Thursday, August 8, 2013

በምድረ – ኢትዮጵያ ያለው አሸባሪ ወያኔና ወያኔ ብቻ ነው!!

የወያኔ አገዛዝ ባለፈው ሳምንት መገባደጃ ላይ ያወጣው የእብሪት ማስፋራሪያና ዛቻ ቀለም ሳይደርቅ ያ የለመዱ እጁ አሁንም በንጹሃን ወገኖቻችን ደም ተጨማልቋል። የወያኔ እብሪት የሰው ልጅ ሊሸከም የሚችለውን ለከት አልፏል። አንድ አመት ከመንፈቅ ሙሉ ጠጠር ሳይወረውር መብቴን፣ ስብእናዬን፣ መሰረታዊ መብቴንና ነጻነቴን ብሎ ህገ-መንግስት እየጠቀሰ አቤት ስሙን ያለ ህዝብ በምን መለኪያ አሸባሪ ሊሆን ይችላል? ለመሆኑ ህፃን፤ሽማግሌ፤ ወንድና ሴት ሳይለይ ያገኘዉን በሙሉ በጥይት የሚቆላዉ ወያኔ ነዉ ወይስ መብቴንና ነጻነቴን አክብሩልኝ ብሎ በትእግስትና በጨዋነት የጠየቀ ህዝብ ነዉ ሽብርተኛ መባል ያለበት መልሱን ወያኔን በጭፍኑ የሚደግፉትን ጨምሮ ህሊና ላለው ዜጋ ሁሉ እንተዋለን።
ዋናው ጥያቄ መሆን ያለበት ይህንን እብሪትና እብጠት እንዴትና መቼ እናቁመው የሚለው ነው። ወያኔ የፈሪ አክራሪ ነው። ታገሱኝ፣ አፈግፍጉልኝ፣ አክብሩኝ እያለም እንኳን ከጭካኔ የሚያቆም ህሊና በሌላቸው ደነዞችና ጨካኞች የተሞላ ዘረኛ ተቋም ነው። ዛሬ የሚቀማጠሉበትን ስልጣንና ምቾት ይነካብናል፣ እንቅልፍ ይነሳናል ያሉትን የህዝብ ትንፋሽን ሁሉ ፀጥ ለማድረግ መወሰናቸውን ካየን ከሰማን ውለን አድረናል። በወያኔ መንደርና አገዛዝ በገዛ ሀገራችን ቀና ብለን መሄድ፣ በትውልድ መንደርና ቀያችን መኖር፣ በዜግነታችን የሚገባንን መሰረታዊ ጥያቄ ማንሳት ሽብርተኞች አሰኝቶ በጥይት የሚያስቆላና በወህኒ የሚያሰበስብ ወንጀልና ሀጢያት ከሆነ ዉሎ አድሯል። ህግና ህገ-መንግስቱ ተብዬዉ የተጻፈበትን ወረቀት ያህል እንኳን ዋጋ ካጣ ሰንበትበት ብሏል።
ሰሞኑን ኮልፌ ዉስጥ በንጹሃን የእስልምና እምነት ተከታይ ወገኖቻችን ላይ ወያኔ የፈጸመው ግፍ የሚዘገንን ጭካኔ ይሁን እንጂ ከወያኔ አረመኔዎች የማንጠብቀው አይደለም። ወያኔ እያሸበረን አሸባሪ ሲለን፣ እየገደለ ገደሉ ሲለን፣ በክብር ስንለምነው እያዋረደን እንደ ህዝብ ሳይሆን እንደ መንጋ እየተቆጣጠረ ሊገዛን ቆርጧል። ወያኔ ከሰዉነት ደረጃ ወጥተን ወደ እንስሳነት ተለዉጠን ሃይማኖታችንን ጭምር እሱ መርጦልን፣ ልማትና እድገትን ከእኔ ዉጭ ከሌላ አትጠብቁ እያለበረሃብ እያለቅን ጠገብን እያልን አጎንብሰን እንድንኖር ይፈልጋል። ባለፈዉ ሳምንት ያሰራጨዉ የማስፈራሪያ መግለጫና ፀረ-ሽብርተኛ የሚለው ህግ አላማም ይሄዉ ነው። ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ መሪዎች፣ የሐይማኖት አባቶች፤ ወጣቶችን ባጠቃላይ ሰላማዊ ታጋዮች፣ የኢትዮጵያን እስር ቤቶች የሞሉት ይህንን የወያኔን ፀረ ህዝብና ፀረ አገር ድርጊትና አላማ ስተቃወሙ ብቻ ነው።
ለወያኔ ግፍና በግፈኝነቱ እንዲቀጥል በከፊል ተጠያቂዎች የሆንን የዚች ሀገር ዜጎች ሁሉ አስተዋጽኦ አላደረግንም ማለት አይቻልም። ነግ በኔ ማለት አቅቶን ዛሬ አንዱን ሲያጠቃ፣ ሲገድልና ሲያስር ሌሎቻችን ዝም እያልን በየተራ ለመጠቃትና ለመዋረድ ተመችተነዋል። ሙስሊሙ ሲጠቃ ክርስቲያኑ ተመልካች ይሆናል። ክርስቲያኑ ሲጠቃ ሙስሊሙ ይመለከታል። ኦሮሞው ሲቀጠቀጥ አማራው ይመለከታል። አማራው ሲወገር ኦሮሞው ቆሞ ያያል። በሌላ አነጋገር ሁላችንም በቃ ብለን በአንድ ላይ መነሳት አቅቶናል። ወያኔ ትላንት ላፈሰሰው ደም ሂሳብ ስላልከፈለ ነው ደግሞና ደጋግሞ ደማችንን የሚያፈሰው። አንድ ሆነን ከመታገልና ከመነሳት ውጭ አማራጭ እንደሌለን የዘነጋነው ይመስላል። አንድ ሆነን የተነሳን እለት ወያኔ ምን ያህል ኢምንት ሃይል እንደሆነ ማየት አቅቶናል።
ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ጥቃትንና ውርደትን መሸከም፣ መስማትና ማየት፣ መሰደድና መታሰር፣ መንገላታቱ ያንገፈገፈህ ወገን ሁሉ፤ ስለ ሀገርህ፣ ስለማንነትህ ህልውና ስትል አንድ ሆነህ ለመነሳት ጊዜው አሁን ነው፤ ፈርጣማ ክንድህን የምታሳይበት፣ የአበውን እምቢና አልገዛም ባይነት ለዘረኛው ወያኔ የምታሳይበት ጊዜ ዛሬ ነዉ እንላለን፤ እኛ የወያኔን ማንነት በቅጡ የተረዳን የግንቦት 7 ንቅናቄ ልጆችህ።
በኢትዮጵያ መሬት ላይ ያለው አሸባሪ ወያኔና ወያኔ ብቻ ነው!! ከወያኔ ውጭ አለምአቀፍም ሆነ ሀገረኛ አሸባሪ በሀገር ውስጥ የለም። ወያኔ አሸባሪ የሚለን አለም አቀፋዊ ልመናው እንዳይቆም ብቻ ነው። ሊበላን የፈለገው አሞራ ስለሆንን ብቻ ነው ጅግራ የሚለን።
ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ የሀገራችን ህዝብ ሁሉ በአንድነት የነጻነት አሞራዎች እንድንሆን ዛሬም ጥሪውን በድጋሜ ያቀርባል። ሽብርተኛው ወያኔ፣ ህግ፣ ሰበአዊነት፣ ስልጡን ፖለቲካ ቀርቶ ተራ ይሉኝታ የሌለው፣ በልቼ ልሙት ወይም እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል ብሎ የቆረጠ ዘረኛ ቡድን ነውና ልናስወግደው የግድ ይለናል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments: