Thursday, August 29, 2013

“በሬ ሆይ ሳሩን አየህና ገደሉን ሳታይ” እንዳይሆን እንጠንቀቅ

ቢከፍቱት ተልባ የሆነውና ላይ ላዩን ሲያዩት ልማት የሚመስለው የወያኔ ኢኮኖሚ “ልማትና እድገት” የገንዘብ ካፒታል የሚያገኘው እንደሌሎቹ በእድት እንደሚገሰግሱ ታዳጊ አገሮች የእንዱስትሪ ሸቀጥ አምርቶ ለአለም ገቢያ አቅርቦና ሽጦ አይደለም። ተሰራ የተባለው ብልጭልጭ ነገር ሁሉ የሚሰራው የድህነት ጌቶች “Lords of Poverty” በሆኑት አለም አቀፍ ተቋሞችና ሀገሮች በሚገኝ እርዳታ ነው። ወያኔ እራሱ በፈጠሩ ችግር ተሰዶ በውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊም ለወዳጅ ዘመድ የሚልከው የውጭ ምንዛሬም ሌላው የወያኔ የገንዘብ ምንጭ ነው። በዚህ ላይ የሀገሪቱ የተፈጥሮ ሀብት የሆነውን ለም መሬት በገፍ ለባዕድና ለሀገር ውስጥ የወያኔ ቤተኞች በመቸብቸብ የሚገኝ ገንዘብ አለ። መቼም ኢትዮጵያዊው በገዛ ሀገሩ የኩርማን መሬት ባለርስትና መብቱ ከተነጠቀ ቆይቷል። ዛሬ ኢትዮጵያ ዉስጥ ባለርሰተቹ ወያኔና ጉጅሌዎቹ ብቻ ናቸው።
የሀገሪቱ የገንዘብ ሀብት ብዙ ጊዜ የሚገባው ከግርጌው በተቀደደ ቋት ውስጥ ስለሆነ ለዘላቂ ልማትም ሆነ ገንዘቡን ለሚቀራመቱት ወያኔዎች በቂ አልሆነም።
ይህንን ቀዳዳ ቋት ለመሙላት ወያኔ ሰሞኑን የፈጠረው ዘዴ ህዝቡን የቤት ባለቤት ላደርግህ ስላሰብኩ አስቀድመህ ገንዘብህን አምጣ የሚል ዘዴ ነው። ሃያ-ሰማኒያ አርባ-ስልሳ ወዘተ የሚል ዘዴ ተገኝቷል። ይህ አርባ ስልሳና ሃያ ሰማንያ የሚሉት ፈሊጥ የኢትኦጵያ ደሃ ህዝብ ነገ ያልፍልኛል እያለ ሆዱን ቋጥሮና አንጀቱን አስሮ ያፈራትን ገንዘብ እንዲሰጣቸው የታለመ የጮሌዎች የገንዘብ መሰብሰቢያ ዘዴ ነዉ።
በተለይ የውጭ ምንዛሬ ያስገኛል ተብሎ የታመነበት 40/60 የሚባል ዘዴ በየኢምባሲው በወረቀት ላይ በተሰሩ ቆንጆ የቤትና የኮንዶሚኒየም ንድፎች አሸብርቆ መጥቷል።
ይህችን የጭልፊት ኢኮኖሚ ማየት የተሳናቸው የዋህ ኢትዮጵያውያን በየባዕድ ሀገሩ ለፍተው ያፈሯትን ጥሪት ይዘው በየኢምባሲው ለምዝገባ ሲጋፉ ማየት እጅግ በጣም ያሳዝናል። ብዙ ኢትዮጵያውያን ይህንን የዝርፊያ ኢኮኖሚ የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ በሚል ፈሊጥም የገቡበት አሉ። ራሳቸውንም ሀገራቸውንም እያዘረፉ መሆኑ የገባቸው አይመስልም። ወያኔ ይልቁንም የገቢያው መድራት ስላስጎመጀው ለውጭ ነዋሪ ያዘጋጀውን 40/60 አቁሞ የተሻለ ጥቅም የሚያስገኝ መንገድ እያሰላ ነው።
ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ይህን የድቡሽት ላይ ቤት እንሰራለን ብለው ያሰቡ ወገኖች ሁሉ የወያኔን ቀዳዳ ኪስ ከመሙላታቸው በፊት ጥቅሙን፤ ጉዳቱንና ትርጉሙን አገላብጠው እንዲያዩ ይመክራል። በተለይ በወያኔ ስር በሚገኝ ንብረት ያልፍልኛል ብለው በስደት ኑሮ ያፈሩትን ገንዘብ የነጻነታቸዉ መያዣ ተደርጎ ለባሰ ውርደት እንዳይዳርጋቸው ግንቦት ሰባት ወገናዊ ምክሩን ይመክራል።
ቤት አልባ ሆኖ በየመንገዱ ላይና በየደሳሳ ጎጆዉ ታጉሮ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ወገናችን በየዕለቱ እየጨመረ ባለበት በአሁኑ ወቅት ከነሱ እየተዘረፈ በሚሸጥ ንብረት ሀብት ለማፍራት መሞከር ለህሊናም የሚቀፍ ነው።
የወያኔ የቤት ስራ ፕሮጀክት ገንዘብ መልቀሚያና ጥቂት ባለሟሎቻቸውን መጥቀሚያ እንጂ ለዚህ ሁሉ የውጭ ነዋሪ የሚደርስም አይደለም። ወያኔ አስቀድሞ ከወለድ ነጻ የሆነ ገንዘብ ከሰበሰበ በኋላ ገንዘቡን ተጠቅሞ ከአምስትና አስር አመት በኋላ ቤቱንም ገንዘቡንም ማግኘት ላይቻል ይቻላል። ወያኔም ተጠያቂነትን የማይወድ አገዛዝ መሆኑን ካሁኑ አለመገንዘብም ራስን ጨፍኖ ለመሞኘት መፍቀድ ነው።
የወያኔ 40/60 ገንዘብ መሰብሰቢያ እንጂ ህዝብ መጥቀሚያ አይደለም። ወያኔዎች ሊጠቅሟቸው የሚፈልጉ ዜጎችን ከፈለጉ በየጎዳናው ላይ ያገኟቸዋል ለምን እነሱን አየረዷቸዉም?
በተለይ በውጪ የምንኖር ኢትዮጵያውያን በፍጹም ድህነትና የወያኔ ዝርፊያ ተዋርዶ የሚኖረውን ህዝባችንን እያየን የዚህ ግፈኛ መንግስት መሳሪያ ከመሆን አልፈን ራሳችንንም ለተዋራጅነት እንዳንዳረግ እንጠንቀቅ!
ድል ለኢትዮጵያ ሀዝብ!!

No comments: