Sunday, August 4, 2013

በኦሮሚያ አርሲ ዞን የሟቾች ቁጥር 11 ደርሰ!

August 4, 2013
 Free Our Heroes

አንዲት ሴት እና ህጻን ልጅ ከሟቾቹ ውስጥ ይገኙበታል!

ትናንት ማለዳ ጀምሮ የመንግስት ታጣቂዎች በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ገብተው በሰነዘሩት ጥቃት የሟቾች ቁጥር 11 ደርሰ፡፡ ከሻሸመኔ እስከ ኮፈሌ እና ዶዶላ ድረስ በሚያካልለው በዚህ የመንግስት ወታደሮች ጥቃት ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው እና የታሰሩ ሰዎች ቁጥርም በከፍተኛ ሁኔታ አሻቅቧል፡፡ በእለተ ቅዳሜ ምንም አይነት ተቃውሞም ሆነ መሰል እንቅስቃሰሴዎች በማይካሄድበት እና ባልተካሄደበት እለት የመንግስት ወታደሮች እስከገጠር ቀበሌዎች ድረስ ዘልቆ በመግባት ያለርህራሄ የቀጥታ ጥይት በመጠቀም የአካባቢውን ዜጎች ሲገድሉ ውለዋል፡፡

የመንግስት ቴሌቪዥን በተለመደ መልኩ ‹‹ጂሀድ ሲቀሰቅሱ እርምጃ ተወሰደባቸው›› የሚል ዜና ያሰራጨ ሲሆን የሞቱት ሰዎች ቁጥርም 3 ብቻ መሆኑን ገልጾ ነበር፡፡ መንግስት ቀድሞ በታሰበበት መልኩ በአካባቢው ከፍተኛ የወታደር ሰፈራ በማድረግና በተጠንቀቅ በማስቆም በፌዴራል ፖሊስ፣ አድማ በታኝ እና በወታደሮች በመታጀብ በአካባቢው ሕዝብ ላይ ከማለዳ ጀምሮ ጥቃት ሰንዝሯል፡፡ አራት ኦራል መኪኖች ላይ የተጫኑ ወታደሮች አካባቢውን በመክበብ መስጂዶች እና መኖሪያ ቤቶች ላይ ጭምር ጥይት ሲተኩሱ እንደነበር የታወቀ ሲሆን በዚሁም የአካባበውን ታዋቂ የሃይማኖት መምህር፣ አንዲት ሴት እና ህጻን ልጅን ጨምሮ የሟቾች ቁጥር 10 ደርሷል፡፡ የፌዴራል ፖሊስ አባላት የራሳቸውን መኪና መስታወት በመሳሪያ ሰደፋቸው በመስበር ‹‹ሕዝቡ ሰበረው›› የሚል ፕሮፖጋንዳ ለመስራት የሚያስችል ጥረት ሲያደርጉም ታይተዋል፡፡

መንግስት ምላሽ መስጠት የተሳነውን ሕገ መንግስታዊ የህዝብ ጥያቄ በጥይት በዚህ መልኩ ምላሽ ሲሰጥ ይህ የመጀመሪያው አይደለም፡፡ ባለፈው አመት በአርሲ ዞን አሳሳ ላይ ተመሳሳይ ጥቃት ፈጽሞ አራት ሰዎች መገደላቸው ይታወቃል፡፡ ከዚያም በመቀጠል በአማራ ክልል ገርባ ከተማና በሐረር ኢማን መስጂድ ላይ ተመሳሳይ ጥቃት ፈጽሞ በድምሩ ከ13 ሰዎች በላይ ህይወታቸው በመንግስት ታጣቂዎች ጥይት ተቀጥፏል፡፡ መንግስት የገደላቸውን ሰዎች በሙሉ ‹‹ለጂሃድ ሲያነሳሱ ገደልኳቸው›› የሚል ማስተባበያ ሲሰጥ ቢቆይም ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አሁንም ይህ የመንግስት ጭካኔ የተሞላበት ጥቃት ቀጥሏል፡፡

አሁንም ሙስሊሙ ኅብረተሰብ መንግስት ሊፈጥር እያሰበ ያለውን ተጨማሪ ኹከት በመገንዘብና ሊፈጠር የሚችለውን አደጋ በማሰብ የመንግስትን ትንኮሳ ቸል እንዲልና በትእግስት እንዲያሳልፍ አስቸኳይ መልእክት እናስተላልፋለን፡፡ የመንግስት ቀዳሚው ፍላጎት መጀመሪያ እንደታየውም ኹከትና ግጭት በመፍጠርና ጥፋት በማድረስ፣ ሙስሊሙን ኅብረተሰብ ለመወንጀልና ለፕሮፖጋንዳ ፍጆታ ለመጠቀም በመሆኑና ይህም በሁሉም ዘንድ የሚታወቅ በመሆኑ፤ መንግስት ኹከት ሲቀሰቅስ በቸልታና አይቶ በማሳለፍ በመንግስት ወጥመድ ላለመውደቅ ሁሉም ጥረት እንዲያደርግ እንጠይቃለን፡፡ ከምንም በላይ ሰላማዊነታችን ዋጋ የምንሰጠው መሆኑን ሁላችንም ከግንዛቤ በመክተት ሰላማችንን ሊነጥቁ የሚመጡ ኃይሎን በሰላም ብቻ እነድንመልሳቸው አደራ እንላለን፡፡

No comments: