Thursday, August 1, 2013

“ላባዋን ሳይሆን ክንፏን!” ሀይሌን ሳይሆን-የሀይሌን አስተሣሰብ (በደረጀ ሃብተወልድ)

ከጥቂት ጊዜ በፊት፤ማለትም ሀይሌ ፕሬዚዳንት የመሆን ፍላጎት እንዳለው ለመጀመሪያ ጊዜ ፍንጭ የሰጠ ሰሞን አንድ ጽሁፍ ጽፌ ነበር። የጽሁፉ ርዕስ ፦”ሀይሌ ፕሬዚዳንት እንዲሆን ስንት ጊዜ መሰደብ አለብን?” የሚል ነበር።ጽሁፉን ለድረ-ገጾች ለመላክ እያሰብኩ ሳለ- ለሀይሌ የነበረኝ ፍቅር ክፉኛ አዕምሮዬን ሞገተኝ። እናም ሳልልከው ተውኩት። እነሆ ከዓመታት በሁዋላ ሀይሌ ወደ አቶ ግርማ ወንበር እየተንደረደረ እንደሆነ በስፋት እየተወራ መሆኑን ሳይ-ያን  ጽሁፍ ማውጣት ነበረብኝ የሚል ቁጭት ውስጥ ሳልገባ አልቀረሁም።ይሁንና ነገሩ አንዴ አልፏል።

 በጽሁፉ ከተጠቀሱት ነጥቦች መካከል፦ ሀይሌ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ኔትወርክ ቀርቦ ከአርቲስትና አክቲቪስት ታማኝ በየነ ጋር ቃለ-ምልልስ ሲያደርግ ፦ “እህል ጠግቦ ላልበላው የኢትዮጵያ ህዝብ ዲሞክራሲ ምን ያደርግለታል?” ማለቱ፣ ከሸራተን አካባቢ ለልማት ተብለው ከዘመናት ይዞታቸው በግዳጅ የተፈናቀሉ በዕድሜ የገፉ አባትና እናቶች በተወሰደባቸው እርምጃ ማልቀሳቸውን አስመልክቶ በኢቲቪ ለቀረበለት ጥያቄ፤ “…እነዚህ ዜጎች የተሻለ ቤት ይሰጣችሁዋል ሲባሉ ከድሪቷችን ጋር ነው የምንኖረው ማለታቸው አስገራሚ ነው” ብሎ አስተያየት መስጠቱ፣ መምህራን የደመወዝ ጥያቄ አንስተው ተቃውሞ ማቅረባቸውን- ከስንፍና ጋር አያይዞ መዝለፉ፣የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ይፋ ሲሆን- ጉዳዩን በ 5000 እና 10000 ሜትር ሩጫ በማስላት እቅዱን ለማሳካት አምስት ዓመት ሲበዛ ነው ማለቱ ይገኙበታል።


 ሰሞኑን አንዳንድ የፌስቡክ ጓደኞቼ - እንደ ሀይሌ ያሉ ታዋቂና ስመ-ጥር ሰዎች ወደ ፖለቲካው በመግባት ተሳትፎ ቢያደርጉ ለውጥ ሊያመጡ ይችላሉ የሚል አስተያየት ሢሰጡ እየተመለከትኩ ነው። እነዚህን ጓደኞቼን ግራ ያጋባቸው ጉዳይ ሀይሌ ወደፖለቲካ መግባቱ ሳይሆን- በኢትዮጵያ መንግስታዊ አወቃቀር መሰረት ብዙም ሚና በሌለው የፕሬዚዳንትነት ወንበር ላይ ተቀምጦ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ ማሰቡ ነው። በእርግጥ ታዋቂና ስመ-ጥር ሰዎች በፖለቲካው መስክ መሳተፋቸው የሚበረታታ ነው። ይሁንና ለኔ ሀይሌ እንደተመኘው ሹመት ቢያገኝ አገሪቱ የምትፈልገውን ለውጥ የማያመጣው ፤ “ፕሬዚዳንት” በመሆኑ ብቻ አይደለም።“ጠግቦ ላልበላ ህዝብ ዲሞክራሲ ምን ያደርግለታል?”ብለው የሚያስቡ እንደ ሀይሌ ያሉ ታዋቂ ሰዎች በማናቸውም ስልጣን ላይ ቢቀመጡም፤ ዕዳችንን ያከብዱትና ብስጭታችንን ያባብሱት ካልሆነ በስተቀር የኢትዮጵያ ህዝብ የሚፈልገውን በጎ ለውጥ ሊያመጡ አይችሉም። በጎ ለውጥ የሚመጣው በ“ታዋቂነት” ሳይሆን በዕውቀት እንዲሀም በቅንና በብሩህ አመለካከት ነው።

 ስለሆነም …በተለይ …በተለይ…፦” ጠግቦ ላልበላ ህዝብ ዲሞክራሲ ምን ያደርግለታል?” የሚል አመለካከቱ አሁንም እንደዚያው ከሆነ(ካልተቀየረ) ፤ ሀይሌ ፕሬዚዳንቴ እንዲሆን ፈጽሞ አልፈልግም! የኢትዮጵያ ህዝብ ዲሞክራሲ ይገባዋል ብሎ እስካላመነ እና ይህን እምነቱን በይፋ እስካላሳወቀ ድረስ-ሀይሌ ፕሬዚዳንት ለመሆን የሚያደርገውን ሩጫ እቃወማለሁ!!

No comments: