መቼ ነው? የታጠቀው መሣሪያ የአገርህና የራስህ ክብር ማስጠበቂያ፤ ነፃነትህን መጎናፀፊያ የምታደርገው መቼ ነው? ለመሆኑ ለመኮንንነት የሚያበቃ ጭንቅላት፣ ልምድ ወይም እውቀት ከፓርቲ አባልነት ነው የሚገኘው? ህወሓቶችና አጋሮቻቸው በሠራዊቱ ያሉትን ቁልፍ ኃላፊነቶችን ሁሉ ጠቅልለው ይዘው “ጀሌዎቻችን እንዲሆኑ ፈቅደንላቸዋል” የሚል ሪፓርት የሚያቀርቡት ምንኛ ቢንቁን ነው? ይህንን ውርደት ኢትዮጵያዊው ወኔህ እንዴት ይቀበለዋል?
ኢትዮጵያዊው ወታደር ከሌላው ኢትዮጵያዊ በባሰ በአምባገነንና ዘረኛ አለቆቹ እየተዋረደ እንደሆነ በገሃድ የሚታይ ጉዳይ ነው። የህወሓት አባላት ቁልፍ የስልጣን ቦታዎችን ይዘው ጦር ሠራዊቱን እንደ ፓርቲ መዋቅር ሲመሩት ማየት የሠራዊቱን አባላት ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ኢትዮጵያዊ የሚያንገበግብ ጉዳይ ነው። ሠራዊቱ አገርና ሕዝብን ሊጠብቅበት ይገባ የነገረው መሣሪያ በንጹሃን ዜጎች ላይ እንዲያነሳ፤ ሰላማዊ ሰዎችን እንዲደበድብ፣ እንዲረግጥና እንዲገድል የሚያዙት እነዚህ የህወሓትና ጥቂት አጎብዳጅ አለቆቹ እንደሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያውቃል። ሆኖም የኢትዮጵያ ወታደር የታዘዘው ሁሉ የሚፈጽም ባርያ አይደለምና በእነዚህ ጥቂት ዘረኛ አለቆችህ ላይ እንዲነሳ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይጠይቃል።
ውድ የኢትዮጵያ ወታደር ሆይ!!! “ዘረኛነት በቃኝ” በል። ለነፃነት፤ ለእኩልነት፤ ለአገር ክብር በሚታገሉ ወገኖችህ ላይ ክንድህን አታንሳ። የጥቂት ዘረኞችን ሥልጣን በማራዘም ከሚመካብክ የኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ ጋር ዘላቂ ቂም ውስጥ አትግባ። በትእቢት “ሁልሽንም ረግጠን እንገዛለን” ብለው የሚፎክሩት አንተን ከወገንህ ጋር ደም በማቃባት ነውና “እምቢ!” በላቸው። ለዘረኞች ስልጣን ብለህ አትሙት! እንዲያውም ለገዛ ራስህ ክብር፣ ለቤተሰቦችህና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት ግንባር ቀደም አርበኛ ሁን።
ከላይ የተባለው ለፓሊስ አባላትም ይሠራል። በህወሓትና ህወሓት በየቦታው በፈጠራቸው ጀሌዎች የሚመራ በመሆኑ ከሕዝብ ፍላጎት በተፃፃሪ የቆመ ይምሰል እንጂ የኢትዮጵያ ፓሊስ የሕዝብ ወገን እንደሆነ በተለያዩ አጋጣሚዎች የታየ ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍትህ እጦት የሚሰቃየውን ያህል ብዙሃኑ ፓሊስ በፍትህ እጦት እየተሰቃየ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ የኑሮ ጫና እንዳዳከመው ሁሉ የኢትዮጵያ ፓሊስም ኑሮ ከብዶታል። እንደሌላው ሰው ሁሉ ፓሊስንም ዘረኝነት አስመርሮታል። ብዙሃኑ ፓሊስ አቅሙን በጥቂት አምባገነን አለቆቹ ላይ የሚፈትሽበት ጊዜ ደርሷል።
የስለላ ተቋማቱ ጉዳይ ለየት ይላል። “ደህንነት” ተብሎ በሚሞካሸው የጆሮጠቢዎች ስብስብ በሆነው መሥሪያቤት እና በኤክትሮኒክስ ብርበራ የተሠማሩ “ባለሙያ ጆሮ ጠቢዎች” ውስጥ ህወሓት በአለቃነትም በምንዝርነትም አብዛኛውን ቦታ ይዟል። ሆኖም እዚህም የሕዝብ ወገኖች እንዳሉ ይታወቃሉ። በእነዚህ ቦታዎች ያላችሁ የሕዝብ ወገኖች ሲቻል በገሃድ ሳይቻል በሚስጥር ተቋማቱን የማዳከም ሥራችዎችን መሥራት የህሊናና የዜግነት ግዴታችሁ ነው። ከእናንተ ብዙ፤ እጅግ ብዙ ይጠበቃል። የምታሾልኳት ትንሿ መረጃ የብዙዎችን ሕይወት ልትታደግ ትችላለች፡
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በህወሓት የጦር፣ የፓሊስና የስለላ መዋቅሮች ውስጥ የሕዝብ ወገኖች እንዳሉ ያውቃል። እነዚህ ወገኖቻችን እንደሌላው ሕዝብ ሁሉ – አንዳንዴም ከሌላው በባሰ ሁኔታ – በፍትህ እጦት፣ በኑሮ መክበድና በዘረኝነት እየተሰቃዩ መሆናቸው ያውቃል። እነዚህ ወገኖቻችን ጥለው እንዲወጡ፤ ይህ ካልተቻለም ከውስጥ ሆነው የወያኔን የጦር፣ የፓሊስና የስለላ መዋቅሮች እንዲያፈራርሱ ጥሪ ያደርጋል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

No comments: