Thursday, August 8, 2013

‹‹የስልጣን ጥመኝነት የወለደዉ የፀረሽብር አዋጅ›› የጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ ደብዳቤ ከቃሊቲ

August 8, 2013 at 1:12pm
 
የፀረሽብር አዋጁንና እየተተገበረ ያለበትን መንገድ ባሰብኩ ቁጥር  ወደአይምሮዬ የሚመላለሱ በርካታ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ከነዚህ መሀከል አዋጁ ለምን ሰብአዊ መብትን የሚጥሱ አንቀጾች ኖሩት/  ከሽብር ጋር ምንም አይነት ንክኪ የሌለን ንጹሀን ሰዎችስ በአዋጁ መሰረት እየተባለ ለምን ይፈረድብናል የሚሉት ይገኙበታል፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ አዋጁ የወጣበትን ምክንያት መመርመር ግድ ይላልና ይህንኑ አደረስኩ፡፡
.
የፀረሽብር አዋጁ ለምን ወጣ
 
 
     ኢህአዴግ የፀረሽብር አዋጅ እንዲወጣ ያደረገዉ እዉተኛ የሽብር አደጋ ተደቅኖበት አለመሆኑን ለመረዳት ብዙ መጓዝ አያስፈልግም፡፡ በአሽባሪነት የተጠረጠርንና የተፈረደብንን ሰዎች ማንነት ማወቁ ብቻ ይበቃል፡፡ ኢህአዴግ ኢትዮጵያዉያን ላይ እየተፈጸመ ያለዉ ግፍ ይብቃ ብለዉ ስርዓቱ በሌላ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ይለወጥ ዘንድ በሰላማዊ መንገድ ሲታገሉ የነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ በመስርያ ቤታቸዉ ወይም ደግሞ በመኖርያ ቤታቸዉ አካባቢዎች የመንግስት ሀላፊዎች በሚጠሯቸዉ ስብሰባዎች ላይ ደፋር ጥያቄዎችን በማቅረባቸዉ ብቻ ጥርስ የተነከሰባቸዉ የነፃ አስተሳሰብ  ባለቤቶች፣ መንግስት ለአገዛዙ  አመቺ በመሰለዉ መልኩ ሀይማኖታቸዉን ለመበረዝና ለመከለስ ያደርግ የነበረዉን እንቅስቃሴ በሚያስገርም ጀግንነት የመከቱ የእስልምና ሀይማኖት መሪዎችና ተከታዮች እንዲሁም የህዝብ ድምፅ መሆናችንን አምነን ሀላፊነታችንን በአግባቡ ስንወጣ የነበርን  የነፃዉ ፕሬስ አባላት የፀረሽብር አዋጁ ሰለባ ሆነናል፡፡
 
      ይህ የመንግስት ድርጊት አዋጁን ያወጣበት እዉነተኛ ምክንያት በስልጣን ወንበር ላይ ያለምንም ተቺ፣ ተቃዋሚና ተቀናቃኝ ተደላድሎ ለመቀመጥ መሆኑን የሚያሳይ ነዉ፡፡ ይህ አይነቱ አካሄድ ደግሞ ኢህአዴግ የጀመረዉ ሳይሆን እሱን ከመሰሉ አምባገነኖች የኮረጀዉ ያረጀና ያፈጀ አሰራር ነዉ፡፡ የአፍሪካዉያን የቀድሞ ቅኝ ገዢዎች አልንበረከክ ብለዉ ያስቸገሩዋቸዉን የነፃነት ታጋዮች የአሸባሪነት ታፔላ ይለጥፉባቸዉ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ዛሬ ደግሞ ኢህአዴግ ሰብአዊና የዜግነት ክብራችንን ለመጣል እምቢ ያልነዉን የገዛ ሀገሩን ልጆች እስር ቤት ለማጎርና ለማሰቃየት አመቺ ነዉ ብሎ ባመነበት በዚህ የቅኝ ገዢዎች አስቀያሚ መንገድ ላይ እየተጓዘ ነዉ፡፡
 
ምን ይሻላል?
 
   የፀረሽብር አዋጁን በመታከክ ኢህአዴግ እየፈፀማቸዉ ያሉትን የመብት ረገጣዎች ለማስቆም ከባድ ትግል ይጠይቃል፡፡ አሁን ያለዉ  የፀረሽብር አዋጅ ተገቢ በሆነ በሌላ የፀረ ሽብር አዋጅ መተካት ይኖርበታል፡፡ ይህ ባይሆን እንኳን አሁን ያለዉ አይነት ለኢህአዴግ የገበረ የፍትህ ስርዓት እስካለ ድረስ ግን ንፁሀን ዜጎች በአሸባሪነት መታሰራቸዉ አይቀርም፡፡ አሁን ባለዉ የፀረሽብር አዋጅ መሠረት በትክክል ብንዳኝ ኖሮ እንኳን ጥፋተኛ ልንባል የማይገባን ምንም አይነት ወንጀል ያልፈፀምን ግለሰቦች አሸባሪ ተብለን በእስር ላይ መገኘታችን ይህንን መራራ እዉነት የሚያሳይ ነዉ፡፡ በመሆኑም አዋጁንና በይበልጥ ደግሞ አዋጁን ለስልጣኑ ማራዘሚያነት ኢፍትሀዊ በሆነ መንገድ እየተጠቀመበት ያለዉን ኢህአዴግን በማዉገዝ እየተደረጉ ያሉትን የተቃዉሞ ሰልፎችና ሌሎች ሰላማዊ የተቃዉሞ እንቅስቃሴዎች ጠንክረዉ መቀጠል ይኖርባቸዋል፡፡
 
     የተቃዉሞ እንቅስቃሴዎች በዋናነት ኢህአዴግ ላይ ማተኮር እንዳለባቸዉ የማምነዉ በፀረሽብር አዋጁና በአተገባበሩ ብቻ ሳይሆን የሌሎች ለቁጥር የሚያዳግቱ የኢትዮጵያዉያን ችግሮች ምንጭ ራሱ ኢህአዴግ በመሆኑ ነዉ፡፡ ኢህአዴግ ስልጣኑን ለማራዘም የሚረዳዉ እስከመሰለዉ ድረስ ማንኛዉንም አይነት ተግባር ከመፈፀም ወደኃላ የማይል መሆኑን እስኪያንገሸግሸን ታዝበናል፡፡ በሌላ አነጋገር የኢህአዴግ ድርጊቶች ሁሉ ምክንያቶች ( motives ) ከዘረኝነት፣ ከስልጣን ጥመኝነት፣ ካለአግባብ ከመበልፀግና ከመሳሰሉት እኩይ ፍላጎቶች ጋር የተያያዙ ናቸዉ፡፡ “If one”s motives are wrong, nothing can be right” ከሚለዉ የአርተር ጎርደን አባባል እንደምንረዳዉ አንድ ነገር የሚደረግበት ምክንያት ስህተት ከሆነ ትክክል የሚሆን ነገር አይኖርም፡፡ በዚህም ምክንያት ከኢህአዴግ መልካም ነገር መጠበቅ አይቻልም፡፡ በመሆኑም የሚኖረን ብቸኛ አማራጭ የሰለጠነና ሰላማዊ ትግል የሚጠይቀንን መስዋዕትነት ከፍለን ስርዓቱን መለወጥ ነዉ፡፡
 
    ስርዓቱን ስለመለወጥ ስናስብ አብረን ልናስባቸዉ የሚገቡ በርካታ ተያያዥ ጉዳዮች አሉ፡፡ ስርዓቱን ለመለወጥ በምንሄድበት መንገድ ላይ ገዢዉ ፓርቲ ያስቀምጣቸዉን በዘር፣ በሀይማኖት፣በፖለቲካ ርዕዮተ ዓለምና በጥቅም የመከፋፈል እንቅፋቶች እንዴት ማለፍ እንደምንችል በጥልቀት አስቦ መንቀሳቀስ ግድ ይላል፡፡  በየአቅጣጫዉ የተበታተኑ እንቅስቃሴዎችን ከማካሄድ ይልቅ በህብረት ሆነን መታገል መቻል ይኖርብናል፡፡ ከኢህአዴግ በኋላ ስለሚመሰረተዉ ስርዓትም በደንብ ማሰብና መመካከር የሀገሬ ጉዳይ ይመለከተኛል ከሚል ማንኛዉም ሀላፊነት ከሚሰማዉ ዜጋ በተለይም ደግሞ የተቃዉሞ እንቅስቃሴዎችን ከሚመሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ሌሎች አካላት ይጠበቃል፡፡ የሚጠበቅብንን ሁሉ እስካደረግንና በፅናት እስከቆምን ድረስ ደግሞ ብሩህ ቀን የምናይበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም፡፡
 
ምንልክ ሳልሳ  https://www.facebook.com/minilik.salsawi
 

No comments: