Friday, August 2, 2013

ኬኒያዊው ጠበቃ ስለየሱስ የሞት ፍርድ ሔግ ክስ ከፈተ!

ጲላጦስን ሔሮድስን ጣልያንና የእስራኤል መንግሥታትን ከስሷል
 
dola-indidis
                   
የየሱስ ክርስቶስ ክስ፣ ፍርድና ሞት ተገቢው የሕግ አሠራር የተከተለ አይደለም፤ ጉዳዩም እንደገና መታየት አለበት በማለት ኬኒያዊው ጠበቃ ዶላ ኢንዲዲስ ሔግ ለሚገኘው ዓለምአቀፉ ፍርድቤት ክስ ማሰማቱን ጀሩሳሌም ፖስት ኬኒያ የሚታተመውን ናይሮቢያን ጋዜጣን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
 
የቀድሞ የኬኒያ ፍርድቤት አፈቀላጤ የነበረው ይኸው ጠበቃ በወቅቱ የሮም ቄሣር የነበረውን ጢባሪዮስ ቄሣር፣ ጲላጦስን፣ የአይሁድ መሪዎችን፣ ንጉሥ ሔሮድስን፣ የአሁኑን የጣልያንና የእስራኤል መንግሥታትን ከስሷል፡፡
 
“ማስረጃው በመጽሐፍቅዱስ ላይ ይገኛል፤ ይህንን ደግሞ ማንም ሊክድ አይችልም” የሚለው ጠበቃ የሱስ በወቅቱ ተገቢውን ፍርድ እንዳላገኘ ጉዳዩም በትክክል በፍርድ ሒደት ውስጥ እንዳላላፈ ጠቁሟል፡፡ ጉዳዩ ሁለት ሺህ ዓመታት ያስቆጠረ ቢሆንም አሁን ያሉት የጣሊያንና የእስራኤል መንግሥታት በዚያን ጊዜ (በስቅለት) የነበረውን የሮም ህግጋትን አሁንም በሕጋቸው ውስጥ በተግባር እየተረጎሙ ስለሆነ ተጠያቂ ናቸው ብሏል፡፡
 
ክሱን የማቀርበው የየሱስ ወዳጅ (ጓደኛ) በመሆን ነው ያለው ጠበቃ አስቀድሞ ለኬኒያ ከፍተኛ ፍርድቤት ተመሳሳይ ክስ አቅርቦ ውድቅ በመደረጉ ጉዳዩን ወደ ለዓለምአቀፉ ፍ/ቤት መውሰዱ ተጠቁሟል፡፡
 
በወቅቱ ተገቢው ምርመራና የፍርድ አሠራር እንዳልተፈጸመ የተናገረው ጠበቃ በቦታው የነበረ “ተፍተውበታል፣ በበትርና በጡጫና በጥፊ መትተውታል፣ አሠቃይተውታል በመጨረሻም ላይ ሞት እንደሚገባው ፈርደውበታል” የሚለው ጠበቃ ኢንዲዲስ የሱስ እንዲናገር እንኳን ዕድል እንዳልተሰጠው ተናግሯል፡፡
 
ስለ ጉዳዩ እንደሚያውቁ የተጠየቁ አንድ የዓለምአቀፉ ፍ/ቤት ኃላፊ ሲመልሱ “ፍርድቤቱ ይህንን ክስ የማየት ሥልጣን የለውም፤ ፍ/ቤቱ የሚመለከተው በመንግሥታት መካከል የሚከሰት ክርክርና ክስ ነው፤ ይህንን ክስ ለመመልከት በጽንሰሃሳብ ደረጃ እንኳን የማይቻል ነው” በማለት መልስ ሰጥተዋል፡፡
 
ጠበቃ ኢንዲዲስ ግን ተገቢና ትክክለኛ ክስ እንዳቀረበ በእርሱ የሕይወት ዘመንም ፍትህ ተፈጽሞ ለማየት እንደሚበቃ ያለውን ተስፋ ተናግሯል፡፡
 
በጌትሰማኒ የመጨረሻውን ጸሎት ኢየሱስ ካደረገ በኋላ የሮም ወታደሮችና የካህናት አለቆች መጥተው በያዙት ጊዜ በሁኔታው ህገወጥነት የተናደደው አንደኛው ደቀመዝሙር (ጴጥሮስ) በሰይፉ የአንዱን አገልጋይ ጆሮ ቆርጦ ነበር፡፡ የጴጥሮስን ድርጊት የተቃወመው የሱስ ሲመልስ አስፈላጊ ከሆነ “12 ሌጊዮን (ከ60ሺህ – 90ሺህ) መላዕክት” በቅጽበት በማዘዝ ራሱን መከላከል ይችል እንደነበር መናገሩን መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ይናገራል፡፡ (ማቲዎስ፡26፤53)

No comments: