Thursday, August 15, 2013

የአቶ መለስ መሞት ወደ ውጭ በወጣው 11 ቢሊዮን ዶላር ምርመራ ላይ ተጽኖ መፍጠሩ ተገለጸ

ነሃሴ ፱(ዘጠኝ)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከኢትዩጵያ በህገ ወጥ የተሻገረውን 11 ቢሊዩን ዶላር ለማስመለስ እና የባለስልጣናትን የሀብት መጠን ይፋ ለማድረግ የተያዘው ቀጠሮ በመለስ ሞት ምክንያት ዳር ሳይደርስ መቅረቱን የስነ ምግባር እና ፀረ ሙስና ኪሚሺን ኪሚሺነር አቶ ዓሊ ሱሊማን ተናገሩ፡፡

አቶ አሊ በጠቅላይ ሚኒስተር መልስ ዜናዊ የስራ ትጋት እና አርቆ  አሳቢነት ምስክርነት ለመስጠት በ ኢቲቪ የፖሊስ ፕሮግራም ላይ በተጠየቁበት ስዓት ነው ይህን የተናገሩት። ይሁን እንጅ የፖሊስ ፕሮግራም  መረጃውን እስካሁን ለህዝብ ይፋ አላደረገውም።

የስነ ምግባር እና ፀረ ሙስና ኪሚሺን ኪሚሺነር አቶ ዓሊ ሱለይማን ከመለስ ሞት ጋር በተያያዘ ጥያቄ ቀርቦላቸው ሲመልሱ የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሐብት ተጣርቶ የተጠናቀቀ ቢሆንም እስካሁን ይፋ ማደርግ አልተቻለም።  ‹‹የመለስ ሀብት  ቀርቶ የአኗኗራቸውን ሁኔታ እንኳ ምን እንደሚመስል የኢትዮጵያ ሕዝብ ተመልክቶታል፡፡ የመለስን ማንነትና የአኗኗር ሁናቴ ከማንም ያልተለየ ስለመሆኑ ከሞታቸው በስተጀርባ ተመልክተነዋል ያሉት አቶ አሊ፣

‹‹መለስ ይህ ነው የሚባል በምዝገባ የሚታወቅ ሀብት የላቸውም፡፡ እንግዲህ ወደፊት ታሪክ የሚያወጣቸው እና የሚዘክራቸው በርካታ እውነታዎች ይኖራሉ›› በማለት የአቶ መለስን ሀብት ይፋ ለማድረግ የሳቸው መሞት አሉታዊ ተጽኖ ማሳደሩን ገልጸዋል። ‹‹መለስ ምንም አልነበራቸውም›› ሲሉም አቶ አሊ አክለዋል፡፡

በኢትዩጵያ የፀረ ሙስና ተቋም የተቋቁመው በሕዝብ ፣ በዕርዳታ ሰጪ አገራት  እና በዓለማዓቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ግፊት መሆኑን የጠቀሱት አቶ አሊ፣  በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አሳሳቢነት ኮሚሽኑን መንግስት ሲያቋቁም የማስተማርና የመመርመሩን ስልጣን ሰጥቶ የመክሰሱን ስልጣን ላለፉት አመታት ሳይሰጥ መቆየቱን ጠቁመዋል።

‹‹መደበኛውን የገንዘብ ዝውውር ባልተከተለ መልኩ በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ወደ ውጭ ባንኮች 11 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ እንደ ሸሸ ግሎባል ፋይናንሺያል ኢንተግሪቲን ዋቢ በማድረግ የተለያዩ የኅትመት ውጤቶች አሰነብበዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር መወያየታቸውን የገለጹት አቶ አሊ ሱሊማን፣‹‹መጠኑ 11 ቢሊዮን ብር የሚደርስ ይሁን አይሁን ማረጋገጫ የሚሻ ጉዳይ ሆኖ ሀገሪቱ በዚህ ገንዘብ መጠን ተርፎ የሚሸሸ ሐብት አላት ዎይ? የሚለውም ምላሽ የሚሻ ጉዳይ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ችግሩ በየትኛውም ሀገር ያለ ነው ያሉት ኮሚሺነር አሊ ፣ የገንዘቡ መጠን ምንም ያህል ቢሆንም በጉዳዩ ላይ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ውይይት አድርገው እንደነበር አጽንኦት ሰጥተው መነጋገራቸውን ገልጸዋል፡፡

ጠ/ሚኒስትሩ  የተጠቀሰው ገንዘብ መጠን አንድ መቶኛም ቢሆን በተባለው መንገድ የሚንቀሳቀስ ስለመሆኑ አስተማማኝ መረጃ ይገኝ እንደሆን ችግሩን ለመጋፈጥ መረጃውን ከለቀቀው ተቋም ዘንድ እንዲረጋገጥ ቁርጠኛ አቋም ይዘው እንደነበረ አቶ ዓሊ ተናግረዋል።  ይህንንም ተከትሎ ኮሚሽነር ዓሊ ለዓለም ባንክ ስብሰባ በሰኔ ወር መጨረሻ አካባቢ ዋሽንግተን ሄደው በነበረበት ወቅት መረጃውን እንዳወጣ ከተነገረለት ግሎባል ፋይናንሺያል ኢንተግሪቲ ተቋም ኃላፊዎች ጋር ተነጋግረው እንደተመለሱ ስለደረሰበት ሁኔታ ለመነጋገር ቀጠሮ እንዲያዝላቸው ባደረጉበት ወቅት የጠቅላይ ሚኒስትሩን ህመም ሲሰሙ እንደተውት እና ጠቅላይ ሚንስትሩ ህይወታቸው ቢያልፍም በሂደት የሚኬድበት ጉዳይ እንዲሆን  ገልፀዋል፡፡

ችግሩን ሙሉ ለሙሉ ማስወገድ ባይቻልም በአስመጪና ላኪዎች  እና በሌሎችም ክፍተት ባላቸው ሂደቶች ላይ አሰራሩን በማጠናከር ችግሩን ለመቀነስ እንደሚሰሩም አስገንዝበዋል፡፡አቶ መለስ ዜናዊ በ6 ሺ ብር ደመዎዝ ብቻ ይተዳደሩ እንደነበር ወ/ሮ አዜብ መናገራቸው ይታወሳል።

ይሁን እንጅ ከሁለት አመታት በፊት አንድ የስፓኒያ ጋዜጣ ወ/ሮ አዜብ በአፍሪካ ካሉ ቀዳማይ እመቤቶች  በአባካኝነት ከሚጠቀሱት በግንባር ቀደምነት ከሚጠቀሱት አንዷ መሆናቸውን ገልጾ ነበር።
ጸረ ሙስና ኮሚሽን አቶ መለስ ከሞቱ ከአንድ አመት በሁዋላም ከአቶ መለስ ውጭ ያሉትን ባለስልጣኖች ሀብት ይፋ አላደረገም። ህዝቡ በአገኘው አጋጣሚ ሆኑ ኮሚሽኑ የባለስልጣኖችን ሀብት ይፋ እንዲያደርግ ሲጠይቅ ቆይቷል።

No comments: